Quantcast
Channel: Zehabesha Amharic » Opinion & Analysis
Viewing all 1664 articles
Browse latest View live

አያ ተክሌ ምነዉ አህያዉን ትተዉ ፈረሱን ቢጋልቡ

$
0
0

 በደርብ ከፈለኝ

አዋቂ መስሎኝ ሰምቼዉ
ትልቅ ሰዉ መስሎኝ ተጠግቼዉ
በቃኝ . . . በቃኝ  አወቅኩትና  ናቅኩት
ለካስ ወዳጄ ኖሯል ፈረስ እየናቀ አህያ የሚጋልብ
በሬ እያቀጨጨ ጅብና ድብ የሚያደልብ

comment picከላይ አያ ተክሌ ብዬ የጀመርኩህ ተሳስቼ ነዉ። ከአሁን በኋላ ግን አቦይ ተክሌ ብዬ ነዉ የምጠራህ። አይዞህ “አቦይ” ያልኩህ እንደ አቦይ ስብሐት አርጅተህብኝ አይደለም። አወቃለሁ አንድ ፍሬ ልጅ ነህ . . .  አዎ ልጅ ነህ . . .  አሁንም ልጅ!  “አቦይ” ብዬ ሹመት የሰጠሁህ  አነጋገርህ፤ አስተሳሰብህና እንዳዉ አኳኋንህ ሁሉ ከአቦይ ስብሐት ጋር ስለተመሳሰለብኝ ነዉ፤ ወይም እንደ አቦይ ስብሐት ቀላማጅ ነህ ትቀለማድለህ ማለቴ ነዉ። አቦይ ተክሌ ምንም ቢሆን የቅርብ ጓደኛዬ ነህና የጓደኝነቴን ምክር ቢጤ ልሰጥህ እስኪ ስማኝ። አቦይ ስብሐት ሃያ ሁለት አመት ሙሉ ቀላምደዋል፤ ከአሁን በኋላ ልቀላምድ ቢሉም አንድ ሐሙስ ነዉ የቀራቸዉ። አንተ ግን አንድ ፍሬ ልጅ ነህ፤ እንግዲህ ይታይህ 35 አመት፤ 40 አመት፤ 50 አመት፤ ስልሳ አመት እያልክ ወዳጅና ጠላት፤ዘመድና ባዳ ፤ ጎረቤትና የማዶ ሰዉ ሳትለይ ይህንን ሁሉ አመት እየቀላመድክ ልትኖር ነዉ . . .  ያዉም በዚህ እንደ አሞራ በሚበርረዉ የዳያስፖራ ኑሮ። ምነዉ ተክሌ ቢቀርብህ!  መዶሻ የያዘ ሰዉ ሁሌም የሚመለከተዉ ሚስማር ብቻ ነዉ ሲባል ሰማሁና መዶሻ የያዘ ሰዉም መሰልከኝ፤ አሁን ግን በደንብ አድርጌ ሳይህ መዶሻ የያዘ ሰዉ ሳይሆን ጭራሽ መዶሻዉን እራሱን መሰልከኝ።

 

“ዬት ይደርሳል የተባለ ጥጃ ሉካንዳ ታየ” . . .  አያ ተክሌ . . .  ይቅርታ አቦይ ተክሌ ማለቴ ነዉ . . . ይህ ስንኝ የተቋጠረዉ ለሌላ ለማንም ሳይሆን ላንተ ብቻ ይመስለኛል። እስኪ ንገረኝ ተክሌ ምነዉ የነካሄዉ ነገር ሁሉ አይበረክት ወይ አንተ አትበረክት። እስኪ መለስ ብለህ አስበዉ ECADF፤ EHSNA፤ ESAT TV ፤ ESAT Radio ሁሉንም ነካ ነካ ግን አንዱንም ሳታረካ አንተም ሳትረካ እንዳዉ ዉኃ ላይ እንደተንሳፈፈ ኩበት ባክነህ ቀረህ። ምነዉ ወንድሜ ተክሌ እንዲህ ነበር እንዴ እኔና አንተ የምንተዋቀዉ? ምን ላድርግ እንደዛ ማታ ማታ እንደምንጫወትበት ካርታ ተበዉዝክብኝኮ። ምነዉ ተክሌ የተደበቀዉ ጸባይህ እየወጣ ነዉ ወይስ ድሮ ሳዉቅህም እንዲህ ወናፍ ነበርክ? ተክሌ ከሁሉም ከሁሉም የምታናድደኝ ደርሶ አዋቂ ለመመሰል  ቱግ ቱግ ስትል ነዉ፡፡ ዉድ ጓደኛዬ ተክሌ እባክህ ተረዳኝ እኔ አዋቂ አትሁን ማለቴ አይደለም፤ ግን አዋቂ ለመሆን አዋቂ ሁን እንጂ አዋቂ አትምሰል። ደግሞም ቱግ ቱግ እንኳን ባንተ በእንደኔ አይነቱ አንድ ክንድ ከስንዝር በማትሞላዉ ባንተ በሸበላዎቹም አያምርም። ስለዚሀ ተክሌ እባክህ እንዳቅምህ . . .  አዎ እንዳቅምህ!

 

በያ ሰሞን በየድረ ገጹ እየገባሁ  ያገኘሁትን ሁሉ ሳነብ አንተም የሞነጫጨርከዉን አገኘሁና አንብቤዉ በጽሁፍህ ሳይሆን በጓደኝነትህ አፈርኩ። እስኪ ንገረኝ ተክሌ ምን ይሁን ብለህ ነዉ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዉን ፖለቲካ አትተንትን ያልከዉ፤ እናስ ምን ይተንትንልህ? እኮ ንገረኝ ተክሌ የፖለቲካ ፓርቲ መሪ ፖለቲካ ካልተነተነ ሌላ ምን ይተንትን?  ለመሆኑ ያልተተነተነ ፖለቲካ ምን አይነት እስትራቴጂ ነዉ የሚወጣለት? ምነዉ ተክሌ “አወቅሽ አወቅሽ ሲሏት” የምንላትን ሴትዮ ሆንክብኝ! የፖለቲካ ፓርቲ መሪ ሆኖ የአገሩን የፖለቲካ ሁኔታ የማይተነትንና መጻኢዉን እዉነት በስዕል ቀርጾ የማያሳየን ከሆነ ምኑን የፖለቲካ ፓርቲ መሪ ሆነ . . .  እንደሱ አይነት የፖለቲካ ፓርቲ መሪማ ካንተ ጋር የዋለ ሰዉ ማለት ነዉ። አይዞህ ተረት ጎበዝ ነህ ብዬ ነዉ (ከአህያ ጋር የዋለች . . . )  አቦይ ተክሌ ችኩልነትህን ድሮም አዉቀዋለሁ፤ ከተናገርክ በኋላ የምታስብ ሰዉ መሆንህም ለእኔ አዲስ አይደለም፤  ግን ምነዉ ተክሌ . . .  ያንተ እዉነት የሰዉ ሁሉ እዉነት ይመስልሃል እንዴ? እንደዚህማ ከሆነ እዉነት የሚባል ነገር ምድር ላይ የለም ማለት ነዉኮ!  ተክሌ እባክህ በዚህ “ካፍ ከወጣ አፋፍ” በሆነበት አለም ከመናገርህና ከመጻፍህ በፊት አስብ። ፈረንጆቹ (Think twice before you speak once) ይላሉ። ተክሌ አንተ ግን የሚጽፈዉ እጀህ ደራሽ የሚናገረዉ አፍህ ነካሽ ነዉና እባክህ እንዳዉ በዚያች በምታከብራት በወላዲት አምላክ ይዤሃለሁ ከመናገርህ  በፊት አምስቴ አስብ (Think five times before you speak once).

 

መቼም የኛ ነገር “አፍ ያለዉ ጤፍ ይቆላል” ነዉና አንድ ሰሞን ይችኑ የምትንጣጣዉን አፍህን አይተዉ  ኢሳቶች ወያኔ ላይ ብትንጣጣላቸዉ ብለዉ አስጠጉህ አንተ ግን ጠላትና ወዳጅ ሳትለይ ሁሉም ላይ የምትተኩስ ጉድ ነህና ኢሳቶች ላይ እሳት ሆንክባቸዉና እሳት አደጋ ጠርተዉ በግዜ ተገላገሉህ። ተክሌ ልክ እንደ ቁመትህ ምን ያህል ትንሽ ሰዉ እንደሆንክ ያየሁት በስራ አጋጣሚ የምታዉቀዉን ነገር ሁሉ ድረ ገጽ ላይ እንዳላዋቂ ሳሚ መለቅለቅህ ነዉ። አሁን ይህ ምን ይባላል? አዋቂነት ወይስ ጅልነት? መልሱ ቀላል ነዉ፤ ተክሌ አንተ አዋቂነት የሚባል ነገር በአጠገብህ ያለፈም አይመስለኝም። ጅልን ለማወቅ ደሞ ጅል መሆን የግድ ይላልና እስኪ እዚያ የሞነጫጨርከዉ መጣጥፍ ላይ የከተብከዉን ዝባዝንኬ እንዳለ ላሳይህ

 

“ይሁን እንጂ፤ የኢሳት አስተዳዳር የሆነው ወዳጄ ነአምን ዘለቀ የዛሬ አመት አካባቢ እንዲህ ያለው ተመሳሳይ ስብሰባ ሲዘጋጅ፤እባክህን መሪዎቹ ንግግር ያሳጥሩና ለሰዉ እንዲተነፍስ ግዜ ይስጡት ብዬ አሳስቤው ነበር። ነአምን አንዳንዴ አይሰማም። ወይም ቢሰማም አያደምጥም” አቦይ ተክሌ

 

“ነአምን አንዳንዴ አይሰማም። ወይም ቢሰማም አያደምጥም” . . . ወይ ጉድ! አንተንስ ምን እንበል? . . .  ተክሌ የሚባል ስም ከተሸከምክ ጀምሮ ሰምተህም አዳምጠህም የማታዉቀዉን ጆሮም አፍም የሌለህ እንግዳ ፍጥረት! ለካስ አለምክንያት መዶሻ አልተባልክም!  ነአምንማ እንተም እንደመሰከርክለት አንዳንዴ ነዉ እንጂ አብዛኛዉን ግዜ ይሰማልኮ፤ እንደዚህ ብዙ ግዜ የሚሰሙ ኢትዮጵያዉያን ደግሞ ብርቅዬ ናቸዉ . . . የሉማ! እስኪ ንገረኝ ተክሌ ምንድነዉ እየነገርከን ያለኸዉ፤ አንተ ሁሉን ነገር  አዋቂዉ ተናግረህ ነአምን አላዋቂዉ አለመስማቱን ነዉ ወይስ ከዚህ ሌላ የምትለን ነገር አለ? ደሞኮ ከብዙ ጉድ ያዳነን የነአምን አንዳንዴ አለመስማት ነዉ እንጂ ሰምቶህማ ቢሆን ኖሮ የዛሬዉ ትግላችን ከወያኔ ጋር መሆኑ ቀርቶ አንተ የቀደድከዉን ቀዳዳ መቋጠር ላይ ይሆን ነበር። ችግሩ ዲሲ ላይ አትቅደድ ብለዉ ሲያባርሩህ ቶሮንቶ ሄደህ ደሞ እንደገና ትቀድዳለህ . . .እስኪ ንገረን የሚቀደድ የሌለበት ዬት አገር እንስደድህ?

 

አቦይ ተክሌ  . . . ዶ/ር ብርሐኑ በሐይማኖት ጉዳዮች ላይ የጻፉት ሰፋ ያለ ጽሁፍ አልገባህ እንደሆነ መጠየቅ አንድ ነገር ነዉ፤ አለዚያ ስምም፤ሀሳብም ጸባይም  እንደምትጋራቸዉ እንደ አቦይ ስብሐት ህዝብ አንዳለ ባኮረፈበት አገር “ያኮረፉ ሰዎች እንጂ ያኮረፈ ህዝብ የለም” ብትል አባባሉ ለግዜዉ ሊያምርልህ ይችል ይሆናል፤ እመነኝ የሚሰማህ ግን አታገኝም። የዶ/ር ብርሀኑ ጽሁፍ ላይ ገጽ 16 መጨረሻና ገጽ 17 መጀመሪያ ላይ የቀረበዉ ሃሳብ ጥልቅ ወይም ሐቀኛ አይደለም ብለሃል። እስኪ ንገረኝ ተክሌ ምንድነዉ መለኪያህ? ጥልቀቱን ባንተ ስንዝር ሐቀኝነቱን ባንተ ሚዛን ነዉ የለካኸዉ? ከሆነ… አብረን ስለኖርን ዝንዝርህንም ሐቅህንም በሚገባ አዉቃለሁና አልፈርድብህም። አቦይ ተክሌ እንዳዉ ያንተ ነገር “አህያ ማር አይጥማት” ሆኖብህ ነዉ እንጂ እስኪ አሁን ምኑ ላይ ነዉ ያ ጽሁፍ ጥልቀት ያጣዉ ምኑስ ላይ ነዉ ሀቅ የጎደለዉ? አንድን ሰዉ ደደብ ነዉ ብሎ አንድ ሙሉ መጽሐፍ መጻፍ ይቻላልኮ፤ ለዚህ ደግሞ የሚያስፈልገዉ ብዙ ጥረትም አይደለም አንድ ያንተ አይነት ጭንቅላት ይበቃል። ችግሩ የሚመጠዉ የሰዉየዉን ደደብነት ዋቢ ጠቅሶና መረጃ አስይዞ ማቅረቡ ላይ ነዉ፤ እንደዚህ አይነቱ መረጃ ደግሞ እንኳን አንተ አያገባዉ ይገባል ያልከዉ ሰዉ ላይ ቀርቶ የእርጎ ዝንብ የሆንከዉ አንተ ላይም ማቅረብ አስቸጋሪ ነዉ። አይህ ወንድሜ ተክሌ አንተም እንደዚሁ ነህ። ሰዉን “ደደብ” ለማለት አፍህ ይቀድማል መረጃ ተብለህ ስትጠየቅ የምታሳየን ግን ያንኑ የምናዉቀዉን ባዶነትህን ነዉ . . .እሱ ደግሞ ሰለቸን . . .  አዎ ሰለቸን! ሰማህ ተክሌ ሰለቸን።

 

አቦይ ተክሌ ደሞ ብለህ ብለህ አንተም እንደ ወያኔ ምሁራን ተቃዋሚዉን ሁሉ “ሊብራል” ልትለዉ ነዉ እንዴ! መቼም አንዳንዴ ነካ ሲያደርግህ እንደ ዕብድም መሆንም ያምርሃል እንጂ በወያኔነት እንኳን በፍጹም የምትታማ ሰዉ አይደለህም፤  ግን . . . ግን ጠንቀቅ በል ልጄ ዉኃኮ ሲወስድ እያሳሳቀ ነዉ . ..  እንግዲህ ይታይህ ተክሌ ባንተ መንቀዥቀዥኮ መወሰድህ ነዉ!  ብሉይን በመቀበል ከዚያ ክርስትናን፤ ከዚያ እስልምናን፤ ከዚያ ካቶሊክን፤ ከዚያ ፕሮቴስታነንስዝምን፤ በመቀበልና በማቻቻል የኖረች አገር ናት ብለሀል አገራችን ኢትዮጵያን። እርግጥ ነዉ፤ ግን ለመሆኑ ብሉይ የሚባል ሐይማኖት አለ አንዴ ወይስ አንተዉ ወደኋላ ሄደህ ልትጀምር ነዉ? ደግሞስ ክርስትና፤ ካቶሊክና  ፕሮቴስታነንስዝም ስትል ካቶሊክና ፕሮቴስታንት ምን መሆናቸዉ ነዉ? ክርስትና አይደሉም እንዴ? ወይስ ኢትዮጵያ ዉስጥ ከምንም ተቋም ጋር የማይገናኝ “ክርስትና” የሚባል ሐይማኖት አለ? አየህ ተክሌ ምን አይነት የተበላሸ ጭንቅላት እንዳለህ የሚያሳየዉ እንደዚህ አይነት ቆሻሻና ወደ አንድ ወገን ያጋደለ ትንተናህ ነዉ። ይልቅ ምነዉ እንዲህ አይነቱን ጭንቅላት የሚፈልገዉን ትንተና ለዚያ አትችልም ላልከዉ ሰዉ ብትተዉለት! ማቻቻል የሚል ቃልም ተናግረሃል፤ ምን ማለትህ ነዉ? ኢትዮጵያ ዉስጥኮ ማን ማንን ችሎ እንደኖረ ግልጽ ነዉ . . .  እና አሁንም በዚያዉ እንቀጥል ነዉ እንዴ የምትለን? ዶ/ር ብርሀኑኮ በዚያ ጸሁፉ ዉስጥ ያስነበበን የተለያየ ሐይማኖት ቢኖረንም እንዴት ሁላችንም ያሰኘንን ሐይማኖት ባሰኘን መንገድ እያመለክን (ይግባህ መቻቻል አይደለም) በእኩልነት ተከባብረን መኖር እንደምንችል ነዉ። ይህንን ደግሞ ሊብራል ዲሞክራሲ በሚገባ ተንትኖ አስቀምጦታል። አየህ ተክሌ  ፖለቲካ ተንትን ተብሎ ስራ ሲሰጥህ አንደጋይኮ ኮሜርሻል ነገር ትደባልቃለህ፤ አዋቂ ሲተነትን ደሞ አትተንትን ብለህ ትወርድበታለህ፤ ምነዉ ተክሌ . . .  “ያግቡብሽ እምቢ ያዉጡብሽ እምቢ” ሆንክሳ!

 

ኦባማ ሲመረጥ ምሁር ነበር ብለሃል. . . . አይደለም ብዬ ብከራከርህስ?  ምነዉ ተክሌ የማታዉቀዉ ዉስጥ ገብተህ ትፈተፍታለህ! አባማ ፕሬዚዳንት ሆኖ ሲመረጥ የፖለቲካ ሰዉ (ሴኔት) ነበር፤ ዛሬም የፖለቲካ ሰዉ ነዉ። በእርግጥ ኦባማ የምሁር ችሎታዉም ተሰጥኦዉም አለዉ፤ ግን በምሁርነት የሚበልጡት ሺዎች አሉ፤ ኦባማን አባማ ያሰኘዉ በምሁርነት ችሎታዉ ላይ አዳብሎ የያዘዉ ከፍተኛ የፖለቲካ ችሎታዉ ነዉ (ይህ ችሎታ የፖለቲካ ትንተናዉንም ያጠቃልላል)። አለዚያ ለምሁርነቱማ ሀርቨርድና ፕሪንስተን ዉስጥ አባማን የሚያስከነዱ ብዙ ምሁራን አሉኮ። ተክሌ አንተኮ አንዳንዴ የምትናገረዉንም የምታዉቅ አይመስለኝም፤ ለዚህ ይመስለኛል ‘ተክሌ’ ከተናገረ በኋላ ነዉ የሚያስበዉ እየተባልክ የምትታማዉ። ምሁር ምሁርነቱ ሲቀንስ ወደ “ቡሽነት” ይለወጣል ነዉኮ ያልከዉ? የፈጣሪ ያለህ!  . . .  ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም አሉ፤ ዕድሜ ላንተ ዘንድሮ ሊጣባ ነዉ። አየህ ተክሌ በዚህ አንተ ባልከዉ ስሌት ከሄድንኮ ኢሳት ዉስጥ ዜና ያነበበ ሰዉ ሁሉ ወናፍነቱ ሲጨምር ‘ተክሌ’ ይሆናል ማለት ነዉኮ . . .  እንዴ! እኛ አነተ አንዱም አላስቀምጥ ብለኸናል ደሞ ስንት ተክሌ ሊኖረን ነዉ?  ከዚህስ ቸሩ ፈጣሪ ይጠብቀን!!

 

“የፖለቲካ ተንታኝ የምለው፤ በፖለቲካ ውስጥ በቀጥታ በአድራጊ-ፈጣሪነት ሳይሳተፍ ወይም መሳተፍ ሳይጠበቅበት፤ የአንድን ፖለቲካዊ ስብስብ/ማህበረሰብ ፖለቲካዊ ሁኔታ እየቃኝ፤ ከአካባቢያዊና አለማቀፋዊ ሁነቶች ጋር እያጣቀሰ የሚናገር ነዉ” ብለሀል። ለመሆኑ ይህ የተናገርከዉ ነገር ያንተ ህግ ነዉ ወይስ የሁላችንም?  ያንተ ከሆነ ያንተ ነገር ሁሉም ግራ የተጋባ ነዉና አልፌሃለሁ። ግን ምነዉ ተክሌ ሰሜን አሜሪካ ዉስጥ እየኖርክ ፖለቲካ በምሁርና በፖለቲከኛዉ ሲተነተን ልዩነቱ አልገባህ አለ? እስኪ የሚገባህ ከሆነ ምሳሌ ልስጥህ . . .  ፕሮፌሰር ላሪ ሰባቶ (ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቨርጂኒያ) አንተ ያልከዉ አይነት የታወቀ ምሁርና ፖለቲካ ተንታኝ ነዉ፤ ግን ፖለቲካ አድራጊም፤ፈጣሪም አይደለም ። ተሳትፊ ግን ነዉ። አንተ ከዬት እንዳመጣኸዉ አላዉቅም አንጂ  ሰዉ ሆኖ ፖለቲካ  ላይ የማይሳተፍ የለም፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ  ፖለቲካ አድራጊም፤ፈጣሪም  ተሳታፊም ናቸዉ፤ ዋናዉ ስራቸዉ  ፖለቲካ መተንተን ላይሆን ይችላል፤ ግን አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ የአሜሪካንን ፖለቲካ ተንትነዉ ለህዝብ ማቅረብ ግዴታቸዉ ነዉ።  ህዝቡም ጆሮዉን በአብዛኛዉ የሚሰጠዉ ለፖለቲካ ኤክስፐርቱ ለላሪ ሰባቶ ሳይሆን ለፖለቲከኛዉ ለኦባማ ነዉ። አየህ ተክሌ ባንተ አባባል ፕሬዚዳንት ኦባማ ፖለቲካ ትንተናዉን ለላሪ ሰባቶ መተዉ አለባቸዉ ማለት ነዉ፤ ወይም የኦባማ ፖለቲካ ትንታኔ ያልጠራ የላሪ ሰባቶ ትንታኔ ግን የጠራ ነዉ ማለት ነዉ . . . እንዴት ሆኖ!  እርገጠኛ ነኝ ይህንን ጽሁፍ አንብበህ ስትጨርስ በራስህ ቅዠት ይምትስቅ ይመስለኛል። በነገራችን ላይ የኢትዮጵያም ፖለቲካ እንደዚሁ ነዉ፤ ጋዜጠኛዉም፤ የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰሩም፤ ሌላ ሌላዉም ሊተነትነዉ ይችላል፤ ግን ህብረተሰቡ (አንተን ላይጨምር ይችላል- አዋቂ ነሃ!) በብዛት ጆሮዉን የሚሰጠዉ ፖለቲካዉን የፖለቲካ መሪዎች ሲተነትኑት ነዉ። ደሞ ማነዉ ምሁር ሁሉ ፖለቲካ መተንተን ይችላል ብሎ የነገረህ?  አቦይ ተክሌ ሌላዉ ትልቁ ችግርህ ሰዉ ያለማክበር ነቀርሳ አለብህ፤ ለምሳሌ ዶ/ር ብርሀኑን አንዴ ዲባቶ ብርሀኑ ፤ አንዴ ብርሀኑ ነጋ፤ ሌላ ግዜ ደግሞ ልክ እንደ ቆሎ ጓደኛህ “ብሬ” ብለህ ጠርተዋኸል። ዶ/ር ብርሀኑ በዕድሜ ይበልጥሃል ደግሞም አስተማሪህ ነዉ፤ ስለዚህ አጠገቡ ስትሆን ዶ/ር ብርሀኑን እንዳሰኘህ መጥራት ትችላህ እሱ ያንተና የሱ ጉዳይ ነዉ፤ ለኛ ስትጽፍልን ግን ኢትዮጵያዊ ባህላችን ነዉና ማክበር ግዴታህ ነዉ። ይህንን ታላቆችህን የመዘርጠጥ ነቀርሳ በግዜ ካልታከምከዉ ብዙ ታዳጊ ልጆቻችንን ታበላሻለህና አንተዉ  ጽሁፍህ ላይ በጠቀስካት በእመ ብርሀን የዤሃለሁ እባከህ ታላቆችህን አክብር።

 

ኢትዮጵያ ዉስጥ ሙስሊም ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ያነሱትን የመብትና የነፃነት ጥያቄ ሙሉ በሙሉ የምንደግፍ ኢትዮጵያዉያን፤ የምንደግፍ ግን ንቅናቀዉን በጥርጣሬ አይን የምንመለከት ኢትዮጵያዉያንና ጭራሽ ንቅንናቄዉን የምንቃወም ኢትዮጵያዉያን አለን። አቦይ ተክሌ አንተም የሙስሊሙን ህብረተሰብ እንቅስቃሴ መጠራጠር መብትህ ነዉ፤ ያ እዚያ ሙንጭርጭርህ ላይ የወረድክበት የፖለቲካ ተንታኝም አትጠራጠሩ አላለምኮ! መቼም ያንተ ዱላ ልክ እንደ ወያኔ ፌዴራል ፖሊስ ዱላ ያገኘዉ ሁሉ ላይ ይመዘዛል እንጂ ዶ/ር ብርሀኑማ እንድያዉም የሙስሊሙን እንቅስቃሴ የሚጠራጠሩ ሰዎችን በመንግስት ፕሮፓጋንዳ የተደለሉና የሐይማኖት አክራሪነትን የሚፈሩ ብሎ በሁለት ከፍሎ ነዉ ያስቀመጣቸዉኮ። አንተ ግን በዚያ በተከፈተ ቁጥር አንደ “ታድፋለች ቅጥ” በሚሰፋዉ አፍህ “ብሬ አድበሰበሰው” ብለህ አረፍከዉ። መቼም በባህላችንም ቢሆን ነዉር ነዉና አደባባይ ላይ “ባለጌ” ብዬስ አልሰድብህም!

 

ምንም ቢሆን ተሰድደህ ዳያስፖራዉን የተቀላቀልከዉ ለትግል ነዉና አስኪ አንድ ነገር ልጠይቅህ . . . . ክርስቲያኑ የሙስሊሙን የመብትና የነፃነት ጥያቄ በጥርጣሬ የጎሪጥ ከተመለከተዉ፤ ሙስሊሙ ደግሞ ይህንን እሱን በጥርጣሬ የሚለከተዉን ክርስቲያን በትግል አጋርነቱ ካላመነዉና ካልተቀበለዉ እንዴት ሆኖ ነዉ የኛ ትግል ግቡን መትቶ አገራችን የምንገባዉ? ይሄዉልህ ተክሌ በዚያ አስቀያሚ የፖሊስ ዱላህ ደጋግመህ የጨረገድከዉ ሰዉ እንዲህ አይነቱን አንተ አይቶ ለመረዳት አመትና ሁለት አመት የሚፈጅብህን ነገር እሱ በግዜ አይቶና ተንትኖ ለህዝብ ያቀረበ ሰዉ ነዉኮ! ምነዉ የልጅነት ገደኛዬ እንዲህ ገብስ ሆንክብኝ ከገብስም የነፈዘዉ! ለመሆኑ ጽሁፉን በደምብ አንብበኸዋል ወይስ ለትችት የሚመችህን ቦታ ብቻ ነዉ እየመረጥክ ያነበብከዉ፤ ለዚያዉምኮ አንተኑ ለትችት የሚያጋልጠዉን ቦታ ነዉ የመረጥከዉ። ለነገሩ አንተ መምረጥ መች ታዉቅበታለህ? ብታዉቅ ኖሮ አንዳቅምህ ትኖር ነበር። ዶ/ር ብርሀኑኮ እንደ ማንም ሰዉ የሚተች ሰዉ ነዉ፤ እንዳዉም እንደሱ ለትችት የተጋለጡ የፖለቲካ መሪዎች በጣት የተቆጠሩ ናቸዉ፤ በየቀኑ እንደሰሩ ነዋ! አንተ ግን ወይ አትሰራ፤ ወይ አታሰራ እንዳዉ “ዝናር በቅፌን” ይመስል መናኛ መናኛዉን ኮተት ተሸክመህ ከሚሰሩ ሰዎች ጋር ትቀላቀላለህ። አሁን እስኪ ተክሌ በሞቴ ንገረኝማ . . .  ተክሌ እንዴት ጎበዝ ነዉ፤ ዶ/ር ብርሀኑን እኮ አገኘዉ፤ ልክ ልኩን ነገረዉ ብለዉ ያንተ ብጤ ጥቅት ወናፎች ቢያናፍሱልህ እዝያ ቁመትህ ላይ ስንዝር ይሚጨምሩልህ ይመስልሃል? ቢጨምሩስ?

 

አየህ አቦይ ተክሌ ጽሁፍኮ ፊደልና ፊደል ማገናኘት ስለምንችል ብቻ የምንገባበት የጨረባ ተዝካር አይደለም። መጻፍ ማሰብ፤ ማሰላሰል፤ ማንበብና ነገሮችን የማመዛዘን ችሎታን የሚጠይቅ ትልቅ ስራ ነዉ፤ አንተ ደሞ ነገሮችን መቀላቀል ነዉ እንጂ ከእነዚህ እሴቶች ጋር በተለይ ከማሰብና ከማመዛዘን ጋር ጭራሽ የምትተዋወቅም አይመስለኝም። እዩኝ እዩኝ ትላለህ፤ አወቅኩ አወቅኩ ታበዛለህ። አንዳንዴማ ጭራሽ ካንተ በላይ የሚያዉቅ ሰዉ ያለም አይመስልህም። የሰዉ ልጅ የማዉቁ ትልቁ ምልክት አለማወቁን ማወቁ ነዉ። ኦይ ተክሌ ላንተ ግን ይህ የጠቢባን አባባል ተረት ነዉ የሚመስልህ። እባክህ የማታዉቀዉን ነገር አላዉቅም በል። በተለይ በተለይ የማተዉቀዉ ነገር ላይና በደምብ ያልገባህ ነገር ላይ አትጻፍ፤ አትተች አስተያየትም አትስጥ። ዉድ ጓደኛዬ ተክሌ አንግዲህ አንድም ገና የምታድግ ሰዉ ነህና ደሞም ሰዉ እፈር ተብሎ የሚነገረዉ ዉድቀቱን ሲረዳ ስለሆነ “እፈር “ ብዬህ አፌን አላበላሽም። እስከዛሬ እንዳየሁህ አንተም እንጣጥ እንጣጥ ማለት ነዉ እንጂ እፍረት የሚሰማህ ሰዉ አይደለህም። እንጣጥ የሚያበዛ ሰዉ ደግሞ ያመለጠዉ ለታ ዕድሜ ልኩን ያፍራል። እንግዲህ ይህ መጥፎ ቀን ሳይመጣብህ ከአቅምህ በላይ መዝለሉን አቁም። እርግጠኛ ነኝ ተክሌ ይህንን ጽሁፍ አንብበህ “ዲሞክራሲ” የማይገባቸዉ ሰዎች ሀሳቤን የመግለጽ መብቴን ሊቀሙኝ ነዉ እንደምትል፤ ሆኖም የዚህ ጽሁፍ ጥረት የዲሞክራሲ ጽንሰ ሀሳብ አንዲገባህና ከሰዎች ጋር በቡድን ስትሰራ ሌሎችን ሳትጋፋና ሳታስቀይም ሀላፊነት ተሰምቶህ ግዴታህን እንድትወጣ ነዉ እንጂ የሁላችንም ትግል ለመብት መከበር ነዉና መብትህን የነካም የደፈረም የለም። የፖለቲካ መሪዎቻችንን መተችትና ስህተት ሲሰሩ ተከታትሎ ማጋለጥ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነገር ነዉ፤ ነገር ግን የሌለ ስህተት እየፈጠርክ፤ ያልተጻፈ  እያነበብክና ሰዎች ደፋር ተቺ ነዉ እንዲሉህ ብቻ የሚሰሩ ሰዎችን ባትቦጫጭቅ ጥሩ ይመስለኛል። አንድ ሰዉ ባጠፋዉ ጥፋት የሚያዝነዉ ለሌሎች ካለዉ ክብርና ፍቅር ነዉና . . .  ተክሌ እስኪ እባክህ ለህዝብ ክብር ስትል ጥፋትህን ተረዳና ከራስህም ከወገንም ጋር ታረቅ። የምትመኘዉን ትልቅ ሰዉ ለመሆን ከፈለግክ የትልቅነት መንገዱ ይህ ነዉ። እግዜር ይርዳህ!


እንኳን ለአዲሱ ዓመት አደረሰህ! –ከፕ/ር መስፍን ወልደ-ማርያም

$
0
0

Pro Mesfinየሰሞኑ መልካም ምኞች የሚመስል ስሜት የምንለዋወጠው “እንኳን አደረሰሽ (አደረሰህ)” በመባባል ነው። ከየት ተነስተን ወዴት እንደደረስን ግን አናውቅም። ምኞቱ የሚገልጸው ሁላችንም በአንድነት ወደተሻለ ደረጃ መሸጋገራችንን ይመስላል፤ እውነቱ ግን ሁላችንም በአንድነት ቁልቁል ወርደናል።
“… ጋሼ ማረኝ ማረኝ፤ ጋሼ ማረኝ ማረኝ
ዶሮ ብር አወጣች እኔን ሥጋ አማረኝ! …”
ተብሎ የተዘፈነበት ጊዜ መቶ ዓመት ሊሆነው ነው፤ ዛሬ እኛ ምን ብለን ልንዘፍን ይቃጣናል?
ለእኔ “ያለምንም ደም” የሚለው የደርግ መዝሙር ተስማሚ ሆኖልኛል። አንድ ዶሮ 200 ብር፣ አንድ ኪሎ ቅቤ 150 ብር፣ አንድ ኪሎ ሽንኩርት 15 ብር፣ አንድ እንጀራ 4 ብር ተኩል፣ አንድ እንቁላል 2 ከሃምሳ ሲሆን፣ የማገዶውንና የውሀውን ትተን (ውሀ ከዘይት መወዳደር ጀምሮአል፤ በአንድ ዓመት ያህል ጊዜ ውስጥ ወደ ሁለት ሺህ ስድስት መቶ ብር ግድም ከፍያለሁ!) አንድ ድስት የዶሮ ወጥ ምን ያህል ሊያወጣ ነው እንግዲህ እንኳን አደረሳችሁ ማለት መልካም ምኞት ነው ወይስ እርግማን? ብዙ ሰው ከ2005 ወደ 2006 የተላለፈው “ያለምንም ደም” ውሀውም ተወዶበት ነው። ለመሆኑ ለሚሌኒየም ግርግርና ከበሮ ምን ያህል ገንዘብ ወጥቶ ይሆን? ቂል አትበሉኝና የወጣው ገንዘብ ለእያንዳንዱ ገበሬ ለዓመት በዓሉ ሃምሳ ብር ቢታደል የሚያስፈልገው ወጪ 500,000,000 ብር ብቻ ነው። ጥድቁቀርቶ ሆነና …
የደላቸው ሰዎች በምድረ ኢትዮጵያ የሉም ማለት አይለም። እነሱ አዲሱን ዓመት ሲቀበሉ ግቢያቸውን ደም በደም አርጥበውታል፤ የዶሮውንም፣ የበጉንም፣ የፍየሉንም፣ የሰንጋውንም ደም ደሀው አላየም። ሀብታሞቹ ለርኩሳን መንፈሶች ገብረውልን የምሳቸውን ሰጥተው ባይገላግሉን በቅዥት እናልቅ ነበር! ሀብታሞች ርኩሳን መንፈሶችን መክተውልናል። ለአዲስ ዓመት ትልቁ ነገር ደም ማፍሰሱ ነው እንጂ ሥጋ መብላቱ አይደለም። ማን ነበር …
“… እኔ ስበላ አይተህ ደስ ይበልህ እንጂ
ያንተ መከጀልስ ለምንም አይበጅ፤ …” ያለው?
ዛሬ መከጀልም ቅንጦት እየሆነ ነው። “ደሀ በሕልሙ ቅቤ ባይጠጣ” ይባል ነበር – ዱሮ። ዛሬ ሕልም ማለም ቀርቷል፤ ዛሬ ሕልሙ ወደቅዠት ተለውጦአል። የዘንድሮው ቅዠት ክፋቱ እስቲተኙ አይጠብቅም፤ የሚያስለፈልፈው ደሀውን ብቻም አይደለም፤ በእውንም በጥጋብም ያቃዣል። ኢኮኖሚው እያደገ ነው፤ የህዝቡ ኑሮ እየተሻሻለ ነው እያሉ በጠኔ ለሚሰቃዩት መንገር ቅዠት አይደለም?
እኔ ከልጅነቴ ጀምሮ ለዕንቁጣጣሽ ዶሮ ማረድ ያልቻለ ደሀ አይቼ አላውቅም። በሠፈሬ የተካንሁት እኔ ብቻ ስለነበርሁ፣ ለዶሮ አራጅነት በየቤቱ እጠራ ነበርና በደንብ አውቃለሁ። ደሀው የሚቸገረው የዶሮውን መልክ መረጣ ላይ ነበር። ገብስማ፣ ጥቁር፣ ወይም ዛጎልማ ወይም ሌላ ነበር ትልቁ ችግር። ዛሬ ችግሩ ሌላ ሆነ፤ ዕንቁጣጣሽን የምንቀበለው ያለ ምንም ደም ሆነ።
ሃያኛውን ምዕተ-ዓመት ስንቀበል ደሀው ዶሮ ማረድ ይቻል እንደነበረ አትጠራጠሩ። ሃያ አንደኛውን ምዕተ-ዓመት ስንቀበል ዶሮ ማረድ ያለመቻላችን ዕድገት መሆኑ ነው? የመቶ ዓመት ዕድገት ለዕንቁጣጣሽ ዶሮ ማጣት!
ደሀነትን ማጥፋት ሲባል ግራ ይገባኝ ነበር፤ ለካስ ያውም ከተገኘ በአምስት ብር ደረቅ ሽሮ፣ የሦስት ብር እንጀራ ለእንቁጣጣሽ መብላት ነው! ማን ነው ይህንን ለደሀው የመረጠለት? ደሀነቱ እንኳን ደሀውን እኔንም ክፉኛ ተሰማኝ። ለዶሮ መግዣ እያልሁ ለዓመት በዓል ትንሽ ገንዘብ የምሰጣቸው ሰዎች ነበሩ። በአቅሜ ያስለመድኋቸው ገንዘብ ዛሬ የዶሮዋን አንድ ክንፍ አይገዛም። ታዲያ እኔ አልደኸየሁም? ዱሮ ለዶሮም፣ ለቅቤም የምሰጠው ዛሬ ለዶሮ ብቻ የሚበቃ ሲሆን አልደኸየሁም?
ተያይዘን ነው እየደኸየን ያለነው፤ በደርግ ዘመን አንድ ሰሞን የአምቦ ውሀና ክብሪት ጠፋና ህዝብ ተንጫጫ። በራዲዮና በቴሌቪዥን የተሰጠው መልስ አድኃርያን ለውስኪ መበረዣና፣ ለሲጃራ ማቀጣጠያ ቢቸግራቸው ሰማይ የተደፋባቸው መሰላቸው የሚል ነበር። ራዲዮኑንና ቴሌቭዥኑን ሲቆጣጠሩት ማሰብ ይቸግራል መሰለኝ።
እንዲያውም ሌላ ሃሳብ መጣብኝ። አድባሮቹ፣ ቆሌዎቹ፣ ምናምንቴዎቹ የሰው ደም ለምደው እንዳይሆን፤ ያለ ምንም ደም የሰውንም ደም ጨምሮ ከሆነ በዚሁ ይለፍልን፤ ሌላ ምን እንላለን።

የሐምሌ ጨረቃ! (ክፍል አንድ) –ከአንዱዓለም አራጌ ዋለ (አንድነት ም/ሊቀመንበር ከቃሊቲ ማጎሪያ)

$
0
0

የሐምሌ ጨረቃ!

ከአንዱዓለም አራጌ ዋለ (አንድነት ም/ሊቀመንበር ከቃሊቲ ማጎሪያ)

ክፍል አንድ

(ሊያነቡት የሚገባ)

andu_udj

ከጉልበተኞች ጠመንጃ የሚወጣ ጥይት ስጋን እንጂ እምነትን ሊገድል እንደማይችለው ሁሉ፣ ከቤተሰብና ወዳጅ ዘመድ ተነጥሎ ቅዝቃዜ በዋጠው ጠባብ ክፍል ውስጥ መታሰርም አካልን እንጂ ምናብን (ህልምን) ሊያስር የሚችልበት ጉልበት የለውም፡፡ ከቶስ እንደምናብ ሜዳውን፣ ተራራውን፣ ቁልቁለቱን፣ ዳገቱን፣ ሸለቆውን፣ ኮረብታውን በሰከንድ ክፍልፋዮች ከብርሃን ፈጥኖ በመምዘግዘግ ያለመዛነፍ ያሰበበት የሚደርስ ምን ኃይል አለ? ከጠባቧ ክፍል ውስጥ ‹‹ድርሻህ›› ተብላ በተሰጠችኝ 90 ሴንቲ ሜትር ላይ ቀሪ ህይወቴን አሳልፍ ዘንድ በግፍ ፍርድ ብታሰርም ዕረፍት ለማያውቀው ምናቤ ገለታ ይድረሰውና ይዞኝ ይከንፋል፤ ወደ ምፈልገው አድርሶ ይመልሰኛል፡፡

አንዳንዴ ከጁፒተር ማዶ ያሉ ተንሳፋፊ ዓለማቶችን ቢያስቃኘኝም፣ አብዛኛውን ጊዜ ግን በሀገሬ ሰማይ ስር በጥቅጥቅ ደመና ላይ አንሳፎ ታላላቅ ወንዞቿን፣ ሃይቆቿን፣ የተንጣለሉ መስኮቿንና ሰማይ ጥግ የሚደርሱ ተራሮቿን በመንፈስ ያስጐበኘኛል፡፡ በተራሮቿ ግርጌና በመስኮቿ እምብርት ላይ ችምችም ብለው የተሰሩ ጐጆ ቤቶችንና በውስጣቸው ለሺ ዓመታት በፍቅር የኖሩ ደሃ ኢትዮጵያውያንን እንደጓደኞቻቸው ከሚመለከቷቸው የቤት እንስሳቶቻቸው ጋ ይታዩኛል፡፡ በየከተሞቹ ከድህነትና ከአፈና ጋር ግብግብ የገጠሙ፣ ከድህነትና ከፖለቲካ አፈና ነፃ ለማውጣት በዓለም ዙሪያ የተበተኑ ወገኖቼን ሳይቀር በአይነ- ህሊና ያስጎበኘኛል፡፡ አንዳንዴ ውሸትን እንደብልህነት፣ አፈናን እንደ አገዛዝ ስልት የወሰዱ አሳሪ ወንድሞቼና እህቶቼ የህሊና ጓዳ ውስጥ ይዞኝ ዘው ይልና ያረበበውን እብሪት፣ ፍርሃት፣ ጭንቀት፣ እርስ በእርስ የሚላተሙ ሃሳቦቻቸውን ፍልሚያ… ያሳየኛል፡፡

እነዚህ ምን አይነት ኢትዮጵያውያን? ምን አይነትስ ወላጆች ናቸው? ብዬ ራሴን እጠይቃለሁ፡፡ የምናብ ፈረስ ጋልቤ የምጐበኘው የዚህን ዘመን ክንዋኔ ብቻ ሳይሆን የተደራረበውን የዘመን ጉም እየጠራረጉ ያለፉ አያሌ ዘመናትን ወደ ኋላ አስጉዞ ያሳየኛል፡፡ የኢትዮጵያን የከፍታ ዘመናት፡- አክሱምን፣ ላሊበላን፣ ጐንደርን፣ ያልዘመርንለትን የገዳ ዴሞክራሲ ስርዓትንና ሌሎች የጥንት ስልጣኔዎችን በብላሽ ያስኮመኩመኛል፡፡ የኢትዮጵያን የዳር ድንበር ነፃነት ለማስከበር አባቶቻችን ያደረጓቸውን የጀግንነት ውሎዎች በተለይም የጀግንነታችን ማማና የጥቁር ህዝብ ሁሉ ኩራት የሆነውን የአድዋን ጦርነት ደጋግሜ አየዋለሁ፡፡ አድዋና መሰል የጀግንነት ማማዎች ላይ ቆሜ ኢትዮጵያውያን በየቀያቸውና በየዘመኑ ሰብዓዊ ክብራቸው ተረግጦ፣ በጭቆና አዘቅት ውስጥ ወድቀው ሲዘቅጡ ይታዩኛል፡፡ አንዳንዴ ኢትዮጵያውያን ሰብዓዊ ልዕልናቸውንና ነፃነታቸውን ለመጐናፀፍ ያደረጉትን ትግል ያሳየኝና መንፈሴን ያበረታዋል፡፡

ታሪክ እንደሚዘክረው ከኋላ ቀሩ የፊውዳል አገዛዝ ነፃ ለመውጣት (በትክክል ወዴት ያመራ እንደነበር መናገር ባይቻልም) የመጀመሪያ አብሪ ጥይት የተተኮሰችው የ1953ቱ የእነ ጄኔራል መንግስቱና ገርማሜ ንዋይን የመፈንቅለ-መንግስት ሙከራ በተደረገበት ዕለት ነው፤ አቤት! እርሱን ተከትሎ የተሻለ ንቃት ያለው ኢትዮጵያዊ በሙሉ ‹‹ሕዝባዊ መንግስት›› ለመመስረት ያሳየው እንቅስቃሴ! የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ለዓመታት የሞቱለት፣ የተጋዙለት፣ የተደበደቡለት፣ የተሰደዱለት… ሰላማዊ ትግል እና ያነሷቸው ጥያቄዎች ጆሮዬ ላይ ደጋግመው አስተጋብተዋል፡፡ በወቅቱ የዘውዳዊ ስርዓት ገበሬዎች፣ ተማሪዎች፣ ሰራተኞችና ልዩ ልዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ተቃውሞአቸውን በሰላማዊ መንገድ አሰምተው፣ በሰላም ወደ ቤታቸው እንዲገቡ የነበረውን ትዕግስት አሁን ካለው ሁኔታ ጋር ባነፃፀርኩት ቁጥር እንደ አዲስ እደመምበታለሁ፡፡ ንጉሳዊውን ስርዓት በመቃወም ተደጋጋሚ ሰልፎች ላይ ይሳተፉ የነበሩት እና ዛሬ ለድል የበቁት የቀድሞዎቹ ተማሪዎች፣ የአሁኖቹ ገዥዎች የትምህርት ነፃነትን ከመርገጣቸውም በላይ ቅሬታ በተነሳ ቁጥር የተማሪዎች መኝታ ቤት ድረስ በመዝለቅ ደም ማፍሰሳቸውን ሳስብ፤ ለተቃውሞ አደባባይ የሚወጡ ንፁሃን ላይ ከውሃ ይልቅ ጥይት ማዝነብ የሚቀናቸውና ተቃዋሚዎቻቸውን በውሸት ድሪቶ ዘብጥያ የሚያወርዱ አምባገነኖች መሆናቸውን ሳስብ የማይፈታ እንቆቅልሽ ይሆንብኛል፡፡

ዘውዳዊ ስርዓቱን የተቃወሙ ሰዎች ከነገስታቱ በላይ ከዘመን ጋር የማይዘምኑ፣ ከአፈሙዝ ጋር የተጋቡ እንዴት ሊሆኑ ቻሉ? የሚል ጥያቄ አነሳለሁ፡፡ የምናብ ፈረሴ ኢትዮጵያውያን ወደዚህ ዓለም በመጣሁበት ሰሞን ከነበረው የጭቆና አገዛዝ ነፃ ለመውጣት አልመው ወደ ከፋ የአምባገነንነት ገደል የወደቁበትን የእልቂትና የዋይታ አብዮት እየደጋገመ ያስቃኘኛል፡፡ በተፋላሚዎች መካከል የርዕዮተ-ዓለም ልዩነት ባይኖርም አፈ-ሙዝን በአፈ-ሙዝ ለማሸነፍ የተደረገው ደም መፋሰስና ወንድም በወንድሙ አስከሬን ላይ ቆሞ የፎከረበት የእርስ በርስ ጦርነትም ሌላኛው እረፍት የሚነሳው ጉዳይ ነው፡፡ ህወሓት/ኢህአዴግ የግፍ ቋት የነበረውን ደርግ በኢትዮጵያ ሕዝብ ድጋፍ አሸንፎ በድል አድራጊነት ወደ ምኒሊክ ቤተ-መንግስት ሲገባ ሌላ የግፍ ቋት ይሆናል ብለው ያልጠበቁ አያሌዎች ነበሩ፡፡ ረጅሙ የመከራ ሌሊት መልሶ ላይጨልም ነግቷል ብለው ለተሻለ ነገር የተዘጋጁ ኢትዮጵያውያን ቁጥር ትንሽ የሚባል አልነበረም፡፡ በአሁኑ አገዛዝ ከቀደሙት ህገ-መንግስታት የተሻለ ህገ-መንግስት ቢፀድቅም ቃልና ተግባር ሳይገናኙ ይኸው 22 ዓመታት አልፈዋል፡፡

እነሆም የሌላ ዙር የአፈና ሰለባ ሆኜ ወደምማቅቅበት እስር ቤት የምናቤ ፈረስ መልሶ አደረሰኝ፡፡ ሌላ ዙር እስር፣ ሌላ ዙር አፈና፣ ሌላ ዙር የህፃናት ለቅሶ፣ ሌላ ዙር የወላጆች ሰቆቃ፣ ሌላ ዙር ውርደት፣ ሌላ ዙር የአጤዎች ቀረርቶ፣ ሌላ ዙር የህዝብ እንባ፣ ሌላ ዙር… ባለንበት መርገጥ ቀጥለናል፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ የከበረና ከፍ ያለ መስዋዕትነት በመክፈል የዳር ድንበር ነፃነቱን ማስከበር ቢችልም በአገሩ ሰብዓዊ ክብሩንና ነፃነቱን ከራሱ ገዢዎች አስከብሮ መኖር የቻለበት ዘመን የለም፡፡ አንዴ ሞቅ ሌላ ጊዜ ቀዝቀዝ እያለ የቀጠለው የኢትዮጵያ ህዝብ የነፃነት ትግል በድቅድቁና ዝናባማው የሐምሌ ጨለማ የምትወጣውን ‹‹ጨረቃ›› ይመስላል፡፡ በተለይ የኤሌክትሪክ ብርሃን በሌለበት የገጠሩ የሀገራችን ክፍል የልጅነቱን የመጀመሪያ ዓመታት እንደእኔ ላሳለፈና የኢትዮጵያን የፖለቲካ ትግል በአንክሮ ለተከታተለ ሁሉ ስርዓቱና ጨረቃዋ የአንድ አባት ልጆች ይሆኑበታል፡፡ የሐምሌ ወር ጨለማ ጥቁር ነው፡፡ እንደግድግዳ ፊት ለፊት ቆሞ ነፍስን ያስጨንቃል፡፡ ጫፉ የማይታይ የጥላሸት ቁልል ይመስላል፡፡ ከጨለማው መደቅደቅ የተነሳ በቅርብ እርቀት ያለ ቁስን እንኳን ለመለየት የሚያስችል ብርሃን የለም፡፡ ወደሰማይ ለሚያንጋጥጥም በጥቁር የደመና ከል የተጋረደ ነው፡፡ በዚህ መሃል ግን ህልቆ መሳፍርት ለሌላቸው ዘመናት የሐምሌ ወርን እየጠበቀች እየደጋገመች የምትወጣው ጨረቃም ወቅቷን ጠብቃ መውጣቷን አላቋረጠችም፡፡ ከአንድ ጥቁር የደመና ኮረብታ ወደሌላው ስትወረወር ለቅፅበት ትንሽ ብርሃን ብትፈነጥቅም ምድሩን እንደቡልኮ የሸፈነውን ድቅድቁን ጨለማ ሰንጥቆ ለማለፍ የሚችል የብርሃን ፍንጣቂ በመልቀቅ የጨለማውን ሀይል መግፈፍ የሚችል አቅም የላትም፡፡ እንዲያውም በብርሃን ጅረት የተሞላው መላ አካሏ በጨለማው ፅልመት ጠልሽቶና ከጨለማው ጋር ተመሳስሎ ይታያል፡፡ የሐምሌ ጨረቃ ወይ ድቅድቁን አትገፋ፣ ወይም የሐምሌን ወር አትዘል በየዘመኑ፣ በየአመቱ ፍሬ አልባ ዑደቷን ቀጥላለች፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ትግልም እንዲሁ፡፡ እንደ ሐምሌ ጨረቃ ሁሉ የኢትዮጵያ ሕዝብም የሀገሩን የህላዌ እድሜ ያህል ከጭቆናው ሌሊት ጋር በየወቅቱ ግብግብ ይገጥማል፡፡ በተለይም ከ1953 ዓ.ም ወዲህ ያሉት 50 ዓመታት ህዝባችን ከአብራኩ ከወጡ አምባገነን ገዥዎች መዳፍ ነፃ ለመውጣት ተደጋጋሚ ትግል አድርጓል፡ ፡ አሁንም እያደረገ ነው፡፡ ይሁን እንጂ የሰብዓዊ ልዕልናው ባለቤት ለመሆን የሚያስችለውን የተጠና፣ በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት የሚመራና ህዝብ የራሱ ያደረገው የፀና ሰላማዊ ትግል በማድረግ ለውጤት አልበቃም፡፡

ለምን? በረጅሙ የሀገራችን ታሪክ የሀገርን ዳር ድንበር ማስከበርን የመሳሰሉ ገንቢ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ፣ ፍልስፍናዎች ማዳበር የመቻላችንን ያህል፤ በሌላ መልኩም አሉታዊ የሆኑ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ስነ-ልቦናዊ ፍልስፍናዎች እንዳዳበርን መረዳት ይቻላል፡፡ እነዚህ ሁኔታዎች ፖለቲካዊ መስተጋብራችን የተፋለሰ እንዲሆን አስተዋፆ አድርገዋል፡፡ በተለይም ከዘመነ-መሳፍንት በኋላ ያለውና በዚያ ዘመን የፖለቲካ ብሒል የተቃኘው ፖለቲካዊ ፍልስፍናችን ከምህዋሩ የወጣ ነው፡፡ በአመዛኙ በፍርሃት፣ በአድርባይነትና በጊዜያዊ ጥቅም የተለወሰ ፍርሃት፣ የማያምኑበትን መናገር፣ በአርምሞ ማሳለፍ፣ ያልሆነውን ሁነን መታየት፣ ነገሮችን በሚስጥር መያዝ፣ ተጠራጣሪነትና በውል ባልታሸ ሁኔታ እራስን ማዕከል ያደረገ አስተሳሰብ ማራመድ የመሳሰሉትን ለአብነት ያህል ማንሳት ይቻላል፡፡ በየዘመኑ የሚነሱ አምባገነኖችና የጎበዝ አለቆች ጥላ ስር ለመጠለል መሞከር እነርሱን አይነኬ አድርጐ መቁጠር እራስን ፍፁም አቅመ-ቢስ አድርጐ መረዳት ለገዥዎች ማሸርገድና ቅዳሴ-ማህሌት መቆም አያሌ ኢትዮጵያውያን በየዘመኑ እንደ ፖለቲካ-ጥበብ የሚቆጥሩት አካሄድ ነው፡፡ ይህም ሁሉ በጥልቅ አስተሳሰብና ከዚያም በሚመነጭ እምነት ላይ ቢመሰረት ችግር አልነበረውም፡፡ የተሳሳተ እምነት በማንገብ የጨለማ አገዛዞችን የነፃነት ንጋት ናቸው ብለው የሚዘምሩ፤ በረሃብ ስንሞት በቁንጣን ነው ብለው ሊያሳምኑን የሚዳዳቸው፤ የአገዛዞች ዋልታና ማገር የሆኑ ኢትዮጵያውያንን በየዘመኑ አይተናል፡፡ እያየንም ነው፡፡

ከዘመናት የአፈና አገዛዝ ነፃ ልንወጣ ይገባናል ብለን የምንታገል ወገኖች እንደመኖራችን ሁሉ፤ አገዛዙ የፀሐይ መውጫ ምኩራብ ነው ብለው የሚያምኑ ወገኖች እምነታቸውን ያራምዱ ዘንድ መብታቸው ነው፡፡ ከስሜታዊነት በፀዳ መልኩ ጨለማው በእርግጥም ጨለማ መሆኑን አይኖቻቸውን ገልጠው እንዲያዩና እንዲመለሱ ማድረግ ይገባል፡፡ ሞታችን ከጨለማው ጋር ነው ብለው በጨለማው አካልነታቸው መቀጠል የሚፈልጉ ከሆነ ደግሞ ታግሎ ማሸነፍና እነርሱም ከጨለማ ነፃ እንዲወጡ ማድረግ ነው፡፡ ከባዱ የቤት ስራና እስከአሁንም ነፃነት ከእኛ እንዲርቅ ትልቁን አስተዋፆ እያበረከተ ያለው ከፍተኛ ቁጥር ያለው ‹‹መሃል ሰፋሪው›‹› ኢትዮጵያዊ ይመስለኛል፡፡ እውነቱን ለመናገር በፖለቲካ ትግል ባሳለፍኳቸው ጥቂት ዓመታት ከባዱ ፈተና የገጠመኝ ከቤተሰቤ፣ ከወዳጆቼና ከቅርብ ጓደኞቼ ነው ብል ማጋነን አይሆንም፡፡ እነዚህ ወገኖች ፖለቲካ ውስጥ ገብቼ ከአገዛዙ ጋር ግብግብ ከመግጠም ይልቅ አንገቴን ደፍቼ ልጆቼን እንዳሳድግ ምክራቸውን በተደጋጋሚ ለግሰውኛል፡ ፡ ለነገሩ ትዳር ባልያዝኩበት፣ ልጆች ባልነበሩኝ ወቅትም ‹‹አርፈህ ተቀመጥ!›› የሚለው ምክራቸው አልተለየኝም ነበር፡፡ ትግል ውስጥ እንዳልገባ የሚሰጡኝ ምክንያቶች ሁለት ናቸው፡፡ የሀገራችን ፖለቲካ በደም መፋሰስና በሸፍጥ የተሞላ መሆኑ አንደኛው ሲሆን በተጨማሪም ከኢኮኖሚ አዋጭነት አንፃር ፖለቲካ ፈፅሞ የማይመከር መሆኑን ያስረዱኛል፡፡ በመሆኑም አንገቴን ደፍቼ፣ ገዥዎች ወደአጋዙኝ ተግዤ እንድኖር፤ ልጆቼንም እንዳሳድግ ምክራቸውን ለግሰውኝ ነበር፡፡ አሁን እንኳን በእስር ላይ እያለሁ እንደሳይቤሪያ ብርድ አጥንትን ሰብሮ የሚገባና ነፍስን የሚወጋ ምክራቸውን ይልኩልኛል፡፡ ‹‹ነግረነው አልሰማንም››፣ ‹‹ህፃናት ልጆቹን ያለአባት ትቶ እንዴት ይታሰራል?›› ይላሉ፡፡ አንዳንዶቹ ከመበሳጨታቸው የተነሳ የመጐብኘት መብቴ ቢከበር እንኳን ሊጐበኙኝ እንደማይፈልጉ ይናገራሉ፡፡ ወንጀልሰርቼ እንዳልታሰርኩ፣ ለመስራትም እንደማላስብና ሰላማዊ የትግል ስልትን የሃይማኖት ያህል እንደማምንበት ወዳጆቼም ሆኑ አሳሪዎቼ እኔ የማውቀውን ያህል ያውቃሉ ብል ያጋነንኩ አይመስለኝም፡፡

ያም ሆኖ ግን ወዳጆቼ ስርየት እንደሌለው ሃጢያት፣ የአገዛዙ ዋናዎችም የሰማይስባሪ እንደሚያክል ወንጀል የቆጠሩት የተቃውሞ ፖለቲካ ጐራ መቀላቀሌን፣ በሀገሬ አንገቴን ቀና አድርጌ በመራመዴና የማምንበትን በቀጥታ በመናገሬ ነው፡፡ አገዛዙም ይኽን አይነት በፍርሃት የተሸበበ ማህበረሰብ እንዲፈጠር ይፈልጋል፤ ወዳጆቼም አገዛዙ በግፍ ስላሰረኝ የነቢይነት ደረጃቸውን በመደመምያስባሉ፤ እርስ በእርሳቸው ይመጋገባሉ፡፡ የትችት ጦራቸውን እስር ቤት ድረስ የሚወረውሩት አብዛኞቹ ጓደኞቼ በታላላቅ ዩኒቨርስቲዎች የተማሩና የሚያስተምሩ፣ በመደበኛ ትምህርት ልህቀታቸው በሊቀ- ጠበብትነት ጐራ የሚሰለፉና ይህች ደሀ አገር ከውስን ጥሪቷ ቆንጥራ ያስተማረቻቸው ናቸው፡፡ የሆነ ሆኖ ዛሬ ወዳጆቼ ያሉት ደርሶብኛል፤ ትንቢታቸው ሰምሯል፡፡ አዎ! ልጆቼ በድንገት ከቤት ወጥቶ እስከአሁን ወደቤት ስላልተመለሰው አባታቸው በህፃንነት የአእምሮ ጓዳቸው ውስጥ እያንሰላሰሉና እየተጐዱ መሆኑን በሚገባ እረዳለሁ፡፡ በተለይ ልክ የታሰርኩ እለት የትምህርት ቤትን ደጃፍ የረገጠው የልጄ የሩህ ጥያቄዎች ከዕለት ወደ ዕለት እየበረከቱ መጥተዋል፡፡ ‹‹ማሚ፣ እኔ አባት የለኝም እንዴ?››፣ ‹‹አባባ መቼ ነው ቤት የሚመጣው?››፣ ‹‹የአንተ ስራ መቼ ነው የሚያልቀው?›› የሚሉ ናፍቆት ያንገበገባቸውን ጥያቄዎች ያነሳል፡፡

እኔ የምከፍለው ዋጋ ይቅርና ልጆቼም በውል በማይረዱት ነገር ትልቅ ዋጋ እየከፈሉ መሆኑን በጥሞና እገነዘባለሁ፡፡ ቀድሞውንም ያልጠበኩትም አልነበረም የሆነው፡፡ ግና! በልጆቼ ሰብዕና ላይ የከፋ ስብራት እንዳይደርስ እውነተኛ ፈራጅ ወደሆነው ፈጣሪ ከመፀለይ በቀር ምን ማድረግ ይቻለኛል? ይህችን ምድር ለመጀመሪያ ጊዜ የተቀላቀለው በእስር ቤት ነው፤ ይኸው አሁን ደግሞ ባልጠኑ እግሮቹ፣ ክፉ ደግ ባለየ ህሊናው ከሚያፈቅረው አባቱ ተለይቶ በባዕድ ምድር የፖለቲካ ስደተኛ ሆኖ የሚንከራተተው የናፍቆት እስክንድር ነጋ ህይወት ለዚህ የበቃው አባቱ እንደኔ የወዳጆቹን የአርምሞ ጥያቄ ባለመቀበሉ ጭምር ነው፡፡ አባታቸውን ተመላልሰው መጠየቅ በማይችሉበት እርቀት ላይ የታሰረባቸው የናትናኤል መኮንን ልጆች እንባም ሰብዓዊ ፍጡርን በተለይም የወላጆችን ልብ ምንኛ እንደሚሰብር ግልፅ ነው፡፡ ከሚያስተምርበት አዲሰ አበባ ዩኒቨርስቲ፣ ከግቢ ውጭ እንደሚፈለግ በስልክ ሲነገረው የጠመኔውን ብናኝ ከእጁ ላይ አራግፎ የወጣው የኦሮሞ ፌዴራሊስ ኮንግረስ /ኦፌኮ/ ም/ሊቀመንበር በቀለ ገርባ ‹‹የኦነግ አባልና የፌደራላዊ አገዛዙን በኃይል ማስገንጠል አሲረሀል›› በሚል ክስ ተፈርዶበት ከህፃናት ልጆቹ ተለይቶ በዝዋይ እስር ቤት የግፉን ፅዋ እየተጎነጨ ነው፡፡ በእርግጥ አቶ በቀለም እንደ እኛ አርፎ ልጆቹን እንዲያሳድግ ተነግሮት ነበር፡፡ ሌሎች አያሌ ኢትዮጵያውያንና ልጆቻቸውም ተመሳሳይ የመከራ ህይወት እየገፋ ይገኛሉ፡፡ ልጆቻችንና የትዳር አጋሮቻችን እየከፈሉ ያሉት ዋጋ እኛ በእስር ቤት ከምንከፍለው የከፋ ይመስለኛል፡፡

ለጓደኞቼና ለወዳጆቼ የማነሳላቸው ጥያቄዎች ይኖሩኛል፡፡ ነፃነት አልቦ ህይወት ምን ምን ይላል? ለመሆኑ ነፃነትን በገዥዎች ችሮታ የተጐናፀፈው የየትኛው ሀገር ህዝብ ነው? በየትኛው ክ/ዘመን ይሆን? …አባቶቻችን ዳር ድንበራቸውን ለማስከበር ልጆቻቸውን፣ ሚስቶቻቸውንና ዘመድ አዝማዶቻቸውን ከኋላቸው ጥለው ወደ አድዋ መዝመታቸው ስህተት ነበር እያላችሁን ይሆን? ቴዎድሮስ በመቅደላ፣ ዮሐንስ በመተማ ለሀገር ክብር መውደቃቸው ትርጉም የለሽ ነበር ማለት ነው? ሌሎች አባቶቻችንስ በጉራ፣ በጉንደት፣ በማይጨው እና በአያሌ የጦር አውድማዎች ለሀገር ክብር እንደወጡ ሲቀሩ የሚናፍቋቸው ሚስቶችና የሚሳሱላቸው ህፃናት ልጆች ያልነበሯቸው ይመስሏችኋል? አሉላ አባ ነጋ እስከ እርጅና ዘመኑ ድረስ ለሀገሩ ዳር ድንበር አጥር ሆኖ ጣሊያንና ግብፅን በማስጨነቅ ዛሬ የምንኮፈስበትን ታሪክ ማጐናፀፉ ስህተት ነበር እያላችሁ ይሆን? የእነ በላይ ዘለቀ፣ የእነ አብዲሳ አጋ፣ የእነዘርአይ ደረሰ፣ የእነ ራስ ደስታ ዳምጠው፣ የእነ አቡነ ጴጥሮስና የሌሎችም ስመ-ጥር ጀግኖቻችን ውሎ በከንቱ ጀብደኝነትና ግብታዊነት የተሞላ ነበር ማለት ነው? እነዚህ ጀግኖች የሀገራቸውን ዳር ድንበር ክብር ለማስጠበቅ ከቀያቸው ርቀው ሲጓዙ ሞትን ከፊት ለፊታቸው እያዩት የቆሙለት እውነት አመዝኖባቸው እንደነበር ዘንግታችሁት ይሆን? አባቶቻችን በየተራራውና ኮረብታው ስለሀገር ክብር ባይቀበሩ ኖሮ የዛሬዋን ኢትዮጵያ ማግኘት የምንችል ይመስላችኋል? ወይስ የዳር ድንበር ነፃነት ከተከበረ፣ ዜጐች በጭቆና ቀንበር ቢማቅቁ ምንም ክፋት የለውም እያላችሁ ነው? ወይስ ጭቆና ከአብራካችን በወጡ ሰዎች እስከሆነ ድረስ እንደክብር ይቆጠራል እያላችሁ ነው? የሀገርን ዳር ድንበር ለማስከበር የተከፈለው ዋጋ ጠጋ ብለን ስናየው የህዝብን መሰረታዊ የሉዓላዊነት ጥያቄ እንደሚያነሳ ሳታችሁት? አባቶቻችን ለሀገር ነፃነት የከፈሉት ዋጋ ተገቢ አልነበረም ካላላችሁ በስተቀር ለዜጐች ሉዓላዊነትና ለዕውነተኛ ዴሞክራሲያዊ መንግስት መታገል ስህተት ሆኖ የሚገኘው በምን ቀመር ነው? በዩኒቨርስቲዎች ስለ- ሰብዓዊ ፍጡር ልዕልና የምትማሯቸውና የምታስተምሯቸው ትምህርቶች ‹ነፃነት›ን በተመለከተ ምን ነበር ያሏችሁ? ወይስ ዲሞክራሲና ነፃነት ለእኛ ሀገር አይሰራም እያላችሁ ነው? የጥቁር ህዝብ ኩራት የሆነውን የአድዋን ድል ያስመዘገቡ አባቶች ልጆች ሉዓላዊነታችን ከገዥዎቻችን መዳፍ ነጥቀን ማስከበር ካልቻልን ‹የእሳት ልጅ አመድ› መሆን አይመስላችሁም? ሌላው ቢቀር ኢትዮጵያ የቅኝ ግዛትን ቀንበር እንዲሰብሩ የረዳቻቸው የአፍሪካ አገሮች በዴሞክራሲ ጐዳና በርቀት ጥለውን ሲተሙ፤ የእኛ በጭቆና አረንቋ ውስጥ መዳከር እንዴት ቁጭት አይፈጥርባችሁም? ወይስ የእናንተ ድርሻ ትችትና ታዛቢነት ብቻ ነው? እነዚህ ከፍ ብዬ ያነሳኋቸው ጥያቄዎች ለምወዳቸው ጓደኞቼ ብቻ ሳይሆን ‹‹የመሃል-ሰፋሪነት›› ሚና ለመረጡ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ሁሉ የተሰነዘሩ ናቸው፡፡

ኢትዮጵያውያን በፖለቲካ ባህላችን ውስጥ ያሉ ሸንኮፎችን አስቀድመን መግረዝ ካልቻልን፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ትግል እንደ ሐምሌዋ ጨረቃ አሁንም በከንቱ ብቅ ጥልቅ ከማለት የዘለለ ፋይዳ አይኖረውም፡ ፡ ምናልባት የሀሳባችሁ ማጠንጠኛ ባለፈው ግማሽ ምዕተ-ዓመት ማሳካት ያልተቻለው እንዴት አሁን ይቻላል? የሚል ከሆነ ይኸንን ጥያቄ ማንሳት፣ ለጥያቄውም መልስ መስጠትና በመልሱም ላይ ተመስርቶ በእውነተኛ ነፃነትና ህዝባዊ ልዕልና ላይ የተመሰረተች ኢትዮጵያን ለመፍጠር መታገል እንደሚያስፈልግ መተማመን ላይ መድረስ ይጠበቅብናል፡፡ የተወሰኑ ጥያቄዎችን አክዬ ላንሣ፡ ፡ ሁሉም የግል ጥቅሙንና የአብራኩን ክፋዮች ብቻ በሚያስቡባት ሀገር እንዴት ህዝብ ከአገዛዝ ነፃ ሊሆን ይችላል? በየማጀቱ አገዛዙን በመርገም ነፃ መውጣት ቢቻል ኑሮ ከረጅም ዘመናት በፊት ነፃ አንወጣም ነበር ትላላችሁ? አባቶቻችን ለነፃነት መስዋዕት መሆናቸው ትክክል ነበር የምትሉ ከሆነ የስብዕና መሰረትና የነፃነቶች ሁሉ የበላይ ለሆነው የሰብዓዊ መብት መታገል ትክክል የማይሆንበት አሳማኝ ምክንያት ምንድን ነው? ከገዥዎች መዳፍ ለመውጣት አሳማኝ ምክንያት ምን ሊሆን ይችላል? ይኽን ከገዥዎች መዳፍ ለመውጣት የሚደረግን ትግል እንዳላየን አይተን ብናልፍ ለሁላችንም የማይቀረው ሞትን ተጋፍጠን ወደመቃብር ስንወርድ በምን አይነት ክብርና የህሊና እረፍት ማሸለብ እንችል ይሆን? የዘወትር ህልማችን ሰብዓዊ ልዕልናችን ተጠብቆ የምንኖርበትንና ልጆቻችን የማያፍሩበትን ሀገር ማውረስ ሆኖ ሳለ የአገዛዙን የጭቆና አርጩሜ በመፍራት ከእምነታችን ውጭ የሆኑ ተግባሮችን ስንፈፅም የምንበጀው እስከመቼ ነው? ለዘመናት እላያችን ላይ ቤት የሰራብንን የጭቆና ቀንበር መስበር በረጅሙ የኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ያልተከወነ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲንከባለል የመጣ የቤት ስራ ነው፡፡ በውዝፍ ያደረ ቁምነገር ከቅርሶቻችን ሁሉ የገዘፈና የታሪካችን ፈርጥና የማንነታችንም መደምደሚያ ነው፡፡ በዚህ የሰብዓዊ ልዕልና ጉዳይ ላይ መታገል ሰው የመሆንና ያለመሆንን ጥያቄ መመለስ ነው፡፡ በነፃነት አለመታገል የቤት ስራውን ለልጆቻችን ወዝፎ ማሳደር በጭቆና ቀንበር ለመገዛት ህዝበ ውሳኔ የመስጠት ያህል ይቆጠራል፡፡ በሌላ በኩል ነፃ ለመውጣት እንደቀድሞ ነፃ አውጭ አበጋዞችን መጠበቅ አይገባንም፡፡ ይኽን የምናደርግ ከሆነ ሰማያችን በጭቆና ደመና እንደተሸፈነ ይቀጥላል፡፡ ጥቂቶችን አንጋጠን ስንጠብቅ በውስጣችን ያለውን ትልቅ የነፃነት ሃይል እንዳናይ ግርዶሽ ይሆንብናል፡፡

ይኽን በመሰለው የነፃነት ትግል የሚጀምረው የራስን የከረመና የተሳሳተ ፖለቲካዊና ማህበራዊ አስተሳሰብ ከመሞገት ነው፡፡ ከዚያም ከፍ ሲል እንደ ፖለቲካ ባህልና የብልህነት ቁንጮ በመውሰድ ለህፃናት ልጆቻችን ሳይቀር በምክር መልክ የምንለግሳቸው ልዩ ልዩ ያልተሰለቀቁ አሉታዊ አስተሳሰቦችን በቅድሚያ ታግሎ መጣል ያስፈልጋል፡፡ እያንዳንዱ ስለሁሉም ፤ሁሉም ስለእያንዳንዱ ግድ በማይሰጠው ሀገር ውስጥ አምባገነኖች የሚዘውሯቸው አገዛዞች መኖራቸው የግድ ነው፡፡ በዚህ ዘመን ስለነፃነት ክብርነት ለማንም ማስረዳት እምብዛም አይጠበቅብንም፡፡ ነፃነት እንደ እንጉዳይ በየዛፉ ስር ያለትልቅ መስዋዕትነት በቅሎ የሚገኝ አይደለም፡፡ ይኸንን የነፃነትን ውድነት ስንረዳ የሀገርን ዳር ድንበር ለማስከበር እንደዘመቱት አባቶቻችን ሁሉ ያለነፃነት ከመኖር ይልቅ ህፃናት ልጆቻችን ጥለን፣ ከሞቀ ቤታችን ወጥተን በእስር ቤት የሲሚንቶ ወለል ላይ መጣልን እንመርጣለን፡፡ በነገራችን ላይ ደጋግሜ ከምጠቅሳቸው ጀግኖች ጋር እራሴን እያወዳደርኩ አለመሆኑን አንባቢዎች ልብ እንድትሉልኝ እወዳለሁ፡፡ በታሪክ ኮረብቶች ላይ ከድንቅ የጀግንነት ውሎዎቻቸው ጋር ከፍ ብለው የሚታዩ ጀግኖች ጫፍ የሚደርስ አንዳች ስራ እንዳልሰራሁ ጥሩ አድርጌ እገነዘባለሁ፡፡ አላማዬ የዳር ድንበርን ሉዓላዊነት ከሰብዓዊ ሉዓላዊነት ጋር ማነፃፀር ነው፡፡

ሌላው የአገር ውስጥ ገዥዎችንን እንዴት ከውጭ ሀገር ወራዎች ጋር ያነፃፅራል? የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፡፡ ሁለቱም የዘመቱት በነፃነታችንና ሰብዓዊ ክብራችን ላይ ነው፡፡ የነፃነት ትርጉም ከሀገር ልጅነትም በላይ ነው፡፡ በሰላማዊ ትግል መንገድ ስንጓዝ ትግላችን ጨቋኝ ወንድሞቻችን ወደልባቸው እንዲመለሱና ሁላችንም በነፃነት የምንኖርባትን የጋራ ሀገር እውን እንድትሆን ከማድረግ ጋር ነው፡፡ ከዚህ በዘለለ እንዲታመሙና እንዲሞቱ አይደለም ፡፡ በእኛና በልጆቻችን ላይ እያደረሱት ያለው በደል በእነርሱም ላይ እንዲደርስ ፈፅሞ የምንመኘው ነገር አይደለም፡፡ ነ ፃነትን ከውጭ ሀገር ወራሪም ሆነ ከሀገር ውስጥ ጨቋኝ መጠበቅ መቼም በይደር የሚያዝ ተግባር አይደለም፡፡ ስለሁላችን ነፃነትና ሉዓላዊነት የተዘረጋ የተማፅኖ ቃል እንጂ፡፡ በሀሰት ‹‹አሸባሪ›› ተብለን ዘብጥያ ብንወርድም ትግሉን ከመቀጠል ውጭ ሌላ አማራጭ የለም፡፡ ነፃነትን መጠየቅና መታገል ነፃነቱን የተጠማ የነፃነት ታጋይ ሁሉ ድርሻ መሆን ይኖርበታል፤ ይሁንና የናፈቃችኋትን ነፃነት አታገኟትም ብለው ወህኒ መወርወር የአፋኞች የአፈና ተግባር ቢሆንም መንበርከክ ለከፋ መከራ፣ ለበረታ ጭቆና ከማገለጥ ውጪ ትርፍ አልባ ነው፡፡ የአሁኖቹ ገዥዎች እንደ ቀድሞዎቹ ሁሉ የተሳሳተ የፖለቲካ ባህላችን ያበቀላቸው መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡ የፖለቲካ ባህላችንና አስተሳሰባችን ካልተቀየረ እንደ እስከ አሁኑ ሁሉ ሌሎች አምባገነኖችንም ማብቀሉን ይቀጥላል፡፡

በአምስት አመት ውስጥ ማዕከላዊ እስር ቤት ሁለት ጊዜ ስታሰር፤ ሃላፊዎች ተለዋውጠው ባገኛቸውም የሁለቱም ዋና ኃላፊዎች ቃልና ተግባር ግን ትንሽ እንኳ ልዩነት አልነበረውም፡፡ በሚገርም ሁኔታ ሁለቱም እንዳገኙኝ የጠየቁኝ አንድ አይነት ጥያቄ ነበር፡፡ ‹‹ወንድ ከሆንክ ለምን ጫካ አትገባም?›› የሚል፡፡ ወንድነት ማለት አፈ-ሙዝን፤ በማይናወጥ የፍቅርና የወንድማማችነት መንገድ መጋፈጥ፤ ተጋፍጦም ሳይገሉ መሞት ነው ወይንስ በራሳችን ጥላ ሳይቀር እየደነበርን ንፁሃንን መግደል? የሚገርመው እኮ ለአፈ-ሙዝ ፍልሚያ የጥሪ ካርድ የሚበትኑት ወገኖች የደሃ ኢትዮጵያውያን ወንድማማቾችን ደም ለማፍሰስ እንጂ እነርሱማ ከመኪና ተደግፈው ለመውረድ ምንም የማይቀራቸው ናቸው፡፡ አንዳንድ በተለይም የአገዛዙ ዋነኛ ሰዎች ይችን ሀገር ለሁላችን ወደሚበጅ ንጋት ይዘዋት ለመውጣት እድሉን ለዓመታት ቢያገኙም ሊጠቀሙበት አልቻሉም፡፡ ይልቅስ እብሪት የሁለንተናቸው ማጠንጠኛ ምህዋር ሆኖአል፡፡ አንዳንዶቹን በጨረፍታ በማየት ለወንድማማችነትና የኢትዮጵያን የባጁ ችግሮች ለመፍታት በጐ አስተዋፆ ሊያደርጉ ይችሉ ይሆናል፣ ሕዝብን እንኳን ባይፈሩ ፈጣሪን ይፈሩ ይሆናል ብለን ተስፋ ብናደርግም ሁለቱንም እንደማይፈሩና የኢህአዴግ ዋና ሰዎች መለያ የሆነውን እብሪትና ሃኬት የሙጥኝ ብለው መንጐድ ቀጥለዋል፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክ አገዛዞች ከዚህ የተለየ ሲያደርጉ አልታዩም፡፡ ይኸኛው አገዛዝ ከቀድሞዎቹ ለመለየት የሚሞክረው በእውነት ላይ ያልተመሰረተ የፕሮፓጋንዳ ደመራ በማቀጣጠል ነው፡፡ የፕሮፓጋንዳ ደመራው ህዝቡንም ሆነ አገዛዙን በብርሃን እንዲመላለስ አላደረገውም፡፡ ሊያደርገውም አይችልም፡፡ አገዛዙም ሆነ ህዝቡ ከፍርሃትና ከጨለማ ጉዞ ነፃ ሊወጣ የሚችለው የእውነት ችቦ ለኩሶ ከዚያም በሚገኘው ብርሃን ዙሪያ ተሰባስቦ መወያየት ሲቻል ነው፡፡ ለዜጐች ሉዓላዊነት ክብር የሚሰጥ አገዛዝ ቢኖር የፕሮፓጋንዳ ደመራ አቀጣጥሎ በዙሪያው መጨፈር ባላስፈለገ ነበር፡፡ ምክንያቱም ተግባር ከቃላት በላይ ይናገራልና፡፡ የአገዛዙን አምባገነናዊ ባህሪዎችና ተግባሮች በመተንተን ከዚህ በላይ ጊዜ ልናጠፋ አይገባንም፡፡ ምንስ የማይታወቅ ነገር አለ? እንኳን የአፈናው ሰለባዎች ኢትዮጵያውያን ቀርቶ ዓለምም በቅጡ ተረድቶታል፡፡ አገዛዙ ለህዝብ ፈቃድ የሚገዛ ቢሆን ለመቃወም ከቤታችን መውጣት ባላስፈለገን ነበር፡፡

ትልቁ መፈተሽ ያለበት ጉዳይ ከ50 ዓመታት በላይ የአገዛዝ ስርዓትን ከኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዋር ለማስወገድ የተደረገው ጥረት፣ የተከፈለው የህይወትና የአካል መስዋዕትነት እንዴት እስካሁን ለፍሬ ሊበቃ አልቻለም? የሚለው ነው፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲዎች እስከ አሁን ቢያንስ ወደተሻለ ምዕራፍ ትግሉን ለማሸጋገር አልቻሉም? እስከ አሁን በተደራጁ የፖለቲካ ትግል ውስጥ ገብቶ ከመታገል ይልቅ በተለየና የራሳችን በሆነ መንገድ አስተዋፆ እናበረክታለን ብለን በተለያየ መስክ ተሰልፈን የምንገኝ ሰዎችም ምን ያህል አስተዋፆ አበረከትን? ብለን ራሳችንን መፈተሽ ይገባናል፡፡ ጊዜው በተግባር የማይደገፍና የተጠጋገኑ ምክንያቶችን በመደርደር ብቻ ከተጠያቂነት የምናመልጥበት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን የአፈናው ሰለባዎች መሆናችንን አለም በቅጡ ተረድቶታል፡፡ አገዛዙ ለህዝብ ፈቃድ የሚገዛ፣ የህግ የበላይነትን የሚያከበር ቢሆን ኖሮ ለመቃወም ከቤታችን መውጣት ባላስፈለገን ነበር፡፡ ትልቁ መፈተሽ ያለበት ጉዳይ ከ50 ዓመታት በላይ የአገዛዝ ስርዓትን ከኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዋር ለማስወገድ የተደረገው ጥረት፣ የተከፈለው የህይወትና የአካል መስዋዕትነት ዛሬም ለፍሬ ሊበቃ ያልቻለበትን ምክንያት ነው፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲዎችስ ስለምን ትግሉን ወደተሻለ ምዕራፍ ማሸገር ተሳናቸው? ዛሬም ድረስ የተደራጀ የፖለቲካ ትግልን ተቀላቅሎ ከመታገል ይልቅ በተለየና የራሳችን በሆነ መንገድ አስተዋፆ እናበረክታለን ብለን በተለያየ መስክ ተሰልፈን የምንገኝ ሰዎችም አበርክቶአችን ምን ያህል እንደሆነ ራሳችንን መፈተሽ ይገባናል፡፡ ጊዜው በተግባር የማይደገፍና የተጠጋገኑ ምክንያቶችን በመደርደር ብቻ ከተጠያቂነት የምናመልጥበት አይደለም፡፡ የነፃነት ጉዳይ ‹ለነገ…› ተብሎ በይደር የሚቆይ አይደለም፡፡

 

- See more at: http://www.fnotenetsanet.com/?p=5640#sthash.q1MeZSR5.dpuf

የማለዳ ወግ …አምላክ ሆይ ! የአዲሱ አመት ተስፋና ምኞታችን አሳካው !

$
0
0

YeMaleda Weg
ነብዩ ሲራክ ከሳዑዲ አረቢያ

አንድየ ሆይ! ያላንተ እዚህ መድረስ አይታሰብምና ከሁሉ አስቀድሜ ለከበረው ስምህ ፣ ለማይደፈር ለማይገሰሰው ሰማያዊ ክብርህ ፣ ለቸርነት ፣ ምህረት ይቅርታህ ምስጋና ይድረሰው ! አባታችን አዳም ትዕዛዝክህ ተላልፎ ታላቁን ስህተት ፈጸመ ፣ ከገነትም ተባረረ ! አባት ሆይ ! አዳም አጠፋ ብለህ አልተውከንም ! የምህረት አምላክ ነህና መንግስትህን እንወርስ ዘንድ በህግ ትዕዛዛትህ እንድንመራ አዘዝከን! ዳሩ ግን ትዕዛዛት ህግ ቀኖናህን ስንጥስ ኖርን … ይህ ሆነ ብለህም አልተውከንም …
ያለባላ በዘረጋህው ሰማይ ፣ ያለመሰረት ባነጠፍከው ምድር ፣ በእጹብ ስራህ የምድር መቀነት አድርገህ ባንሰራፋህው ውቅያኖስ እና ወንዝ ደምቀን ስታኖረን የምንበላው የምንጠጣውን የምንለብስ የምንጠለልበት በመለኮታዊ ስልጣን ከቸርነት እና ከምህረትህ ጋር ያልተውከን አንተው ብቻ ነህ ! እናም እናመሰግንሃለን ! ዘመን በዘመን ሲተካ ፣ ትውልድ በትውልድ ሲታደስ የዛሬ ባለተሮች ሆነናልና ለቀኖና ህግ የምንገዛ ለሰማያዊ ትዕዛዝህ የምናከብር አድርገን ! በይቅርታ ቸርነትህ ተጠብቀን አዲሱን አመት ስንቀበል የአዲሱ አመት ምኞታችን ብዙ ነው …ከሁሉም በላይ የሰው ልጅን ኢትዮጵያን እና ህዝቧን አንድነታችን ከሚያናጋ ፣ ህብረታችን ከሚንድ እኩይ ስራ ሁሉ ትጠብቃት ዘንድ ምኞቴ ነው ! በአዲሱ አመት መባቻ አሮጌው አመት ለመሸኘት ስንሰናዳ የሃገር የወገናችን ጉዳይ የሚያሳስበን የሚያስጨንቀን ተጠራርተን እንዲህ ብልን የህብረት ምኞት ተመኘን … አዲሱ ዓመት ሲጠባ፣ በአዲስ መንፈስ አዲስ ሕልም ለአገራችን ብሩህ እድገት ለወገኖቸቻችን ሰላም ጤና ህብረት ጥንካሬ የማለሙንቀዳሚ የምኞት ህልም ለማጠናከር ቃል ገባን። ኢትዮጵያ የብሔር፣ የሃይማኖት፣ የሃብት፣ የትምህርት፣ የፖለቲካ አመለካከት እና ሌሎችም ልዩነቶች አብሮነታችንን የማያደናቅፉባት፤ ከነልዩነታችን በጋራ እድገት የምንጠቀምባት፤ ለሁላችንም እኩል ዕድል እና ተጠቃሚነት የሚቀርብባት፤ ሁላችንም እንደ የችሎታችን ለጋራ ነጻነታችን፣ ደኅንነታችን እና ብልፅግናችን የምንሠራባት ሃገር ትሆን ዘንድ ተመኘን . …ለሃገራችን ብሩህ መጻኤ ህይዎት በጋራ ስኬታማ የምንሆንባት፤ እንዲሁም ሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚያፈቅራት፣ በዜግነቱ የሚደሰትባትና የሚኮራባት ኢትዮጵያ እንድትሆን በጋራ የአዲስ አመቱን አዲስ ምኞት ተመኘን ! አቤቱ የጭንቀት ምልጃ ልመናችን ተቀበለው ! ተስፋ ምኞታችን አሳካው !
ስደት ክፉ ነገር ነው … በስደት ረክሰናል ፣ በስደት ተዋርደናል ፣ በስደት መልካሙ ገጽታችን ከፍቷል ! ለስደቱ የከፋ መከራ አማኝ ለመሆኔ የአረብ አለም የገፋሁት ህይዎት አማኝ ምስክር መሆኔን በፊትህ ስመሰክር አንተ አታውቀውም ብየም አይደለም ! እናም ለቀሩው ትምህርት ቢሆን ደግሜ ደጋግሜ እናገረዋለሁ !

ለአመታት በከተምኩበት የአረቡ አለም የስደተኛ የከፋ መከራ የከፋ ነው ! የተሻለ ኑሮን ለመግፋት ከሚለው የተሻለ ኑሮ ፈላጊ ይልቅ የኑሮ ውድነት እና ድህነቱ አፈናቀሏቸው ወደ አረብ ሃገራት የሚሰደዱት ወገኖች ስቃይ በቃላት ሊገልጹት የሚቻል ያለመሆኑ ምስጥር ስደቱ ከሞት ጋር ተፋጦ የሚከወን ነው! ይህ በመኖርና አለመኖር መካከል በሚደረገው አሰቃቂ ስደት በሶማሌና በጅቡቲ እና በሳውዲ በቀይ ባህር ማዕበል እና ጭልጥ ባሉ በርሃዎች እልፍ አእላፍ ዜጎች ውሃውና በርሃው እየበላቸው በሃዘን ተለይተውናለል ! በራሳችን አዘዋዋሪ ዜጎች በንዋው ፍቅር ተለክፈው ጨክነው ጎድተውናል! ዜጎች በዘላን ሴሰኛ አረቦች እየተደፈሩ ሊናገሩት የሚሰቀጥጥ ግፍ እየተፈጸመባቸው እስከ ወዲያኛው አሸልበዋል ! ነፍሳቸውን ይማረው ! በባህር እና በበርሃዎች የቀሩትን ዜጎችስቃይ ህልፈት እያመመን ሲቀጥል በውል በማይታይ የማይጨበጥ የሃገራት የህግን ማዕቀፍ ወደ አረብ ሃገራት በኮንትራት ስራ ስም የሚሰደዱ ዜጎች ሰቆቃም ከህገወጡ ስደት ባልተለ የከፋ ሆኗል! ያሳለፍነው አሮጌ አመት ዜጎች ያለ ጠባቂ መብት አስከባሪ እንደጨው ሲበተኑ የሚሰደርስባቸው ፈተና ቀላል አልሆነም! ድህነትንና የኑሮ ውድነትን ሸሽተው የመጡ እድሜ ያልጠገቡ እህቶች እና ወንድሞች መሪር የመከራ ጩኸት ከፍ ብሎ ተሰምቷል ! ብዙዎች ድምጻቸው ሳይሰማ በግፍ ጠፍተዋል ፣ ከሞት የተረፉት በአካልና በመንፈስ ሁከት ደዌ ተሸብበው አብደውና ጨርቃቸውን በአደባባይ ጥለው ያየንበት አሰቃቂ ሰቆቃ ተስተናግዷል ! ይህ ሁሉ ግፍ ሲፈጸም ለመብት ማስጠበቁ የተሰየሙ ምስለኔዎቻችን የፈየዱልንን የመብት ጥበቃ ከማውሳት የበደሉንን በቁጭት ማዘከሩ ይቀላል ! ይህ ሆነ ብለን ግን አንተን ከማመስገን እና በጎ በጎውን ከመመኘት አንቦዝንም !
አቤቱ አምላክ ሆይ ! የምህረት የቸር አምላክ ነህና በአዲሱ አመት በስደት የተሰበረ ልባችን አጽናው ! ለሃገሩ ለወገኑ ቀናኢ መንግስት ስጠን ! ከተሰየሙለትና ከቆሙለት ሃገር ወገናዊ በጎ አላማ ይልቅ በቡድናዊ ስሜት ኑሯችን ያጨለሙትን ልብ አቅናው ! በመዋዕለ ንዋይ ታውረው በወገን ደም የሚበለጽጉትን አዘዋዋሪ ደላሎች በጭካኔ የታበለ ልብ አራራው !
ከህብረት ይልቅ መለያየትን ፣ ከሰላም ይልቅ ብጥብጥን ከመመኘት ሰውረን ! ክፉ ክፉ ከሚያሳስበን እኩይ ሰይጣናዊ ምግባር እቅበን ! ልዩነታችን ከፍቷልና በህብረት አንድነት ትስስር አሽረው ! አንድ አድርገን ! አዲሱን አመት በአዲስ ተስፋ እጀምረው ዘንድ በማወቅና ባለማዎቅ ያስቀየምኩ ፣ ያስከፋኋቸው ይቅርታየን ይቀበሉ ዘንድ ልባቸውን አራራው ! አቤቱ እግዚአብሔር አምላክ ሆይ ! አንተም በይቅርታህ ጎብኘን ! ዘመኑን የምህረትና የይቅርታ ዘመን አድርግልን !
አቤቱ ሁሉንም ማድረግ የማይሳንህ አምላክ ሆይ ! የአዲሱ አመት ተስፋና ምኞታችን አሳካው !
አሜን ! ! !
ነቢዩ ሲራክ
መስከረም 1ቀን 2006 ዓ.ም
ከሳውዲ አረቢያ

2005 እንዴት አለፈ? –የአመቱ አበይት ክንውኖች –በማህሌት ፋንታሁን Zone 9

$
0
0

ዶ/ር መሠረት ቸኮል

ዶ/ር መሠረት ቸኮል

በማሕሌት ፋንታሁን

ክቡራት የዞን 9 ነዋሪዎች ዓመቱ ከማለቁ በፊት እንዴት እንዳለፈ ለማስታወስ እንዲረዳን በማሰብ በ2005 የተከናወኑ አበይት ተግባራትን በዓመቱ የጊዜ መሥመር ላይ እንደሚከተለው ለማሳየት ሞክረናል፡፡ መልካም አዲስ ዓመት ይሁንላችሁ፡፡
መስከረም
•  መስከረም 11/2005 የተከበሩ ኃ/ማርያም ደሳለኝ የኢትዮጵያ ጠ/ሚ ሆነው፣ የተከበሩ ደመቀ መኮንን ደግሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ቃለ መሐላ ፈፀሙ፣
•  መስከረም 17 ቀን 2005 ድምፃዊ ቴድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) በሒልተን ሆቴል አንድ ሺሕ ያህል ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ጋብቻውን ፈፀመ፣
ጥቅምት
•  ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ አሜሪካን ሃገር ከሚገኘው የዓለም አቀፉ የሴቶች ሚዲያ ፋውንዴሽን የ2012 ‹ፅናት በጋዜጠኝነት ሥራ› የተሰኘ ሽልማት አገኘች፣
•  የ2005 የእስልምና ምክር ቤት /መጅሊስ/ ምርጫ በየቀበሌው ተካሄደ፣
ሕዳር
•  የጋዜጠኝነት እና የኮሚውኒኬሽን ባለሙያ ዶ/ር መሠረት ቸኮል ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፣
•  ጠ/ሚኒስቴር ኃ/ማርያም ደሳለኝ አቶ ቴድሮስ አድሃኖምን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤አቶ ሙክታር ከድር እና ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል በጠ/ሚኒስቴርነት ማዕረግ የሲቪል ሰርቪስ፣ የትራንስፖርት እና ቴክኖሎጂ ሚኒስተር፤ አቶ ከበደ ጫኔን የንግድ ሚኒስቴር እንዲሁም ዶ/ር ከሰተብርሃን አድማሱን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አድርገው ሾሙ፣
tewedrosታኅሳስ
•  በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ሦስተኛ የወንጀል ችሎት በቀረበባት የሽብርተኝነት ወንጀል 14 ዓመታት እስርና 33 ሺሕ ብር ቅጣት የተጣለባት ጋዜጠኛና መምህርት ርዕዮተ ዓለሙ፣ በይግባኝ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የእስር ጊዜዋን ወደ አምስት ዓመታት በመቀነሱ ምክንያት ለሰበር ችሎት “በሥር ፍርድ ቤቶች ውሳኔ ላይ የሕግ ስህተት ተፈፅሟል” ስትል አቤቱታ አሰምታ፤ ሠበር ሰሚ ችሎቱ በሰጠው የመጨረሻ የቅጣት ውሳኔ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤትና ጠቅላይ ፍርድ ቤት ያስተላለፉትን የቅጣት ውሳኔ አፀና፣
•  የአውሮፓ ፓርላማ አባላት ለጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በጻፉት ግልጽ ደብዳቤ፤ ከሽብርተኝነት እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ክስ ተመስርቶበት የ18 ዓመት እስር የተፈረደበት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በአፋጣኝ ከወህኒ ቤት እንዲለቀቅ ጥያቄ አቀረቡ፣
•  አራት በፍ/ቤት እስር የተፈረደባቸው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች የ2012 የሄልማን/ሃሜት ሽልማት መሸለማቸውን፤ ተሸላሚዎቹ በእስር ላይ የሚገኙት እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ ውብሸት ታዬ እንዲሁም በሌለበት የተፈረደበት የቀድሞዋ የ“አዲስ ነገር” ጋዜጣ አዘጋጅ መስፍን ነጋሽ ሲሆኑ ጋዜጠኞቹ ሽልማቱን ያገኙት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትን ለማስጠበቅ ላደረጉት ጥረት መሆኑም ተጠቅሷል፣
ጥር
•  የ33ቱ ፓርቲዎች ኅብረት በሚያዚያ ወር የተካሄደውን የአዲስ አበባ መስተዳደር እና በመላው ሃገሪቱ በሚካሄደው የወረዳና የክልል ምክርቤቶች ምርጫዎች ላይ ላለመሳተፍ ውሳኔ አሳለፉ፣
•  በአሠልጣኝ ሰውነት ቢሻው የሚመራው ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከ31 ዓመታት ቆይታ በኋላ በደቡብ አፍሪካ በሚካሄደው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለመሳተፍ በቃ፤ በዚሁ የአፍሪካ ዋንጫ ላይ አዳነ ግርማ ከ37ዓመት በኋላ የመጀመሪያ የሆነችውን ብቸኛ ጎል ለኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ አስቆጠረ፣
•  ኢትዮጵያ የራሷን ሳተላይት ለማምጠቅና የሰው ኃይሏን ከቴክኖሎጂው ጋር ለማስተዋወቅ የሚያስችል የሙከራ ሥራ መጀመሯን፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የኢኮኖሚ ዘርፍ አስተባባሪና የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ዶ/ር ደብረ ፅዮን ገብረ ሚካኤል አስታወቁ፣
•  በ2004 ከሃያ ዓመት እስር በኋላ የተፈቱት ከፍተኛ የደርግ አመራር የነበሩት ኮሎኔል ደበላ ዴንሳ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፣

አቡነ ማቲያስ

አቡነ ማቲያስ

የካቲት
•  ድምፃዊ ታምራት ሞላ ለረጅም ዓመታት ሕክምና ሲከታተል በነበረበት የደም ካንሰር ሕመም ምክንያት ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ፣
•  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤ/ክርስቲያን 6ኛውን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስን አድርጋ መረጠች፣
•  የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ጽሑፍ ተባባሪ ፕሮፌሰር የነበሩት ዶክተር ዮናስ አድማሱ በ69 ዓመታቸው ከዚህ አለም በሞት ተለዩ፣
•  በአዲስ አበባ በባሕል ሕክምና ታዋቂ የነበሩት ሐኪም ማሞ ኃይሌ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፣
•  ከሁለት ዓመት በፊት በአምባሳደርነትና በምክትል አምባሳደርነት ማዕረጐች ተሹመው በተለያዩ አገሮች ከተመደቡ የቀድሞ ከፍተኛ ባለሥልጣናት መካከል ዐሥራ ስምንት የሚሆኑት ወደ አገር እንዲመለሱ ተደረገ፤ ሁለቱ በድጋሚ ሹመት ወደሌሎች አገሮች ሲመደቡ የተቀሩት ግን በአገር እንዲቀሩ ውሳኔ ተላለፈ፣
መጋቢት
blue party•  በኢትዮጵያ ሕዝብ ክብር ተቆርቋሪ የግል ተነሳሽነት ኮሚቴ፣ በሰማያዊ ፓርቲ እና በባለራዕይ ወጣቶች ማኅበር አስተባባሪነት፤ በጣሊያን አፊሌ በተባለ ቦታ የተገነባውን የግራዚያኒ ኀውልት እና መታሰቢያ ቦታ በመቃወም፤ ከሰማእታት ኀውልት (6 ኪሎ) አንስቶ እስከ ጣሊያን ኤምባሲ የሚዘልቅ የእግር ጉዞ መጋቢት 8/2005 ጥሪ ተላለፈ፤ ሰልፉን ለማካሄድ የተገኙ አባላት እና የሰልፉ ዓላማ ደጋፊዎች ሰማእታት ኀውልት መሰባሰብ እንደ ጀመሩ ፖሊስ ሰልፉን ሕጋዊ አይደለም ብሎ በኃይል በመበተን እና 40 የሚሆኑ በሰልፉ የተገኙ ሰዎች ለአንድ ቀን ታስረው ተፈቱ፣
•  የኢሕአዴግ ዘጠነኛ ጉባዔ በባሕር ዳር ከተማ ለአራት ቀናት ተካሄደ፣
•  ‹ኢትዮትዩብ› በአሜሪካ አምስተኛ ዓመቱን አከበረ፣ በዕለቱም ‹ለፕሬስ ነፃነት የተጋ› በሚል ዓመታዊ ሽልማት ለጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ተሸላሚ በወኪል ተበረከተለት፣
•  የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መታሰቢያ “መለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን” መሥራች ጉባኤ በአፍሪካ ኅብረት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሄደ፣
ሚያዚያ
abune_petros•  ላለፉት አምስት ዓመታት በተደረገ ኮንትራት አማካኝነት በአሜሪካ ስትጎበኝ የነበረችው ሉሲ (ድንቅነሽ) ጉዞዋን ጨርሳ ወደ ሃገሯ ተመልሳ ለሕዝብ ዕይታ ክፍት ሆነች፣
•  ፒያሳ አራዳ ጊዮርጊስ ቤ/ክርስቲያን ጀርባ የሚገኘው የአቡነ ጴጥሮስ ኀውልት፤ በአዲስ አበባ በመሠራት ላይ በሚገኘው የቀላል ባቡር ግንባታ ምክንያት ከነበረበት ቦታ ተነስቶ ብሔራዊ ሙዚየም እንዲገባ ተደረገ፣
•  በጋምቤላ ክልል አኙዋክ ዞን አቦቦ ወረዳ ልዩ ቦታው ቁርጫ በሚባል አካባቢ 17 ተማሪዎችንና በኢንቨስትመንት ሥራ ላይ የተሠማራው ሳዑዲ ስታር ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ሠራተኞች የሆኑ ስድስት ሰዎችን፣ በድምሩ 23 ሰዎችን በጥይት ደብድበው በመግደልና በሽብር ወንጀል ተከሰው ከነበሩት 14 ግለሰቦች መካከል፣ ዘጠኙ በሞት እንዲቀጡ ተወሰነባቸው፣
•  ጋምቤላን ለሰባት ዓመታት በፕሬዚዳንትነት የመሩት አቶ ኡሞድ ኡቦንግ የጋምቤላ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢሕዴን) እና የክልሉ ምክር ቤት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ከፓርቲው ምክትል ሊቀመንበርነትና ከክልሉ ፕሬዚዳንትነት እንዲነሱ በመወሰኑ፣ ምክትል ፕሬዚዳንቱ አቶ ጋትሉዋክ ቱት በምትካቸው የክልሉ ፕሬዚዳንትነት ሆነው ተሾሙ፣
•  የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሰኔ 20 ቀን 2004 ዓ.ም. የሰጠውን የጥፋተኝነት ብይንና ብይኑን ተከትሎ የተጣለባቸውን የቅጣት ውሳኔ በመቃወም፣ ከነሐሴ ወር 2004 ዓ.ም. ጀምሮ በተለያዩ ጊዜያት ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የይግባኝ አቤቱታ አቅርበው በነበሩት፣ እነ እስክንድር ነጋ ላይ ሚያዝያ 24 ቀን 2005 ዓ.ም. የመጨረሻ ውሳኔ ተሰጥቶ ይግባኝ ካሉት ፍርደኞች ውስጥ ከክንፈሚካኤል ደበበ (አበበ ቀስቶ) በስተቀር የሁሉም የሥር ፍርድ ቤት ቅጣት ውሳኔ እንዲፀና ተደረገ፤ በመሆኑም ክንፈሚካኤል በሥር ፍርድ ቤት ተጥሎበት የነበረው የ25 ዓመት ፅኑ የእስራት ቅጣት ማቅለያው ሲያዝለት ወደ 16 ዓመት ፅኑ እስራት ተቀነሰ፣
•  የፌዴራሉ ዋና ኦዲተር በ124 የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች የ2004 ዓ.ም. ሒሳብን ኦዲት በማድረግ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲያቀርብ፣ መንግሥት ሊያገኘው የሚገባ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ በምን ሁኔታ ላይ እንዳለ አለመታወቁንና በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ደግሞ መንግሥት ማጣቱን አሳወቀ፤ ከዚህ ውስጥ ትምህርት ሚኒስቴር 401.757 ሚሊዮን ብር የሚሆነውን ከፍተኛ ድርሻ የያዘ ሲሆን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር 173.756 ሚሊዮን ብር፣ የግብርና ቴክኒክ ሙያና ትምህርት ሥልጠና ፕሮጀክት ማስተባበሪያ 155.597 ሚሊዮን ብር የታየባቸው መሥሪያ ቤቶች መሆናቸው ተገለፀ፣
ግንቦት
Melaku-Fenta-and-Gebrewahid-Woldegiorgis•  የፌደራል ፀረ ሙስና እና የሥነ ምግባር ኮሚሽን የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዳይሬክተር የሆኑት አቶ መላኩ ፋንታን ጨምሮ ሌሎች የባለሥልጣኑ ኃላፊዎችና ባለሀብቶች በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር በመዋላቸው የክስ የፍርድ ሒደቱ ተጀመረ፣
•  በባሕርዳር ከተማ የፌደራል ፖሊስ አባል የሆነ ግለሰብ በከፈተው ተኩስ 10 የሚሆኑ ሰዎች ሕይወታቸው ሲያልፍ ወንጀለኛው ፖሊስም ራሱን አባይ ወንዝ ውስጥ ወርውሮ ሕይወቱን አጠፋ፣
•  በኢትዮጵያ የአውሮፓ ኅብረት አምባሳደር ዣቪየር ማርሻል በ61 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፣
•  በከፍተኛ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር በዋሉት በሚኒስትር ማዕረግ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መላኩ ፈንታ ምትክ፣ የአዳማ ከተማ ከንቲባ የነበሩት አቶ በከር ሻሌ ተሾሙ፣
•  በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ በመምህርነት፣ በተመራማሪነት እና በልዩ ልዩ የኃላፊነት ቦታዎች ያገለገሉት እና “ቤተ ክሕነትና መንግሥት በኢትዮጵያ ከ1262-1527” (Church and state in Ethiopia 1262-1527) በተሰኘው መጽሐፋቸው የሚታወቁት ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፣
•  አዲስ አበባ የሚከበረውን የአፍሪካ ሕብረት 50ኛ ዓመት የወርቅ እዮቤልዩ በዓል ላይ ሰማያዊ ፓርቲ ታላቅ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጥሪ ቢያደርግም የአ.አ መስተዳድር ሰልፉን ጥበያ የሚያደርግ የፖሊስ ኃይል እጥረት አለብን በማለት ለሌላ ጊዜ እንዲያዘዋውሩት ጠየቀ፣
•  የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/የአፍሪካ ኅብረት የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች ዋናው ጽ/ቤት በሚገኝበት በኢትዮጵያ አከበረ፣
•  የሕዳሴው ግድብ ቀጣይ የግንባታ ምዕራፍ የሆነው ወንዙን አቅጣጫ የማስቀየስ ሽራ ተከናወነ፣ ይህን ተከትሎም ከሃገሪቷ ፖለቲከኞች ጋር በቀድሞው የግብፅ ፕሬዝዳንት ሙርሲ የተመራ ውይይት ሲካሄድ የግድቡ ሥራ እውን እንዳይሆን የሚያደርጉ ሐሳቦች መሰንዘራቸው፤ ይህ ውይይትም በስህተት በሃገሪቱ የብሔራዊ ቴሌቭዥን ጣቢያ በቀጥታ ተላለፈ፣
•  ሰማያዊ ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ መነሻውን የፓርቲው ፅ/ቤት፤ መድረሻ ቦታውን ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ያደረገ፣ በርካቶችን ያሳተፈ እና ከ97 ምርጫ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደ የተቃውሞ ሰልፍ አካሄደ፣
UDJ Candlelight vigilሰኔ
•  አንድነት ለፍትሕና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ‹‹ሚሊዮን ድምፆች ለነፃነት›› የተሰኘ፣ ለሦስት ወራት የሚቆይ ሕዝባዊ ንቅናቄ ጀመረ፤ በንቅናቄው ሕዝባዊ ስብሰባዎች፣ ሠላማዊ ሰልፎችና በፀረ-ሽብር ሕጉ ላይ የተቃውሞ ፊርማ እንደሚሰበሰብ ተነግሯል፣
•  ለቀደሙት 20 ወራት በሽብር ወንጀል ተፈርዶበት ቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኘው ጋዜጠኛ፣ ጦማሪ እና አራማጅ እስክንድር ነጋ፤ ከባለቤቱ እና ልጁ ውጪ በሆኑ ቤተሰቦቹ፣ ወዳጆቹ እና አድናቂዎቹ እንዲጎበኝ ሲፈቀድለት የሚጎበኝበት ሰዓትም እንደማንኛውም በማረሚያ ቤቱ የሚገኙ ታራሚዎች እንደሆን ተደረገ፣
•  በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው የ2013ቱ የቢግ ብራዘር አፍሪካ ውድድር ከኢትዮጵያ የሄደችው ቤቲ የወሲብ ትእይንና አነጋጋሪ መሆን፣
•  የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ሦስተኛውን ጨዋታ በሃገሩ አድርጎ ተጋጣሚውን ደ/አፍሪካን 2-1 በመርታት የቀሪውን ጨዋታ ነጥብ ሳያሳስበው ምድቡን በአንደኝነት መምራቱን ቢያረጋግጥም በማግስቱ በፌዴሬሽኑ ስህተት ብሔራዊ ቡድናችን ሦስት ነጥቦችንና ሦስት ጎሎች የሚያስቀጣውን ጥፋት ማጥፋቱን ተነገረ፣
•  ፓርላማው በ2005ዓ.ም የሥራ ዘመን ማጠናቀቂያ ላይ የሥልጣን ሹም ሽር በማድረግ አስር አዳዲስ ሚኒስተሮች ሾመ፣
betty-bba-chase-ethiopia•  የቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ወደ ኮንፌደሬሽን ካፕ የምድብ ማጣሪያ ያለፈ የመጀመርያ ክለብ መሆኑ፣
ሐምሌ
•  ወጣት የፖለቲካ ተንታኙ ጃዋር መሐመድ አልጀዚራ የቴሌቪዥን ጣቢያ በሚያዘጋጀው ‹ዘ ስትሪም› በተሰኘ ፕሮግራም ላይ ስለ ኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ እና ተያያዥ ጉዳዮች የብዙዎችን (በተለይም ማኅበራዊ አውታር ተጠቃሚዎችን) ትኩረት የሳበ እና ያነጋገረ ንግግር አደረገ፤
•  አንድነት ፓርቲ በጎንደርና ደሴ ከተሞች በተመሳሳይ ቀን (ሐምሌ 7/2005) ‹‹ሚሊዮን ድምፆች ለነፃነት›› በተሰኘው ሕዝባዊ ንቅናቄው ሠላማዊ ሰልፎችን አካሄደ፣
•  አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገ/ሥላሴ ከሁለት ዓመት በኋላ በሚካሄደው በ2007ቱ ጠቅላላ ምርጫ አዲስ አበባ የካ ክፍለ ከተማ በመወዳደር ወደ ፓርላማ ለመግባት ማቀዱን በቃለ ምልልሶች አረጋገጠ፣
ነሐሴ
merara gudina•  የአምስት ፓርቲዎች ጥምረት የሆነው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ ዶ/ር መረራ ጉዲናን ሊቀመንበር አድርጎ መረጠ፣
•  1434ኛው የኢድ አልፈጥር በዓል በእስልምና እምነት ተከታዮች በተለይ በአዲስ አበባ ብሔራዊ ስታዲየም ሲከበር፣ ፌደራል ፖሊስ በዓሉን ለማክበር የተገኙትን በርካታ ሰዎች ላይ እስር እና አካላዊ ጥቃት ፈፀመ፣
•  ሞስኮ በተዘጋጀው የ14ኛው የዓለም አትሌትክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ 3ት የወርቅ፣ 3ት የብር እና 4ት የነሃስ ሜዳሊያ በማግኘት ከዓለም 6ኛ ከአፍሪካ 2ኛ ሆና አጠናቀቀች፤ ወርቁን ያስገኙት ዝነኞቹ የረጅም ርቀት ተወዳዳሪዎች ጥሩነሽ ዲባባ እና መሰረት ደፋር እንዲሁም በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ የሆነውን የ800ሜ ርቀት አሸናፊ መሐመድ አማን ናቸው፣
•  የአቡነ ጳውሎስ እና የቀድሞ ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ሙት ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች ተከበሩ፤ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ሙት ዓመት ለማክበር መንግሥት አረንጓዴ ዘመቻ አደረገ፣ በርካታ ፓርኮችንም በስማቸው ተሰየመላቸው፣
•  ወጣቱ ድምፃዊ ኢዮብ መኮንን ባደረበት ድንገተኛ ሕመም ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ፣
•  የ33ቱ ፓርቲዎች ዐቢይ ኮሚቴ ባደረገው የጋራ ስብሰባ፣ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት በየጋዜጣው ላይ የሚሰጡት መግለጫ የፓርቲው አቋም መሆኑ በመረጋገጡና በጋራ ለመሥራት ከተስማሙበት የጋራ ሰነድ ውጪ ሆነው መርሖችን በመጣላቸው ምክንያት ፓርቲው ከኅብረቱ መታገዱን አሳወቁ፣
•  ሰማያዊ ፓርቲ ነሐሴ 26/2005ዓ.ም በአዲስ አበባ ሊያካሂድ ያቀደውን እና ከሦስት ወር በፊት ሲያስተዋቅ እንዲሁም ዝግጅት ሲያካሂድ የከረመበትን ሠላማዊ ሰልፍ፤ የአዲስ አበባ ፖሊስ ሰልፉ እንዳይካሄድ ከለከለ፣
•  በተለያዩ የእምነት ተቋማት ኅብረት ጠሪነት፤ በመንግሥት ወኪሎችና የኢሕአዴግ አባላት ቀስቃሽነት የሃይማኖት አክራሪነትና ፅንፈኝነትን ለመቃወም በሚል ነሐሴ 26/2005ዓ.ም በአዲስ አበባ ሰላማዊ ሠልፍ ተካሄደ፣
Ethiopia national teamጳጉሜ
• የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያ ከሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር ኮንጎ ብራዛቪል ላይ ገጥሞ ተጋጣሚውን 2 ለ 1 በመርታት፤ ምድቡን በመሪነት በማጠናቀቅ አፍሪካን የሚወክሉ 5 ቡድኖች ተለይተው ለሚወጡበት 10 ብሔራዊ ቡድኖች ለሚያደርጉት የደርሶ መልስ ጥሎ ማለፍ ከገቡት ውስጥ መካተት ቻለ፡፡

የሙስና ነገር (ክፍል ሁለት) በዳዊት ከበደ ወየሳ

$
0
0

የሙስና ነገር (ክፍል ሁለት)
በዳዊት ከበደ ወየሳ

እውነት የማይመስሉ ግን እውነት የሆኑ የሙስና ታሪኮች – በኢትዮጵያ።

አሁን በኢትዮጵያ አቆጣጠር ወደ 2006 ተሻግረናል። ከአመት ወደ አመት ስንሸጋገር ደግሞ ያለፈውን አመት የሙስና ነገር በገደምዳሜ ዳሰስ አድርገን ብናልፍ ክፋት የለውም። በመሆኑም የስራ ባልደረባዬ ክንፉ አሰፋ “ክፍል አንድ” ብሎ በጀመረው የሙስና ጉዳይ… “ክፍል ሁለት” ብዬ እኔ ቀጠልኩበት፤ አንብቡት።

የጉምሩክ ከፍተኛ ሃላፊዎች ሲታሰሩ፤ በየፊናው የነበሩ ጉምቱ ባለስልጣናት መደንገጣቸው አልቀረም። “እገሌስ መቼ ነው የሚታሰረው ወይም የምትታሰረው?” የሚለው ሹክሹክታም ከቢሮ አልፎ በአደባባይ የህዝቡ መነጋገሪያ ሆኖ ሰንብቷል። በዚያኑ ሰሞን ከኢትዮጵያ የመጣ አንድ ዘመዴ ጋር ቁጭ ብለውን ስናወራ፤ “ገብረዋህድ የሚባለውንስ እንኳንም አሰሩት።” አለኝ።

“ምነው?” አልኩት።

“በጣም መጥፎ ሰው ነው” ብሎ ጀመረልኝ – ፊቱን አጨፍግጎ። “መጥፎ ሰው ነው። አንዳንዴ እንደተራ ሰው ሻይ ቤት እና ቡና ቤት ገብቶ፤ የሆነ ነገር አዝዞ ይቀመጣል። ከዚያም አንዱ ተስተናጋጅ፤ ሂሳቡን ከፍሎ ሲወጣ፤ ድንገት ደረሰኝ ይዞ ካልወጣ…  ከመቀመጫው ተነስቶ፤ ‘ሌቦች አጭበርባሪዎች’ ብሎ ይሳደብና ፖሊስ ወዲያው ጠርቶ የንግድ ቤቱን ያሳሽጋል።” (ደረሰኝ ለደንበኛ አለመስጠት ሙስና መሆኑን እዚህ ላይ ጠቅሰን እንለፍ)… እናም ይህ የጉምሩኩ ምክትል ሰውዬ ያላስለቀሰው ነጋዴ የለም።

ደግሞም በነጋዴዎቹ ቢበቃው ጥሩ ነበር። የመስሪያ ቤቱን ሰራተኞች በሙስና እየወነጀለ ያላሳሰረው ሰራተኛ እንዳልነበር፤ የቅርብ ሰዎች ያወራሉ። እዚህ ላይ አንድ አስቂኝ ነገር አለ። ይሄ ለሰማይና ለመሬት ከብዶ ህዝቡን ሲያስለቅስ የነበረ ሰውዬ በመጨረሻ የሱም ቀን ደረሰና ሊታሰር ሆነ። እናም በቁጥጥር ስር በዋለበት ቀን፤ ሁለት የፌዴራል ፖሊስ አባላት ወደ ቢሮው ገብተው በቁጥጥር ስር ሊያውሉት ሲሉ ይደነፋል።

“ማን እንደሆንኩ ታውቃለህ?” ይላል።

“አዎ እናውቃለን!” አሉት። አንድ ሁለት ቃል ከተለዋወጡ በኋላ፤ ልክ እንደ ነጋ ገብረእግዚአብሄር – አንቱ ወደተባሉ ከፍተኛ የህወሃት አባላት ስልክ መደወል ይጀምራል። ከባለስልጣናቱ የሚሰማው ነገር ያልጠበቀው ነበር። በመሃል ፌዴራል ፖሊሶቹ ከቢሮው እንዲወጡ ያደርግና ከውስጥ በኩል የቢሮውን በር ይቆልፈዋል። ፖሊሶቹ ቢያንኳኩ – ቢያንኳኩ የሚከፍት ሰው ጠፋ። የጉምሩክ መስሪያ ቤት ተጨነቀ። በቢሮ አካባቢ ያሉት “በቃ ይሄ ሰውዬ እንደ አጼ ቴዎድሮስ የራሱን ህይወት ሊያጠፋ ነው” ብለው በመስጋት፤ ከአሁን አሁን የተኩስ ድምጽ በጉጉት ይጠባበቃሉ። ሌሎች የግቢው ጥበቃ ሰራተኞች ደግሞ፤ ‘ከፎቅ ላይ ራሱን ወርውሮ ይገድላል’ በሚል ስጋት አንገታቸውን ወደ ፎቁ አንጋጠው፤ ድንገት ከፎቅ ላይ ሲወድቅ ሮጠው እንደኳስ ሊቀልቡት ተዘጋጅተዋል። ይሄ ሁሉ ሲሆን፤ ሰውየው ቢሮውን ቆልፎ ከህወሃት ባለስልጣናት እስከ ጠቅላይ ሚንስትሩ ቢሮ ድረስ ስልክ እየደወለ ነበር።

የደወለላቸው ባለስልጣናት በሙሉ ለራሳቸው በመስጋት የተለያየ ምክንያት እየሰጡ ስልኩን ጆሮው ላይ ዘጉበት። በዚህች ቀውጢ ወቅት በመከላከያ ውስጥ የኮሎኔል ማዕረግ የተሰጣት፤ እጩ ጄነራል ሚስቱም ልታድነው አልቻለችም። ፌዴራሎቹ ጉዳዩን አስመልክተው ወደ አለቆቻቸው ደወሉ። “ሰውየው እራሱን እንዳያጠፋ ስለሰጋን ነው” አሉ።

ከአለቆቻቸው የተሰጣቸው መልስ አጭር ነበር። “እራሱን አያጠፋም። ተጨማሪ ትዕዛዝ እስከሚሰጥ ድረስ እዚያው ቆዩ”።

“ሰራተኛ ሲወጣ፤ እሱ ከቢሮ ካልወጣ ሰብራችሁ ትገባላችሁ” ተባሉ። ፖሊሶቹም ሰራተኛው ከስራ እስኪወጣ መጠባበቅ ጀመሩ። ሰራተኛው ከወጣ በኋላ፤ ፌዴራሎቹ በር የሚሰብሩበትን መሳሪያ እያፈላለጉ ሳለ ገብረዋህድ ከተደበቀበት ቢሮ ሹክክ ብሎ ወጣ።

“ምነው ብዙ የምታስጠብቀን?” ብለው ጠየቁት ፌዴራሎቹ።

“በሰራተኛው ፊት ታስሬ መሄድ ስላልፈለኩ ነው” አላቸው።

ገብረዋህድ በማግስቱ የፈራው ደረሰበት።  ለፖሊስ ቃሉን ከሰጠ በኋላ፤ በሚቀጥለው ቀን የመንግስት ንብረት እንዲያስረክብ ወደ ጉምሩክ ሲወሰድ፤ በሰራተኞቹ ፊት ሁለት እጁን ተጠንጎና በፌዴራል ፖሊሶች እየተጎነተለ መጣ። “ከዚህ በላይ ውርደት?” ብለን ቃሉን አለመጨረሹ ይሻለናል።

ሌላም የሚገርም ነገር አለ። ይሄ ሰው ከመታሰሩ አንድ ወር በፊት በመላው አገሪቱ የሚገኙ የጉምሩክ ባለስልጣናትን በኮንፈረንስ ስብሰባ አድርጎ ነበር። የፈረደበትን የሟቹን ጠቅላይ ሚንስትር ፎቶ በመለጠፍም “በሙስና ለምትጨማለቁት እንደደርግ ጥይት አናጎርሳችሁም፤ እናስራችኋለን።” እያለ ስለመለስ ራዕይ ሲያወራ ነበር። በንግግሩም መጨረሻ፤ (ያን ሰሞን የመለስ ሚስት የምኒልክን ቤተ መንግስት ለቅቃ ነበርና…) “በአሁኗ ደቂቃ የመለስ ዜናዊ ልጆች መኖሪያ ቤት እንኳን የላቸውም። ሜዳ ላይ ነው የቀሩት።” ሲል የዋሆቹ ሲያለቅሱ፤ ነገሩን የሚያውቁ ግን ስቅስቅ ብለው ይስቁ ነበር።

ገብረዋህድ ከታሰረ በኋላ በስሙ የአርሲን ቆዳ ስፋት የሚያህሉ የቤት ካርታዎች ሲገኙ፤ “ምናለበት አንዱን ቤት ሜዳ ላይ ለወደቁት ለመለስ ዜናዊ ልጆች ቢሰጣቸው ኖሮ?” መባሉ አልቀረም።

ወደ አዲስ አበባ ከተማ ሲገቡ፤ ቦሌ መንገድ ላይ ያሉትን ህንጻዎች ከተመለከቱ፤ ህዝቡ ራሱ እንደጎበዝ አስጎብኚ ይነግርዎታል። “ይሄ ህንጻ የጄነራል ጻድቃን ነው። ይሄኛው የጄነራል እገሌ ነው እያሉ፤ መድሃኔአለም ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊት ከሚገኘው ኤድናሞል ህንጻ ጋ ሲደርሱ ደግሞ “ከጎኑ ያለው የሚያምር ህንጻ የጄነራል አባ ዱላ ነበር።” ይሏችኋል።

“አሁንስ የማነው?” ካሉ አስጎብኚዎ የሙስናን ነገር እያጣቀሰ ወሬውን ሊቀጥል ይችላል። እኛም እንንገርዎ – የነ አባ ዱላን ነገር። አባ ዱላ ገመዳ አሁን የፓርላማው አፈ ጉባዔ ነው። ከዚያ በፊት የኦሮሚያ ፕሬዘዳንት፡ ከዚያም በፊት የመከላከያ ሚንስትር፡ ከዚያ በፊት በሻዕቢያ የተማረከ የደርግ ወታደር ነበር… መቼም አንድ ወታደር ለሻዕቢያ እጅ ሰጥቶ ከተማረከ ከዚያ በፊት ምን ነበር? ተብሎ አይጠየቅም። እናም አባዱላ እና በሙስና ስለተሰራው ትልቅ ቤተ መንግስት የመሰለ ቤታቸው ከማውራታችን በፊት፤ ሰውየው ሌሎቹን ጄነራሎች ጭምር እንዴት በሙስና እንዳነካኩ ላጫውታችሁ።

በአንድ ወቅት ለጄነራሎቹ (ያው ከአባ ዱላ በቀር ብዙዎቹ ህወሃቶች ናቸው) አዲስ አበባ ውስጥ መኖሪያ እንዲሰሩ መሬት ተሰጣቸው። የሲሚንቶ እና የሌላ ሌላው ነገር ዋጋ መጨመርን ተከትሎ የብዙዎቹ አቅም የሚችለው አልሆነም። እናም የኦሮሚያ ፕሬዘዳንት የነበሩት አባ ዱላ ገመዳ ከሌሎቹ ጄነራሎች ጋር በመመሳጠር በኦሮሚያ የሚገኙ መሬቶች፤ እየተሸነሸኑ ለጄነራሎቹ በስጦታ መልክ እንዲሰጣቸው አደረጉ። ይህ የተደረገው ያለ ምክንያት አይደለም። በኋላ ላይ ጄነራሎቹ በኦሮሚያ ባለስልጣናት የተሰጣቸውን መሬት እየሸጡ፤ አዲስ አበባ ላይ በተሰጣቸው መሬት ላይ ህንጻ

ከቢሾፍቱ እስከ አዳማ፤ አልፎም እስከ ሻሸመኔ ድረስ ያሉ መሬቶች በዚህ አይነት የሙስና ቅብብሎሽ ለጄነራሎቹ ታደሉ። አባ ዱላ ገመዳ ይሄንን ሁሉ ሲያደርግ፤ ለሱም ትንሽ ጉርሻ ይሰጠው ነበር። ያቺ በጉቦም በ እጅ መንሻም ያገኛትን ገንዘብ ሰብስቦ ቦሌ መድሃኔአለም ፊት ለፊት የተንጣለለ ህንጻ መገንባት ጀመረ።

እንግዲህ ልብ በሉ። በቦሌ መንገድ እርስዎ ብቻ አይደሉም የሚሄዱት- ሟቹ ጠቅላይ ሚንትርም በዚያ መንገድ ብዙ ጊዜ ተመላልሰው ነበር – ያውም መንገድ እየተዘጋ። እናም አስጎብኚው ለርስዎ እንደሚነግርዎ ለመለስ ዜናዊም፤ “ይሄ የእገሌ ነው። ይሄኛው የጓደኛችን እገሌ ነው።” መባሉ አልቀረም። ነገር ግን ሟቹ ጠቅላይ ሚንስትርም ቢሆኑ፤ የስርአቱ ዋነኛ መገለጫ የሆነውን የሙስና አደጋ በዝምታ ሲያልፉት ነበር። የኢህአዴግ ሰዎች ሙስናን እንደጥፋት የሚያዩት ከዚያ ሰውዬ ጋር እስከሚጣሉ ድረስ ነው። እናም ከአባ ዱላ ጋር እስከሚጣሉና የጄነራልነት ማዕረጉን እስከሚገፈፍ ድረስ ምንም አላሉም። በኋላ ላይ ግን… አባ ዱላ ከህወሃት ሰዎች ጋር ሳይሆን ከራሱ ሰዎች ጋር መጋጨት ጀመረ። በተለይም በኦህዴድ ውስጥ ካለው ከነ ግርማ ብሩ ቡድን ጋር ክፉኛ ተጋጨ – የቁርጡ ቀን ሲመጣም በመታሰር፣ ክብርን በማጣት እና ንብረቱን በመስጠት መካከል ዋዠቀ።

በመጨረሻ አባ ዱላ ገመዳ ያሰራውን እና ሊኖርበት የነበረው በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ የወጣበት ባለ ትልቅ ግቢ ቪላ ጥያቄ ውስጥ ገባ። ጸቡ እየከረረ ሲመጣ፤ በመጀመሪያ ደረጃ ያሰራው ትልቅ ህንጻ በሙስና መሆኑን ነገሩት። መጀመሪያ ሊከራከር ፈለገ። በኋላ ላይ ግን ደሞዙና የወጣው ወጪ እንደማይመጣጠን ሂሳቡን ሰርተው ሲያሳዩት፤ “አይ እኔ እንኳን Surprise ላደርጋችሁ ብዬ ነው” አለ።

ኦህዴዶቹም በመገረም፤ “ምንድነው Surprise የምታደርገን?” ሲሉ ጠየቁት።

“ይሄንን ቤተመንግስት የመሰለ ቪላ የሰራሁት ለኔ ሳይሆን፤ ለድርጅታችን ነው።” ብሎ የቤቱን ቁልፍ ሲያስረክብ፤ አጨብጭበው ዝም አሉት። አሁን በቦሌ በኩል ስታልፉ፤ “ይሄኛው የጄነራል አባ ዱላ ነበር” ይሏችኋል። ከርክክቡ በኋላ ግን የኦህዴድ ዋና ጽህፈት ቤት ሆኗል – እውነት የማይመስል የአገራችንን ታሪክ ነው እያወጋናችሁ ያለነው።

ባለስልጣናቱ “Surprise” ከመባላቸው በፊት፤ እዚያው ቤት ምሳም እራት ተጋብዘው በልተዋል። የቤት ምርቃቱ ጊዜ፤ ስጦታ ይዘው መጥተዋል። ጸቡ ሲመጣ ዝምድናው ወደ ሙስና ተቀይሮ፤ አባ ዱላ ገመዳ ቪላ ቤቱን ከነ ሙሉ እቃው የኦሮሚያ ቤተ መንግስት እንዲሆን ሰጥቶ ከመታሰር አመለጠ። የጄነራልነት ማዕረጉን ከመቀማት ግን አልዳነም። ከመከላከያ ሚንስትርነትም ሆነ ከኦሮሚያ ፕሬዘዳንትነት በጥፋት ተወንጅሎ ከተነሳ በኋላ ይህንን ታማኝ ሰው ሙስና የሌለበት ቦታ ሊመድቡት ፈልገው ክፍት የስራ ቦታ ፓርላማ ውስጥ ተገኘ። እናም የፓርላማው አፈ ጉባኤ በመሆን፤ ኢህአዴግን በማገልገል ላይ ይገኛል – አባ ዱላ (ምናሴ ገብረማርያም )።

እንግዲህ ይህ ሙስና የምንለው ነገር… ዋናዎቹን ሰዎች እስካላስከፋ ድረስ፤ በኢህአዴጎች ዘንድ እንደባህል የሚቆጠር ነውር ያልሆነ ተግባር ነው። የሙስና ነገር አውርተን… የኢህአዴግ ሙስና እመቤት ስለሆነችው ወ/ሮ አዜብ መስፍን ሳንጨዋወት ብንቀር እሳቸውም ቅር ይላቸዋልና ስለ ወይዘሮዋ ትንሽ እንዙር።

በአንድ ወቅት ለጄነራሎቹ መሬት ሲታደል ወይዘሮዋ ቦታ አምልጧቸው ኖሮ ተናደዋል። ወደ አዳማም ሆነ ቢሾፍቱ ደውለው ቢጠይቁ፤ “መሬት ተወዲ’ዩ” አሏቸው። ቆይተው ግን በኦሮሚያ ሰበታ ከተማ መሬት መሰጠት መጀመሩን ሰምተው፤ እንዲሰጣቸው ጠየቁና ተሰጣቸው። ከዚያም የሚያውቋቸውን ሰዎች እየላኩ መሬት ያሳድሉ ጀመር። በኋላ ላይ… የሰበታ ከተማ አስተዳዳሪዎች ሁኔታው ሲበዛባቸው፤ በወ/ሮ አዜብ አማካኝነት የሚላኩትን ሰዎች መሬት ከለከሏቸው። በዚህን ጊዜ ወ/ሮ አዜብ መስፍን እሳት ለብሰው፣ እሳት ጎርሰው ለከተማው አስተዳዳሪ ደወሉና ከፍ ዝቅ አድርገው ተናገሩት። በመጨረሻ የሆነው ነገር ነው የሚገርመው… ወይዘሮዋ ዛቻ ቢጤ አሰሙ። እንዲህ ሲሉ።

“እንዲያውም በሰበታ አካባቢ ሙስና አብዝታችኋል ማለት ነው! ሙስና ስላበዛችሁ ግምገማ መደረግ አለበት።”

ወ/ሮ አዜብ እንዳሉትም በህወሃት ሰዎች ታጅበው ሰበታ ከተማ በመገኘት የመንግስት ሃላፊዎችን ከላይ እስከታች አተረማመሷቸው። ለሳቸው መሬት የሰጧቸው ሰዎች ሳይቀር፤ በሙስና ተወንጅለው እየተለቀሙ ታሰሩ። መሃንዲሱ እና መሬት ፈቃጆቹ ሁሉ ተቀፈደዱ። ከዚያም የራሳቸውን ታማኞች ሹመው ሰበታ ከተማን ለቀው ተመለሱ። ባለፈው አመት ኢቲቪ ስመለከት እነዚያ በሰበታ ከተማ “ሙስና ውስጥ አላችሁበት” የተባሉ ሰዎች እያንዳንዳቸው ከአስር አመት በላይ እንደተፈረደባቸው ሰማሁ። በርግጥ ሰዎቹ ሙስና ውስጥ ነበሩበት። ቢሆንም ግን ለወ/ሮ አዜብ መስፍን እና ለሌሎች መሬት ሲሰጡ፤ ሙስና አልተባለም… የአዜብን “ትዕዛዝ አንቀበልም” ሲሉ ግን የጨዋታው ህግ ተቀይሮ፤ ሰዎቹ በሙስና ወንጀል እየተለቀሙ ወህኒ ወረዱ።

መቼም የወ/ሮ አዜብ መስፍን ታሪክ ማለቂያ የለውም። ባለፈው ሰሞን ደሞ፤ አቶ አያሌው የተባሉ ትልቅ ባለሃብት ፍርድ ቤት ቀርበው ሲናገሩ፤ “ክቡር ፍርድ ቤት እኔ ምንም ጥፋት እንደሌለብኝ አቃቤ ህጉም ያውቀዋል። የኔ ጥፋት ከወ/ሮ አዜብ መስፍን ጋር በሽርካነት እንድሰራ ተጠይቄ እምቢ ማለቴ ነው።” ብለው ነበር። አቶ አያሌው በተከበሩበት አገር አስራ ስድስት አመት ተፈርዶባቸው ወደ እስር ቤት መወርወራቸውን ከጥቂት ወራት በፊት ስንሰማ ማዘናችን አልቀረም። እንግዲህ አቶ አያሌው በደርግ የሶሻሊዝም ዘመን ሳይቀር በንግድ ሙያ ውስጥ የቆዩ ናቸው። የደርግ ዘመን አልፎ በዘመነ – ነጻ ገበያ ሲታሰሩ ያልገረመው ሰው የለም።

እዚህ ላይ የምናወራው ላይ ላዩን የምናውቀውን… እውነት የማይመስል፤ ነገር ግን እውነት የሆኑ የሙስና ታሪኮችን ነው። ውስጥ ውስጡን የማናውቀው ብዙ ነገር ሊኖር እንደሚችል ምንም አያጠያይቅም። ሌላ ነገር ትውስ አለኝ። የዛሬ 12 አመት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ወደ አሜሪካ ሲመላለሱ፤ ብዙም አይን የሚገቡ ሰው አልነበሩም። ሃብታቸውም ሰማይ አልደረሰም ነበርና ብዙዎች ትኩረት አንሰጣቸውም ኖሯል። ሆኖም እዚሁ አሜሪካ ኮሎምበስ ኦሃዮ ለምትገኘው እህታቸው፤ 250 ሺህ ዶላር ካሽ ከፍለው ቪላ ቤት ሲገዙ ብዙዎቻችን ማመን አቃተን። እናም ‘አዜብ ሙስና ውስጥ የለችበትም’ እያለ ለሚጨቀጭቀኝ ዘመዷ ስልክ ደወልኩና ጠየኩት።

“የምንሰማው እውነት ነወይ?” አልኩት።

“ምኑ?” አለኝ።

“ዘመድህ ካሽ ከፍላ ለእህቷ ቪላ ቤት የመግዛቷ ነገር…” ብዬ ሳልጨርስ፤ የነገሩን እውነተኛነት አረጋግጦ በትህትና ሊያስረዳኝ ሞከረ።

“እሷም ሆኑ ልጆቿ ሲመጡ የሚያርፉበት ቤት ያስፈልጋቸዋል። … ታዲያ ይህን ማድረጓ ምን ያስደንቃል?” የሚል አይነት ምላሽ ሰጠኝ። ለነገሩ ከደጃዝማች ጎላ የሚወለዱ፤ የነአዜብ መስፍን የቅርብ ዘመዶች ብዙ ናቸው። ድርጊቷን የሚደግፉ እንዳሉ ሁሉ፤ በግልጽ የሚቃወሟትም አሉ። ለገንዘብ ሳይሆን ለህሊናቸው ላደሩ ዘመዶቿ አክብሮት እንዳለኝ በዚህ አጋጣሚ ጠቅሼ የውጪ ሃብት ግዢውን ነገር እዚህ ላይ ገታ ላድርገው።

          የ”ደቡብ ክልል” ፕሬዚዳንት የነበሩት የአቶ አባተ ኪሾ ጉዳይም አለ። አባተ ኪሾ  ከወያኔ ሳይጣሉ ከደቡብ በጀት ተመላሽ የሆነ ሰባ ሚሊዮን ብር (70.000.000) ለመንግስት ተመላሽ ሊያደርጉ ሲሉወዲህ በል! የምን መንግስት ነው?” በማለት ወ/ሮ አዜብ ተቀብለው ወስደዋል።  ብሩ ወደ አዜብ ካዝና ይግባ እንጂ የፖለቲካ ቂም የተቋጠረባቸው አቶ አባተ ወደ ወህኒ ከመወርወር አልዳኑም። አቶ አባተ ኪሾ ይህንን ጉዳይ /ቤትም ጭምር ምስክር ሰጥተውበት ነበር።

 

የወ/ሮ አዜብን ጉዳይ ጨርሼ ወደሌሎቹ መሄድ ብፈልግም። ብዙ እውነት የማይመስሉ፤ ነገር ግን እውነት የሆኑ አስገራሚ ነገሮች ታወሱኝ። ስለሁሉም ነገር ምንም ማለት ስለማልችል ጥቂት ነገር ብዬ የሴትዮዋን ነገር ልቋጭ። በኢትዮጵያ የፀረ ሙስና ኮሚሽን ሲቋቋም በዋናነት እንዲሰራ ከታዘዙት ነገሮች አንዱ፤ የመንግስት ባለስልጣናት ሃብታቸውን እንዲያስመዘግቡ ማስደረግ ነው። ይህ ስራ እንደተጀመረ… “አሻፈረኝ አላስመዘግብም” ካሉት ውስጥ ወ/ሮ አዜብ እና የህወሃት ጄነራሎች መሆናቸውን ከዚህ በፊት በሌላ ጉዳይ ላይ ጠቅሼው ነበር። አሁንም ልድገመው። እናም የወ/ሮ አዜብ መስፍን የሃብት መጠንም ሆነ ምንጭ እስካሁን ድረስ በመንግስት ደረጃ አልተመዘገበም። አሁንማ ሴትዮዋ ጥቁር ሲለብሱ፤ ጥቁር ለብሰው የሚያጅቧቸው፤ ሲያስነጥሳቸው መሀረብ የሚያቀብሉ አሽከሮች አላቸው። ሴትዮዋ ከመለስ ዜናዊ ሞት በኋላ እንደጎማ ተንፈስ ብለዋል። ሜጋ ሚሊዮን ዶላር ከሚያንቀሳቅሰው የህወሃት ኤፈርት ሊቀመንበርነት ተነስተው፤ የመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን ዛፍ አስተካይ ከመሆን ያለፈ ስልጣን እንደሌላቸው እየስማን ነው።

 

በሌሎች ላይ የሚደረገውን የሙስና ክስ አመሰራረት እያየን… “የሙስና እመቤቷ ወ/ሮ አዜብ እና ሌሎች የኢህአዴግ ሰዎችስ ተራ መቼ ይሆን?” ማለታችን አልቀረም። ደግሞም “የጉምሩክ ባለስልጣናት ሲታሰሩ ዋነኛውን ሃላፊ አቶ መላኩ ፈንታን ወንጀል አግኝተውበት ይመስላችኋል?” አይደለም። ነገሩ የህወሃቱን ገብረዋህድ ብቻውን ቢያስሩት በህወሃት አካባቢ ከፍተኛ ጫጫታ መምጣቱ አይቀርም። ስለዚህ ከብአዴንም “የአማራ ድርጅት አባል አስረናል” በማለት ነገሩን ለማብረድ የተጠቀሙበት ነው የሚመስለው።

 

ባለፈው አመት ብቻ ምን ያህል ሙስና እንደተፈጸመ እናውጋ እና እንለያይ። ባለፈው አመት (እ.ኢ.አ 2005) ከ1 ሺህ 500 በላይ ጥቆማዎች ለፀረ ሙስና ኮሚሽን ደርሰው በ200 ያህሉ ላይ ክትትል አድርጓል። የሚገርመው ግን ከሁለት ሺህ በላይ ጥቆማዎች ደግሞ፤ ከስልጣኔ በላይ ነው በማለት ባሉበት ትቷቸዋል። (ይህንን መረጃ ያገኘነው ከራሱ ከፀረ ሙስና መስሪያ ቤት ነው።) እነዚህ ከፀረ ሙስና ኮሚሽን አቅም በላይ የሆኑት እንግዲህ፤ የጄነራሎቹ፣ የነአዜብ እና የህወሃት ከፍተኛ ንብረት እና የመከላከያ ጉዳይ መሆኑ ነው።

ለመሆኑ መከላከያ ሚንስቴር መስሪያ ቤቱ በሙስና ተወዳዳሪ ያልተገኘለት፤ ከፌዴራል መንግስት ውጪ የራሱ ባለ አምስት ሆቴል እና ሌሎች የንግድ ስራዎችና ገቢዎች እንዳለው ያውቃሉ? የምናወራው እውነት ስለማይመስሎት፤ የሙስና ታሪካችን ስለሆነ አብረውን ይቆዩ።

 

ፀረ ሙስና ኮሚሽኑ ከስልጣኑ ውጪ ያሉትን ሙስናዎች አይከታተልም። እናም ከዚህ በታች ያሉት ኮሚሽኑ እርምጃ ስለወሰደባቸው ጉዳዮች ነው።

 

ባለፉት ሁለት አመታት ከአንድ ሺህ በላይ የሙስና ክሶች ተከፍተው፤ ጉዳያቸው በፍርድ ቤት ታይቷል ወይም እየታየ ነው። እውነት ከማይመስሉ መካከል አንዳንዶቹን እንጥቀስ። በየሰፈሩ ወጣቶችን ሳያደራጁ፤ ያደራጁ አስመስለው መሬት የወሰዱ የኢህአዴግ  አባላት ብዙ ናቸው። የሃሰት የማህበራት ማደራጃ ሰነድ በማዘጋጀት ግምቱ 25 ሚሊዮን ብር የሆነ መሬት በነዚህ ሰዎች እንደአባት ውርስ ። ከሰላሳ ሚሊዮን ግምት በላይ ያለው 4ሺህ ካሬ መሬትም በ’ነዚህ የኢህአዴግ ሰዎች ያለአግባብ ወደ ግል ይዞታነት ተቀይረዋል ወይም ካርታ ወጥቶባቸዋል፤ አልፎ ተርፎም የገንዘብ ብድር ተወስዶባቸዋል። ግምቱ 842 ሚሊዮን ብር የሆነ መሬትም ያለአግባብ በግለሰቦች እጅ ገብቶ፤ የፀረ ሙስና ኮሚሽኑ የሚያደርገው ጠፍቶት፤ ግራ እንደተጋባ 2006 ዓ.ም. ገብቷል።

 

የኢህአዴግ አባላትና ሹመኞች በመሬት ቅርምት ብቻ አያበቁም። ጉምሩክ መስሪያ ቤት ዋነኛ የገቢ ምንጫቸው ነበር። በኮንትርባንድ የተያዘን ለዋስትና የተያዘን ቦንድ ሰነድ በማጥፋት ገንዘቡን ቅርጥፍ አድርገው ይበሉታል። የኢህአዴግ ወዳጆች ወይም ጉቦ የሚሰጡትን አነስተኛ የታክስ መጠን በማስከፈል ከመቶ ሚሊዮን ብር በላይ ወደ ግለሰቦች ኪስ ገቢ ሆኗል።

 

በመንግስት መስሪያ ቤቶች ትላልቅ ግዥና ሽያጭ ሲደረግ ያለው ማጭበርበር ደግሞ አይን ያወጣ ነው። የአፋር መስተዳድር ቻይናዎች መንገድ እንዲሰሩ ከተዋዋሉ በኋላ የፌዴራሉ መንግስት የሰጣቸውን 10.7 ሚሊዮን ብር እጃቸው አስገብተው ከመብላታቸው በፊት ተይዘዋል። እንዲህ አይነት ብዙ ታሪክ  መዘርዘር ይቻላል። ባለፈው አመት ብቻ ልዩ ልዩ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ባወጧቸው ጨረታዎች እና የሃራጅ ሽያጮች 3 መቶ ሚሊዮን ብር ተጨበርብሮ የተያዙም የተፈቱም ሰዎች አሉ።

 

ከፊንጫ ስኳር ፋብሪካ 75 ሚሊዮን ብር መሰረቁን እንንገርዎና በየመስሪያ ቤቱ እንዲህ ያለው ማጭበርበር ምን ያህል ሊሆን እንደሚችል እርስዎ ይገምቱ።

 

“በኢትዮጵያ አየር መንገድ በኩል የሚመጡ ተጓዦች ንብረት መጥፋቱንስ ሰምተው ይሆን?” አዎ ባለፈው አመት ብቻ፤ ከሰባት ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው ንብረቶች እና ሻንጣዎች ጠፍተዋል።

 

“ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም” ነው የሚባለው… እንዲህ እንዲህ እያልን፤ የዳኛውንም፣ የጉቦኛውንም ታሪክ እያወራን ከቀጠልን ጊዜና ምሽቱ ላይበቃን ነው። ስለዚህ የሰማነውን በልቦናችን ያሳድርልን በማለት ልንለያቹህ ነው። ጊዜ አግኝተን እንደገና ከተጨዋወትን ከአጼ ምኒልክ ቤተመንግስት ስለተሰረቁት የወርቅ ሹካ እና ማንኪያዎች ጭምር እናወጋለን። እንደገና ከተገናኘን የአጼ ኃይለስላሴ የወርቅ ቀለበት ስርቆት እንጨዋወታለን። አረ ሌላም አለ። የአጼ ምኒልክን ሽጉጥ ሰርቆ፤ መጠጥ ቤት ሲፎልል የነበረን አንድ የኢህአዴግ ኮሎኔል ኢትዮጵያ ውስጥ በሚታተመው ጋዜጣዬ ላይ አጋልጠነው ነበር። በአገራችን የሚፈጸመው እውነት የማይመስለን የኢህአዴግ ሙስና ማብቂያ ያለው አይመስልም። በዚሁ እንሰነባበት… መልካም አዲስ አመት።

 

Pen

በበዓል የረሃብ አድማ!! –ርዕዮት ምን ልትነግረን ነው?

$
0
0

ከዳዊት ሰለሞን (ጋዜጠኛ)

በብሄራዊ በዓላት ቀን በአብዛኛው ከወደ እስር ቤት የሚሰማው ዜና አስደሳች ነበር፡፡ይህንን አጼዎቹ ፣ሰው በላው የደርግ ስርዓትና ብሶት ወለደኝ ያለን ኢህአዴግ ሲያደርጉት ቆይተዋል፡፡በዘንድሮው አዲስ አመትም የመንግስትን ይቅርታ በማግኘት ከወዳጅ ዘመዶቻቸው የተቀላቀሉ ስለመኖራቸው ተሰምቷል፡፡በአዲሱ ዓመት ይቅርታ ከተቸራቸው እስረኞች መካከል ታዋቂ ፖለቲከኞች፣አክቲቪስቶችና ጋዜጠኞች አለመኖራቸው ተፈቺዎቹ በደረቅ ወንጀል ታስረው የነበሩ መሆናቸውን ለመናገር ብዙ መድከም አይጠይቅም፡፡
መንገስት ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ፣ሂሩት ክፍሌና ዘሪሁን ገ/እግዚአብሄር አቅርበውት ለነበረ የይቅርታ አቤቱታ የእምቢታ ምላሽ መስጠቱም ይቅርታ የሚገባውና የማይገባው በመንግስት ማውጫ ውስጥ ስለ መኖሩ ማሳያ ነው፡፡የይቅርታው ጉዳይ ለጊዜው ይዘግይልንና በጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ ላይ በበዓል ቀን ስለ ተፈጸመ ግፍ ላካፍላችሁ፡፡

 ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ

ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ


ጋዜጠኛዋን በበዓሉ ዋዜማ ለመጠየቅ ወደ ቃሊቲ አምርተን ነበር፡፡በመጠየቂያ ሰዓት መድረስ የቻልን ቢሆንም ጥበቃዎቹ ‹‹ርዕዮት የምትጠየቀው በዋናው በር ሆኗል፡፡ስለዚህ ወደ ዋናው በር ሂዱ›› አሉን፡፡ዋናው በር ፈጣን ተራማጅ በ10 ደቂቃ የሚደርስበት በመሆኑ ሰዓቱ እንዳይረፍድና እንዳንከለከል በማለት መሮጥ ጀመርን፡፡
ዋናው በር ግብረ ገብነት አልያም ፖሊሳዊ ስነ ምግባር በዞረበት ለሰላምታ እንኳ አግኝቷቸው የማያውቁ የሚመስሉ ጠባቂዎች ‹‹በዚህ በኩል እስረኛ አይጠየቅም ሂዱ ››አሉን፡፡ግትር ብለን በዚህ በኩል ግቡ ተብለናል አልን፡፡ሰዓቱ እየሄደ ፖሊሶቹም በአቋማችን የበለጠ በመበሳጨት እየዛቱ ነው ፡፡በመካከሉ የርዕዮት ታናሽ እህት እስከዳር አለሙና እጮኛዋ ስለሺ ሀጎስ ከግቢው ውስጥ እየተጣደፉ ወጡ፡፡
ስለሺ አንገቱን አቀርቅሮ እጆቹን እያወናጨፈ ብቻውን ያወራል፣እስከዳርን በሙሉ አይን ማየት ያስፈራል፡፡ ፊቷ በርበሬ መስሎ በእንባ ጎርፍ እየታጠበች ነው፡፡አብሮኝ የነበረው ሰውና እኔ ለመግባት እናደርግ የነበረውን ትንቅንቅ በመተው ሁለቱን ለማጽናናት እና ምን እንደተፈጠረ ለማወቅ መወትወቱን ተያያዝነው፡፡
ርዕዮት ቤተሰቦቿን እንዳገኘች‹‹ያለሁበት ሁኔታ አስቸጋሪ ነው፣ችግር ውስጥ ነኝ››ትላቸዋለች፡፡በዚህ ወቅት በዙሪያዋ የነበሩ ሴት ፖሊሶች ጋዜጠኛዋ ላይ በመጮህ ‹‹ስለ ራስሽ ብቻ አውሪ››ይሏታል፡፡
‹‹የነገረችን እኮ ስለ ራሷ ነው››የእስከዳር ምላሽ ነበር፡፡በዚህ መሃል በጊዜያዊነት የሴቶች ዞን ሃላፊ የሆነች ፖሊስ ‹‹እናንተ አቅማችሁ ጋዜጣ ላይ ነው ከፈለጋችሁ ሂዱና እንዳንጠይቃት ተከለከልን በሉ፡፡››በማለት በዚህ ቦታ ለመጥቀስ ኢትዮጵያዊ ጨዋነት የሚያቅበንን የስድብ መዓት በስለሺ ፣በርዕዮትና በእህቷ ላይ ታወርዳለች፡፡

ርዕዮት ሁኔታውን መቋቋም ተስኗት ሃላፊዋን ለምን እንዲህ አይነት በደል እንደምትፈጽምባት ለመጠየቅ ስትሞክር እየገፈታተሩ ወደ ውስጥ እንድትገባ በማድረግ እነ ስለሺን ግቢውን እንዲለቁ ያደርጋሉ፡፡
በንጋታው መስከረም 1/2006 ነው፡፡የመንግስት ሃላፊዎችና የሃይማኖት አባቶች የቴሌቭዥኑን መስኮት በአዲስ አመት ቀና መልዕክት አጨናንቀውታል፡፡አዲስ ቀን አዲስ ገጠመኝ እንደሚፈጥር ተስፋ ያደረጉት የርዕዮት ቤተሰቦች ከቃሊቲ አልቀሩም፡፡ነገር ግን የሰሙት ነገር በቀኑ እንጂ በአስተዳደሩ መካከል ለውጥ ወይም ዕድሳት አለመኖሩን ነው፡፡ለካ የአዲስ አመት በጎ መልእክት የሚያስተላልፉልን መሪዎቻችን ያሉት‹‹በድሮው ቀን ነው፡፡››
ርዕዮትን እንዲጠይቁ የተፈቀደላቸው ‹‹እናቷ፣አባቷና የነፍስ አባቷ ብቻ ናቸው››እነ ስለሺ ከቃሊቲ ሃላፊዎች ዛሬ ያደመጡት መንፈስ ሰባሪ ቃል ነው፡፡የህግ ባለሞያው አቶ አለሙ ጌቤቦ ድርጊቱ ህገ መንግስታዊ ጥሰት እንደሆነ በመግለጽ ቃሊቲ ደርሰው ልጃቸውን ሳይጠይቁ ተመልሰዋል፡፡ወላጅ እናቷ ያመጡትን ምግብ ለማስገባት ቢሞክሩም ርዕዮት በቃሊቲ የሴቶች ዞን ጊዜያዊ ሃላፊ እየደረሰባት የሚገኘውን ህገ ወጥ ድርጊት ለመቃወም የርሃብ አድማ በመጀመሯ እናት ያመጡትን ምግብ የሚቀበላቸው አላገኙም፡፡
ወዳጄ ስንቶቻችን ነን አዲሱ ዓመት በጾም ቀን ዋለ ብለን የተከፋን?ይህው እንግዲህ በዓሉን ርዕዮት በርሃብ አሳልፋዋለች፡፡
የርዕዮት የርሃብ አድማ መልእክቱ ግልጽ ነው፡፡አቅም ያላት በራሷ ላይ በመሆኑ ራሷን በመቅጣት ህገ ወጦችን እምቢ አለቻቸው በዚህ ሰላማዊውን ታጋይ ማህተመ ጋንዲን መሰለችው፡፡ሰዎቹ እየበሉ በርሷ ላይ የሚፈጽሙት በደል እየተራበች በምታስተላልፈው መልእክት የህሊና ርሃብተኞች መሆናቸውን ይነግራቸዋል፡፡
ከቃሊቲ ውጪ ያለንም ምግብ ወደ አፋችን ባስጠጋን ቁጥር ርዕዮት የቃሊቲ አጥር ሳይበግራት ትመጣብናለች፡፡በምግብ ብቻ በማይኖርባት አለም በምግብ ብቻ ለመኖር ለምናደርገው ከንቱ ሩጫም ርሃቧ ትልቅ ደወል ይሆንብናል፡፡

መስከረም ሁለት – ኢትዮጵያ ትቅደም! –ከተመስገን ደሳለኝ (ጋዜጠኛ)

$
0
0


‹‹እንኳን ከ፲፱፻፷፮ ዓ.ም ወደ ፲፱፻፷፯ ዓ.ም አዲሱ ዓመት ከሰላማዊ የአስተዳደር ለውጥ ጋር በደህና ያሸጋገራችሁ፤ ይህ ያለምንም ደም መፋሰስ የተጀመረው ‹ኢትዮጵያ ትቅደም› ዓላማ መሰላል ሆኖ የመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ኑሮ የሚቀራረብበት፣ አንድነታችንን የሚያጠናክርበት ዘመን እንዲሆን እንመኛለን፡፡ ‹ኢትዮጵያ ትቅደም!› መጪው ዘመን የሰላም የለውጥ ጊዜ ይሁንልን፡፡›› (አዲስ ዘመን ጋዜጣ መስከረም 3 ቀን 1967 ዓ.ም)

እነሆም ይህ ክስተት ከሶስት ቀን በኋላ ሰላሳ ዘጠነኛ ዓመቱን ደፈነ። በዚህ የመፅሄታችን ልዩ ዕትምም ታሪኩን መዘከርና ባለውለታዎቹን ማመስገን ወደድኩ፡፡

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

ቅድመ-አብዮት

በ1953 ዓ.ም ‹የነዋይ ልጆች› ያስተባበሩት መፈንቅለ መንግስት በርካታ መኳንንትንና ሹማምንትን የህይወት መስዋዕትነት አስከፍሎ ቢከሽፍም፣ በጥንታዊቷ ‹የባላባቶች› ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ የነፃነት ጎህ መቅደዱ አይቀሬ መሆኑን አመላክቶ ነበር ያለፈው፡፡ የአቤ ጉበኛ ‹‹አልወለድም›› እና የጄነራል አብይ አበበ ‹‹አውቀን እንታረም›› መፅሀፍት፤ አምባሳደር ብርሀኑ ድንቄ ለንጉሱ የላኩት ረጅም ደብዳቤ እና ሀዲስ አለማየሁ ‹‹የገለፅኩበት ቋንቋ ትንሽ ወፈር ያሉ መሆናቸው ይሰማኛል›› በሚል ሀረግ በመፈንቅለ መንግስቱ ማግስት ለአፄው ያቀረቡት ማስታወሻ በገደምዳሜ ይህንኑ አመላካች እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ ጊዜው ደርሶ ትንግርቱ ሲፈፀም፣ ታሪክ የተጎረደውንም መቀጥል የሚችልበት አጋጣሚ እንዳለ ያሳየበት ክስተትም ነበር፤ ይኸውም ተማሪዎቹ የለውጥ ንቅናቄውን ፈትለው የገመዱት በመፈንቅለ መንግስቱ ሙከራ የባለስልጣናት ደም የፈሰሰበት ‹ልዑል መኮንን ቤተ-መንግስት›ን ገደ-ቢስ (ክፉ ምልኪ) አድርገው የወሰዱት ቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ ሠፈራቸውን ወደ ‹ኢዮቤልዩ ቤተ-መንግስት› ቀይረው፣ ‹ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ› (የዛሬው አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ) ይሆን ዘንድ በፈቀዱት ያው ግቢ መሆኑ ነው፡፡

በእነጄነራል መንግስቱ ነዋይ ጉልበቱ የተፈተነው የዘውድ አስተዳደር፣ ከአስራ አራት ዓመት የተማሪዎች ጠንካራ ትግል በኋላ በወርሀ የካቲት (1966 ዓ.ም) የዘመኑ ዘጋቢዎች ‹ማምለጡ አዳጋች ነው› ያሉት ድንገቴ አጣብቂኝ ተፈጠረበት፤ ነገሩ እንዲህ ነው፡- በአረቦችና እስራኤል ጦርነት የተነሳ የስዊዝ ካናል መዘጋት ባመጣው የአለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ ንረት የካቲት 6 በነዳጅ ላይ የአስር ሳንቲም ማሻሻያ መደረጉን ተከትሎ፣ የካቲት 11 የታክሲ ሹፌሮች ጭማሪውን፣ መምህራን አዲሱን ‹ሴክተር ሪቪው› የትምህርት ፖሊሲ በመቃወም የስራ ማቆም አድማ መቱ፤ የካቲት 13 ተማሪዎችና የመንግስት ሰራተኞች ለተቃውሞ ሰልፍ አደባባይ ወጡ፤ ሁኔታዎች መባባሳቸውን ያስተዋለው የአፄው መንግስት የካቲት 16 ነዳጅ ላይ የጨመራትን አስር ሳንቲም ማንሳቱን በይፋ ቢያሳውቅም፣ ተቃውሞውን ሊያስታግስለት አልቻለም፤ በዚሁ ዕለት በተለያዩ ካምፖች የሠፈሩ የሠራዊቱ አባላት የንቅናቄው ደጋፊ መሆናቸውን ከመግለፅ ባሻገር ‹‹አቆርቋዥ›› ሲሉ የወነጀሏቸውን የጦር አዛዦች በቁጥጥር ስር አዋሉ፤ ንጉሱም የካቲት 19 መፍትሄ ይሆናል በሚል ስልት የጠቅላይ ሚንስትር አክሊሉ ሀብተወልድን ካብኔ አፍርሰው በእንዳልካቸው መኮንን የሚመራ አዲስ ካቢኔ አቋቋሙ፤ ይሁንና የንቅናቄው አራማጆች ‹ጉልቻ ቢለዋወጥ ወጥ አያጣፍጥም!› ብለው ትግሉን አቀጣጠሉ፡፡ ሠራዊቱም ከአዛዦቹ በተጨማሪ የሲቪል ባለስልጣናትን ማሰሩን ሳያቋርጥ ከባድ ክረምት የተሸከመው ወርሀ ሰኔ ደረሰ፡፡

አፄው ለመጀመሪያ ጊዜ ለህዝብ ጥያቄ ተንበርክከው ሹም-ሽር ማድረጋቸው የአብዮቱን ወደ መጨረሻው ምዕራፍ መዳረስ በማብሰሩ፣ የኢትዮጵያ ወታደር በዩኒቨርስቲና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ደጃፎች የሚደረጉ የተቃውሞ ሰልፎችን ለመበተን ይወድረው የነበረውን አፈ-ሙዝ ወደ ዙፋኑና ባለሟሎቻቸው አዞረው፡፡ ሰኔ 21 ቀን 1966 ዓ.ም ከጦር ሠራዊት፣ ከክቡር ዘበኛ፣ ከብሄራዊ ጦር፣ ከፖሊስ አባላት የተወከሉ መለዮ ለባሾች ‹የጦር ኃይሎች፣ የፖሊስ ሠራዊትና የብሔራዊ ጦር አስተባባሪ› በሚል ስያሜ (ሐምሌ 1/1967 ዓ.ም ‹ደርግ› በሚል መቀየሩን ልብ ይሏል) በአራተኛ ክፍለ ጦር ግቢ ተሰባስበው ሲያበቁ ኮሚቴ አቋቋሙ፡፡ ዕለቱንም ሻለቃ መንግስቱ ኃ/ማርያም ሊቀ-መንበር፣ ሻለቃ አጥናፉ አባተ ምክትል ተደርገው ተመረጡ፡፡ በወቅቱ የሆነውንም ገስጥ ተጫኔ (ዘነበ ፈለቀ) ‹‹ነበር›› በሚል ርዕስ ባሳተመው ቅፅ አንድ መፅሀፉ እንዲህ ገልፆታል፡-

‹‹ሰኔ 20 ቀን 1966 ዓ.ም ሻለቃ አድማሴ ዘለቀ፣ ንቡረ ዕድ ድሜጥሮስና አቶ አበበ ወንድሜነህ የተባሉ የፓርላማ አባላት ወደ አራተኛ ክፍለ ጦር ጠቅላይ መምሪያ ሄደው በምድር ጦር መሐንዲስ ትምህርት ቤት (ጎፋ ሠፈር) ውስጥ በጥበቃ ሥር የሚገኙ ባለስልጣኖች እንዲለቀቁ በአማላጅነት ጠየቁ፡፡ ጦሩ በዚህ ድርጊታቸው በቁጣ ገንፍሎ እነርሱንም በቁጥጥር ሥር አዋላቸው፡፡ ይህ ቁጣው ሻለቃ መንግስቱ ኃ/ማርያም ወልዴ የሚባሉ፣ አጭር፣ ኮሳሳና ቁጡ ሰው ወደ ሥልጣን ያመጣል ብሎ ያሰበ አልነበረም፡፡›› (ገፅ 8)

የኢትዮጵያ ወታደር በዚህ መልኩ አብዮቱን መቀላቀሉ ስህተት ነው ብዬ አላስብም፡፡ በየትኛውም ሀገር ለስኬት የበቃ የአብዮት ታሪክ ንባብ እንደሚያትተው ህዝብ የመንግስት ለውጥ ፈልጎ አደባባይ በመውጣት ጫና ፈጥሮ ስርዓቱን ያዳክማል እንጂ፣ የቤተ-መንግስት አጥር ሰብሮ ወንበር አይይዝም፤ በቅርቡ በቱኒዚያና በግብፅ (ሆስኒ ሙባረክን ለማስወገድ) የታየውም የሠራዊቱ ጣልቃ-ገብ መግፍኤ ይኸው ነው፡፡ ሻለቃ መንግስቱና ጓደኞቹም ያደረጉት ተመሳሳዩን ነው፡፡ በዚህ አይነት የህዝብ አመፅ ወቅት ‹በእምቢተኝነት› ሥልጣን የሙጢኝ ያለ መሪን ለሕዝብ ፍላጎት የማስገዛትና ሀገር የማረጋጋት ኃይል ያለው በሠራዊቱ መዳፍ ብቻ እንደሆነ መረሳት የለበትም፡፡ በተቀረ ደርጎች በስልጣን ነጠቃም ሆነ በጭፍጨፋ የሚከሰሱት ከለውጡ በኋላ ያ ሁሉ መስዋዕት የተከፈለበትን የ‹‹ህዝባዊ መንግስት›› ጥያቄ አሳክተው ወደ ጦር ሠፈራቸው ከመመለስ ይልቅ በጥያቄው ላይ አምፀው በፈፀሙት ውንብድና ነው፡፡ በዚህ ፅሁፍ ‹‹መስከረም ሁለት››ን ለመዘከር የተገደድኩበት ምክንያት ብዬ የምጠቅሳቸው ሀገራዊ ጉዳዮች በሙሉ ለፍሬ በማብቃቱ የአንበሳውን ድርሻ የሚወስደው ደርጉ ሳይሆን የተማሪው ትግል መሆኑን ግን በቅድሚያ አስታውሳለሁ፡፡

ደርግ

መንግስቱ ኃ/ማርያም የደርጉ ሊቀ-መንበር ሆኖ ከተመረጠ በኋላ ግድግዳው ላይ በተሰቀለው ሰሌዳ ‹‹ኢትዮጵያ ትቅደም›› የሚል መፈክር መፃፉ ዛሬም ደርጉንና ተቺዎቹን እንዳወዛገበ ነው፡፡ የውዝግቡ መንስኤ መንግስቱ የፃፈውን ሀረግ ተከትሎ የደርግ አባላት ‹‹ሀገሪቱን የምንመራው ‹ኢትዮጵያ ትቅደም!› በሚል የፖለቲካ ፍልስፍና ነው›› በማለታቸውና ከዚህ ቀደም እንዲህ አይነት ፍልስፍና ባለመኖሩ ‹ከየት አመጣችሁት?›፣ ‹ምን ማለትስ ነው?› ለሚሉ ጥያቄዎች መልስ መስጠት አለመቻል ነበር፡፡ መንግስቱ ኃ/ማርያም አለመግባባቱ የተፈጠረበትን አጋጣሚ ‹‹ትግላችን›› በሚል ርዕስ ባሳተመው መጽሀፉ እንዲህ ሲል ገልፆታል፡-

‹‹በተፈጥሮው እጅግ ችኩል የሆነው የማስታወቂያ ኮሚቴ ሊቀ-መንበር …ደርግ በተቋቋመበት ቀን የደርጉ አባላት የእኔን አስተዋጽኦ በጠየቁኝ መሰረት ያሉኝን ሃሳቦች ሳቀርብ የመጀመሪያው የደርጉ የፖለቲካ ወይም የትግል መፈክርን ‹ኢትዮጵያ ትቅደም› እንዲሆን ማሳሰቤ ይታወሳል፡፡ ጉባኤው መፈክሩን በይሁንታ እንዳፀደቀው ሻለቃ አስራት ከስብሰባው አዳራሽ ሹልክ ብሎ በመውጣት የሀገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞችን በመሰብሰብ ‹የደርጉ የፖለቲካ ፍልስፍና ኢትዮጵያ ትቅደም ይባላል› በማለቱ እስከ ዛሬ በተራማጅ ምሁራን ዘንድ ሲያስተቸን ይኖራል፡፡›› (ገፅ 153-154)

ይሁንና በወቅቱ የነበሩ የመንግስት ሚዲያዎች በ‹ኢትዮጵያ ትቅደም› ዓላማ መሰረት እያሉ የሚዘረዝሯቸው የፖለቲካ ሃሳቦች እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ ደርጉ ወደ ጅምላ ጭፍጨፋው ሲንደረደር ያስተላለፈው ማስጠንቀቂያ ‹‹የኢትዮጵያ ትቅደምን ዓላማን በመቃወም፣ የሥራ ማቆም አድማ፣ የተቃውሞ ሰልፍ የሚያደርግ… ጥብቅ እርምጃ ይወሰድበታል!›› የሚል እንደነበረም ይታወሳል፡፡

የሆነ ሆኖ ይህ ዕለት (ይህ ፅሁፍ) አብዮቱ ጎርምቶ የሠራዊቱን ጣልቃ መግባት ባሻበት በዛች ቀውጢ ወቅት ቆራጦቹ ሻለቃ መንግስቱና ጓዶቹ የነበራቸውን አበርክቶ ማመስገንና መዘከር በመሆኑ ወቀሳውን እዚሁ ገተን (ሁነቱን ‹ዝግምተኛ መፈንቅለ መንግስት› ነበር የሚለውን ሙግት ሳንዘነጋ) ወደዚያው አንለፍ፡፡

ደርግ፣ የጦር ካምፑን ወደ አብዮት ካምፕ ቀይሮ በወርቃማ ቀለም ያስከተበውን ታሪክ በሁለት ከፍለን ከመደብነው፡- የመጀመሪያው የዘውድ ስርዓቱን ለመለወጥ ከሰኔ 20/1966 ዓ.ም አንስቶ፣ መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም ድረስ ባሉት ሰባ ጭንቅ ያማጡ ቀናት ውስጥ የሚወድቀው ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ከለውጡ በኋላ የተወሰዱ ታላላቅ እርምጃዎችን የሚያካትት ይሆናል፡፡

አብዮቱ-ያችን ሰዓት!

ደርግ በይፋ ከተቋቋመ ከሁለት ቀናት በኋላ የታሪኩ ‹ምዕራፍ አንድ› ደረጃ በደረጃ እንዲህ ይጀምራል፡- ለፖለቲካ እስረኞች ምህረት አደረገ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ አብዮቱን ለመቀልበስ ያቋቋሙትን ‹ብሔራዊ የፀጥታ ኮሚሽን› አፍርሶ፣ በእርሳቸው ትዕዛዝ ‹አመፀኛ› ተብለው የታሰሩ የሠራዊቱ አባላትን በነፃ ለቀቀ፤ ሜ/ጄነራል አማን ሚካኤል አንዶምን በሌፍተናንት ጄነራል ማዕረግ የጦር ኃይሎች ኤታማዦር አድርጎ አስሾመ፤ ባለስልጣናቱ ለግል መጠቀሚያ የወሰዱትን ሁሉንም አይነት የመንግስት ንብረት እንዲመልሱ በብዙሀን መገናኛ አዘዘ፤ የጠ/ሚኒስትር እንዳልካቸው መኮንን ካቤኔን አፍርሶ፣ ልጅ ሚካኤል እምሩን ተካ፤ የዙፋን ችሎት፣ የዘውድ ምክር ቤትና የፍርድ አጣሪ ጉባኤን አፈረሰ፤ አፄው የደህንነት፣ የጦርና የሲቪል ባለስልጣኖቻቸውን እና መላ ሀገሪቷን በዘመናዊ መንገድ አዋቅረው የሚሰልሉበትን ‹‹የንጉሰ ነገስት ልዩ ኤታማዦር›› የተሰኘ ተቋም በመከላከያ ሚኒስቴር ስር እንዲጠቃለል ወሰነ፤ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ለደርግ ሳያሳውቁ ገንዘብ እንዳያንቀሳቅሱ ከለከለ፤ በቀዳማዊ ኃ/ስላሴ የግል ይዞታ ስር የነበሩት የብሔራዊ ልማት አክሲዮን፣ የአንበሳ አውቶብስ ድርጅት እና የቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ ፋብሪካን ባለቤትነት ወደ መንግስት አዞረ፤ የመሳፍንትና ባለስልጣናት ልጆች በመንግስት ገንዘብ ወደ ውጭ ሀገር ሄደው መማራቸውን አገደ…

በዚህ መልኩ በዝግታ የተጓዘውን አብዮት የመሩት የደርግ አባላት ለመጨረሻው ውሳኔ ጳጉሜ 4/1966 ዓ.ም ተሰበሰቡ፤ ሙሉውን ቀንም በአጀንዳው ላይ ሲከራከሩና ሲመክሩ ውለው፣ ጀንበር ስታዘቀዝቅ በለመዱት አሰራር ወደ ድምፅ መስጠቱ አመሩ፣ በውጤቱም ከ1909 ዓ.ም እስከ 1923 ዓ.ም በ‹አልጋ ወራሽ›ነት፤ ከ1923 ዓ.ም እስከ እዚህች ዕለት ደግሞ በ‹ንጉሰ- ነገስት› ማዕረግ በሀገሪቱ ላይ የፈጣሪን ያህል የተከበሩትን ቀዳማዊ አፄ ኃ/ስላሴ ከዙፋናቸው እንዲወርዱ በአብላጫ ድምፅ ወሰኑ፡፡

ከውሳኔው በኋላ እንቅፋት እንዳይኖርና ህዝቡን በስነ-ልቦና ለማዘጋጀት በማሰብ የተንዛዛውን የንጉሱን 80ኛ ዓመት የልደት በዓል አከባበርን፣ በወሎና በትግራይ ከተከሰተው አስከፊ ረሀብ ጋር እያነፃፀረ የሚተርክ አሰቃቂ ፊልም በቴሌቪዥን አስተላለፉ፤ ፊልሙ እንደተጠናቀቀም ቀዝቃዛው የክረምት ምሽት ያቆረፈዳቸው የአዲስ አበባ ጎዳናዎች ስሜት በፈነቀላቸው ነዋሪዎች ተቃውሞ ተጥለቀለቁ፤ በማግስቱም (በአዲሱ ዓመት) ይኸው ትዕይንት ቀጥሎ ዋለ፤ በዕለቱ የሆነውን ኮሎኔል መንግስቱ ኃ/ማርያም ከላይ በጠቀስኩት መፅሀፉ እንዲህ ገልጾታል፡-

‹‹መስከረም 1 ቀን 1967 ዓ.ም በጉልታዊ ሥርዓተ-ማህበር የሚመራው ፈላጭ ቆራጭ፣ መለኮታዊ የዘውድ አገዛዝ ተገረሰሰ›› (ገፅ 492)

መስከረም 3/1967 ዓ.ም የታተመው ‹‹አዲስ ዘመን›› ጋዜጣ ደግሞ ‹‹ትናንት ጠዋት›› በሚል ርዕስ ባስነበበው ዘገባ፡-

‹‹ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ከሥልጣን መውረዳቸው በጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር መታወጁን የአዲስ አበባ ኗሪ ትናንት ጧት በአንድ ሰዓት ተኩል ላይ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ሲሰማ፣ ምንም አይነት መደናገጥና መሸበር ሳያደርስ እንደተለመደው ወደ ሥራ መስኮቹ ሲሰማራ ታይቷል፤ …የለውጡን ሁኔታ ለመከታተል በብዛት ወደ አደባባዮች እና ዋና መንገዶች የወጣው ሕዝብ ወደ ሥራውና ቤቱ እንዲሄድ ወታደሮች በኩምቢቮክስ ባገን መኪና ውስጥ ሆነው በድምፅ ማጉያ ‹ስለተባበራችሁን ከልብ እናመሰግናለን፤ ሆኖም የእናንተ እዚህ መሰብሰብ አስፈላጊ መስሎ ስላላገኘነው ወደየሥራችሁ እንድትሄዱ እንጠይቃለን› በማለት እየተዘዋወረ አሳስቧል፡፡›› ሲል ነበር በሕዝቡ ዘንድ የነበረውን ድባብ የገለፀው፡፡

እነሆም እዚህ ድረስ ለሆነው ሁሉ ‹ቪቫ አብዮታዊያን፣ ቪቫ ደርግ፣ ቪቫ መንጌ!› ማለትን ወደድኩ!

የአብዮቱ-ማግስት

ንጉሱ ከዙፋናቸው ከተነሱ በኋላ የታሪኩ ‹ምዕራፍ ሁለት› እንዲህ ይቀጥላል፡- የመሀይምነት ጨለማ አስጥሞት ለነበረው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ማንበብና መፃፍ የሚችልበትን መሰረት ለመጣል ‹‹የዕድገት በህብረት የዕውቀትና የሥራ ዘመቻ››ን አውጇል፤ ኃይማኖትና መንግስት የተለያዩ መሆናቸውን እና ‹ሁሉም ቤተ-እምነት ያለአድልኦ በዕኩልነት ይታያሉ› የሚል ደንብ አውጥቷል፤ በስርዓቱ ሹማምንትና ባላባት ቁጥጥር ስር የነበረውን የገጠር መሬት፣ እንዲሁም የከተማ ቦታና ትርፍ ቤቶች የመንግስት መሆናቸውን ደንግጓል፡፡ …እነዚህ ሁሉ ተንሻፈው የተመለሱ ቢሆኑም ተማሪው ያነሳቸው ከነበሩ ጥያቄዎች ውስጥ መመደባቸውን ግን መካድ አይቻልም፡፡

በአናቱም በወቅቱ ከኢትዮጵያ በተሻለ ጥራት ሠራዊቷን ያደራጀችው ሶማሊያ ‹በእኔነት› ዕብሪት በሐረርጌ፣ ባሌና ሲዳሞ የፈፀመችውን የኃይል ወረራ ለመመከት ኮሎኔል መንግስቱ ኃ/ማርያምና ጓዶቻቸው ኃላፊነታቸውን በሚገባ ተወጥተዋል፤ በሶቭየት ህብረት፣ በኩባና የመን አደራዳሪነት የተሞከረው ሽምግልና በሶማሊያ እምቢ-ተኝነት ከከሸፈ በኋላ፣ ከምስራቁ ካምፕ የጦር መሳሪያ እና ፖለቲካዊ ድጋፍ ለማግኘት ያደረጉት ዲፕሎማሲያዊ ጥረት የሚያስመሰግን ነው፤ የሶማሊያው መሪ ዚያድ ባሬ በወታደሩ ጥንካሬ ተማምኖ በሰላም ሂደቱ ላይ ለመሳተፍ ከመለገሙ ጋ ተያይዞ መንግስቱ ኃ/ማርያም በየመን-ሰንዓ በተደረገ ድርድር ላይ የተፈተነበትን ገጠመኝ ከራሱ መፅሀፍ ልጥቀስላችሁ፡-

‹‹ጓድ ፊደል ካስትሮ ከምክትል ፕሬዘዳንታቸው ጋር፣ ጓድ አብዱል ፈታህ ከፕሬዘዳንቱ ጋር አራት ሆነው መጡ፤ ከስብሰባው በፊት ወደ እኛ የመጡበት ምክንያት ‹ሶማሊያዎቹ ይህ ውይይት እንዳይሳካ የማይፈጥሩት ችግር ስለሌለና ምናልባትም የእናንተን ትዕግስት የሚፈታተን የብልግናና የዘለፋ ቃላቶችን ከመሰንዘር ስለማይመለሱ በእናንተ በኩል እስከ መጨረሻው ትዕግስታችሁን እንጠይቃለን› አሉን፡፡ በእኛ በኩል ምንም ችግር እንደማንፈጥር በማረጋገጥና በማበረታታት መልሰን ሸኘናቸው፡፡ …የሶማሊያው መሪ ማንንም ሳያነጋግር ወይም ሳይጨብጥ አዳራሹ ማዕከል ሜዳ ላይ ሁለት እጁን ሱሪ ኪሱ ከቶ ዘለግ ባለ ድምፅ ‹ሁለት ስቱፒድ የሆንን ሕዝቦች አስቸገርናችሁ አይደለም?› በማለት ተናግሮ ወደ መቀመጫው ሲያመራ ከአነጋገሩ በላይ ጠቅላላ ሁኔታው፣ ኩራቱና ትእቢቱ ደሜን ስላፈላው፣ ለትዕግስቴ ዳርቻ አይኖረውም ብዬ ለራሴ ቃል የገባሁት ሰውዬ ‹የራስህን ስቱፒድነት ተናገር እኛ ግን አንተን ወይም እናንተን አይደለንም› ስለው አስተናጋጆቹ ተደናገጡ፡፡ ዚያድ ባሬ ያልኩትን ያልሰማኝ ይመስል ‹ምንድነው ያለው?› እያለ ሰዎቹን ሲጠይቅ አስተውለው ነበር፡፡ ›› (ገፅ 354)

የሰላም ድርድሩ ባለመሳካቱም ኮለኔሉና ጓዶቹ ሕዝባቸውን ከዳር ዳር ቀስቅሰውና አስታጥቀው፣ ከሶሻሊስት ሀገራት ጋር በመተባበር፡-

‹ማን ይፈራል ሞት

ማን ይፈራል

ለእናት ሀገር ሲባል!›ን እየዘመሩ ወራሪውን የሶማሊያ ወታደር የኢትዮጵያ ምድር ግዛቱ ሳይሆን፣ መቀበሪያው ማድረጋቸውን ታሪክ መዝግቦታል፡፡

ዛሬ ስለመንግስቱ ኃ/ማርያም እና ጓዶቹ አምባገነንት፣ ጨፍጫፊነት፣ ጦርነት ናፋቂነት… ካልሆነ በቀር ሀገራዊ አስተዋፅኦዋቸውን መናገሩ ያስቀስፋል፤ ምክንያቱም እነመንግስቱ ተራቸው ደርሶ ተሸንፈው ከስልጣናቸው ተባረዋል፤ ታሪክ ደግሞ ምንጊዜም ከአሸናፊ ጋር ትወግናለች፡፡

የሆነው ሆኖ መንግስቱ ኃ/ማርያም እንደ መለስ ዜናዊ ስልጣን ላይ እያለ ህይወቱ ቢያልፍ ኖሮ እነጓድ ለገሰ አስፋው ምን የሚያደርጉ ይመስላችኋል? …እልፍ አዕላፍት ‹ፓርክ› በስሙ ይሰይማሉ፤ በተማረበት ‹ሆለታ ገነት የጦር አካዳሚ› ግቢ ውስጥ በ20 ሚሊዮን ብር የምርምር ተቋም ይገነባሉ፤ ለሙት አመቱ መታሰቢያ በየዓመቱ ችግኝ መተከሉ ስለማይቀርም በርካታ ‹አማዞኖች› በስሙ ይኖሩታል፤ ‹ራዕዩ› የሚቀጥልበት ፋውንዴሽንም ይቋቋምለታል… ይህ ነው የጉልበተኞች የ‹ታሪክ› ትርጓሜ (አረዳድ)፤ አስገራሚው ጉዳይ ይህ ብቻ አይደለም፤ ሁሉም አምባገነን ተመሳሳይ መሆናቸው ነው፤ ራሱ መንግስቱ ኃ/ማርያም በዘመኑ የጃንሆይን ሀገራዊ አስተዋፅኦ ሊያወድስ ቀርቶ፣ ስማቸውንም እንኳ መስማት አይፈልግም ነበር፤ ተራው ደርሶ በተሸነፈ ጊዜም ያጨደው የዘራውን ይመስለኛል፤ ግና! ይህንን ባህል (ክፉ ልማድ) መቀየር አለብን፤ የአሜሪካኖቹ ‹የምስጋና ቀን› ምክንያትና ዓላማንም እንዲህ በሆንበት ክፉ ጊዜ በልባችን ብናስበው ምንኛ መልካም ይሆናል፡፡

በመጨረሻም በዚህ ፅሁፍ ለጠቀስኳቸው ሁነቶች ብቻና ብቻ ‹ቪቫ ደርግ፣ ቪቫ መንግስቱ› እላለሁ! ለዜጎች ጥቅም ዛሬም፣ ነገም ኢትዮጵያ ትቅደም!

መልካም አዲስ ዓመት!!


ገድሎ ለቅሶ የሚደርሰው ስርዐት ሞቶ ቀብር የምንወጣለት አዲስ አመት ይሁልን

$
0
0

Melak addis  ametመቸም የዘመን ዑደት ማለት አሮጌው አልፎ አዲሱ የሚተካበት፣ ዘር አፈር ቅሞ ወሀ ጠጥቶ በቅሎና አብቦ የሚያሸትበት መስከረም ማለትም አይደል? አዎ አዲስ ዘመናችን ምድሪቱ ጭጋግን ለብሳ፣ አራዊቱ ያጠራቀሙትን ስብ እያቀለጡ የሚኖሩበት፣ አእዋፍ ስደት የሚጀምሩበትና የሰው ልጅ አንደ በቆሎ በልብስ የሚጠቀለልበት የበረዶ ወቅት ባለመሆኑ እርግጥም አዲስ አመት ነው። በምንም መስፈርት በማንም መለኪያ ዘመን አቆጣጠራችን ለኛ ተገቢም ትክክልም ነው። አዲስ አመት ማለት ለኛ ለኢትዮጵያውያን ተስፋ ማለትም ነው።

ታድያ ተስፋ ላይ ለቅሶና ቀብር እንዴት ርዕስ ሆነ ማለታችሁ አይቀርም። አዎ ሸፍጥ ሞቶ ሀቅ ቀብር ቢወጣና ለእውነት ኖረን ስለ ዕውነት ብናልፍ፤ በዚህ የአመታት ቅብብሎሽም እንደ አደይ አበባ ሁሉ የተስፋ ብስራት ቢያሸትልን ምን ይለናል? የሚል መንደርደርያ ነው የዚህን አይነት ርዕስ ያስመረጠኝ። አዎ እነዚህ አዲሶቹ ገድሎ ቀብር ወጪዎች ‘ተረትና ማቅራራት’ የአማራ ነው እንዳለው አስተኳሻቸው ገድለው አያቅራሩም። በፊት በረሃ እያሉ እርግጥ ነው በአንድ ጥይት 10 ሰው መደዳውን እንደሚገድሉ ተራራው እንደሚንቀጠቀጥላቸው ነግረውን ነበር። ‘ፍሬንድሊ ፋየር’ የምትለውን ብልጥ ቃል መጠቀም የጀመሩት ግን ያኔ ‘ፍሬንዶቻቸውን’ እያጋደሙ ሲያርዱ ነበር። እድሜ ለገብረመድህን አርአያ አስገድሎ አሸርጦ ማልቀስን በሜጋ የፊልም ቅንብር ሀውዜን ላይ መተወናቸውን ነግሮናል። አተረፉበት ነው የሚባለው! ከበሩበት እንጂ ሸገር ይዞአቸው የገባው ሞት የሀውዜኑም አይደል? ከዚያ በሁዋላ ያፈነገጠውን ሁሉ እርድ ያደርጉና ጉድ ተሰራን? ገዳዩን ለማግኘት የማንፈነቅለው ድንጋይ የለም ብለው አደባባይ ይምላሉ።

በሁዋላ ግን የፈነቀሉትን ድንጋይ መቃብሩ ላይ ቆልለው ወሬውንም ያጠፉታል። አይንአውጣ ስለሆኑ ለቅሶ ሁሉ ይደርሳሉ። ስፍስፍ ብሎ የሚያለቅስና ሁዋላ አደጋ የሚያመጣ የሚመስላቸውን መንጥረው ለማባረር የሚጠቀሙበትም ይመስላል። ይህ ወንጀላቸው ወደ ህግ ባይመጣም እንኳ ሕሊናን መበጥበጡና ነገም ለኔ አይመለሱም የሚለው ፍርሀት መኖሩን ከሰዎቹ ፊት ማንበብ ይቻላል። ይህ ጥርጣሬና ፍርሃት ፊታቸውን አበላሽቶታል።

የሆነ እርኩስ መንፈስ የተጠናወተው የሚመስል ቅብዝብዝ ዐይኖች አላቸው። የተሸበረ ፊ የሌለው ባለስልጣን እኮ የለም። አዎ የሰው ደም ያቅበዘብዛል። እነዚህ በጎደለ የተተኩ ከበረሀኞቹ በላይ በረሀኛ የሚመስሉትም ቶሎ የደለበ ግን መታረጃውን ያየ ሰንጋ መስለዋል የሚሉም አሉ። አሁን በቀደም ሼክ ኑሩን መስዋዕት ሲያደርጓቸው ገድሎ አልቃሾቹ መስጊድ እንደጧፍ ሲነድ ቤተክርስትያን እንደ ደመራ ቦግ ሲል ሕዝቡ ሲተራረድና እነሱ ገላጋይ ሆነው ሲወጡ የሚያሳይ ባለቀለም ሕልም አይተው ነበር። ሕዝቡ ግን አረ ቀልዳችሁን አቁሙ ብለው ‘የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ’ የሚል የአማራ ተረት ተረተባቸው ሲባልም ሰምተናል። አዎና አርባ አመት ሙሉ ገድሎ ማልቀስ እንዴት ይቻላል? ማነው ስሙ አንድ አስለቃሽ ጋዜጠኛ ወደ ወሎ ሄዶ የ’አይዶል ሾው’ ቢሆን “ለዛሬው አልተሳካልህም” የሚያስብል ሳይጀመር ያለቀ ዘገባ አቅርቦ ነበር። ከዚህ የበለጠ ጭካኔ መቸም የለም።

ለቅሶ ላይ መፈክር ሲያሰሙ እንዲውሉ አደረጋቸው። ውሸታቸው ወንዝ የመሻገር አቅም ስለሌለው ውሸቱን በውሸት ለመሸፈን አሁን መዘዙ ለሼኩም ልጅ አልቀረለት መታሰርና መጋዝ ውስጥ ወስጡን ሌላ ሞት መደገስ ሆነ። የሰለቸንም ይኸው ነው! ዘዴውም ጃጀ እንደ ተሰነጣጠቀ ሽክላ በድምጽ ሲፈርስም አየነው። አሁን አስተኳሹ ብቻ ሳይሆን ስርዐቱም ሞቱን በጸጋ ሊቀበል ይገባዋል። ብዙ የለቅሶን ወሬ ወደ የመልካም ምኞት መግለጫ እንቀይረውና በሚቀጥለው አመት ገድሎን ለቅሶ የሚወጣው ጎጠኛና ወሮበላ ስርዐት ሞቶ ቀብር የምንወጣለት ይሁን ብለን እንመራረቅ። እንዲህ እያልን ምክርም እንምከር “ከነሱ ጋር በልቶ በሰላም ተኝቶ ማደር የለምና በቁልቋል የተመሰልክ ተላላ ሆይ ይህንን አጋም ተጠግተህ እድሜ ልክህን አታልቅስ።” ብለን። የፍቅር አደይ አበባ የተነጠፈባት፣ የተስፋ ቀስተ ደመና የተዘረጋባት፤ ፍትህ፣ ነፃነትና እኩልነት መለያዋ የሆነች ውብ ኢትዮጵያ የመልካም አዲስ አመት ምኞታችን ትሁንልን እውነትም እናድርጋት።
ዳኛቸው ቢያድግልኝ
biyadegelgne@hotmail.com

የአርቲስት ሻምበል በላይነህ አገራዊ ስራዎች አርአያነት –“ወጣቱ አንበሳ ላገርህ ተነሳ…” (ከሉሉ ከበደ)

$
0
0

shambel belayeneh
ሉሉ ከበደ (ጋዜጠኛ)

ውድ ኢትዮጵያን ወገኖቼ እንኳን ለአዲሱ አመት አደረሳችሁ። እዲሱ አመት ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ታላቅ ብስራት ይዞ የሚመጣ ይሁን። ያለምንም ደም መፋሰስ ይህ ዘረኛ የወያኔ ገዢ ቡድን መቃብር ገብቶ፤ ዘረኝነት፤ ጎጠኝነትና በታኝነት ከምድራችን ጠፍቶ፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ተፋቅሮ ተከባብሮ፤ ሲያጠፉ የሚቀጣቸውን የሚሽራቸውን፤ ሲያለሙ የሚሾማችውን የሚሸልማቸውን መሪዎች በድምጹ መርጦ፤ የሚኖርበት፤ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ከዘር ማንነቱ በፊት በኢትዮጵያ ሲምል ሲገዘት የምናይበት፤ ዜጎች ሁሉ ለሀገሬ፤….. ለወገኔ.. እያሉ ሲተጉ፤ ለጋራ እድገትና ብልጽግና ሲጓጉ….አንተ ትብስ አንቺ ትብሽ እያሉ አንዳቸው ላንዳቸው ሲሞቱ የምናይበት የተአምር ዘመን ይሁንልን,….ዘረኞች ለአንዴና ለመጨረሻ የሚጠፉበት ዘመን ይሁንልን….2006. አሜን!
አርቲስቶች የተሰጥኦና የህዝብ ሁለንተናዊ ባህልና ወግ፤ እናም የህዝብ ድጋፍና አድናቆት ውጤቶች እንደ መሆናቸው፤ ስራዎቻቸው ሁሉ የህብረተሰብ ህይወት ነጸብራቆች የመሆን ተፈጥሮአዊ ግዴታ አለባቸው። ሰላምና ጦርነት፤ ድልና ሽትንፈት፤ ደስታና ሀዘን፤ ፍቅርና ጥላቻ ምን ጊዜም ከሰው ልጅ ጋር የሚኖሩ ክስተቶች በመሆናቸው፤ ሰውም በጥብበ ስራዎቹ ውስጥ እነዚህን ባህሪያት እያንጸባረቀ፤ ይማማርባቸዋል። ይዝናናባቸዋል። ያስተላልፋቸዋል። ለሚከታተል ትውልድ የታሪክ መንገሪያም ያደርጋቸዋል ።
ጥበብ የአንድ ህብረተሰብ የስልጣኔ፤ የባህል፤ የሳይንስ፤ የፖለቲካ፤ የሁለንተናዊ እድገት ነጸብራቅና ማሳያም ነው። ጭቆናን ለመታገል፤ ፍትህ ርትእ እንዲሰፍን ህዝብን መቀስቀሻና ማስተማሪያ መሳርያም ነው። ትያትር፤ ስነጽሁፍ፤ ሙዚቃ፤ወዘተ…የህዝብን ንቃተ ህሊናና ታሪካዊ ሁለንተናዊ እውቀት እንደሚያጎለብቱ የሚያጠያይቅ ነገር የለውም።
በሀገራችን የወኔ ስራት ከሰፈነ ያልፉት ሀያ ሁለት አመታት ወዲህ ኢትዮጵያውያን አርቲስቶች አድሎን፤ ዘረኛነትን፤ የመብት ረገጣን በመታገል ረገድ ማን ምን አስተዋጾ አበረከተ ብለን የመረመርን እንደሆን፤ የተወሰኑ ጠንካራ አርቲስቶች እንዳሉን ብናውቅም፤ አሰሩትም ፤አንገላቱትም፤ ሰደቡትም አዋረዱት፤ ስለመከረኛው የኢትዮጵያ ህዝብ አለቀሰ አንጎራጎረ፤ መከረ አስተማረ፤ አጽናና እንጂ ለወያኔ ስራት አድሮ የወያኔ ፕሮፓጋንዳ ማይክራፎን አልሆነም። የሚወዳት ሀገሩንም ጥሎ አልሄደም….ማን?… ሀዋርያውን ብላቴና ቴዲ አፍሮን ዙፋኑ ላይ እናስቀምጠዋልን።
አርቲሥቶች ህዝባዊ ሀላፊነት አለባቸው። ይህም ማለት በጥበብ ስራዎቻቸው የሚያገለግሉትን ህብረተሰብ የሞያ ስነምግባርን በጠበቀ መልኩ፤ ማህበራዊ፤ ባህላዊ፤ ኢኮኖሚያዊ፤ ከባቢያዊ ብሎም ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ህጸጾችን እያፈነፈኑ፤ ነቅሰው እያወጡ፤ በብሩሽ በዜማ በግጥም እያዋዙ ማዝናናት፤ ህብረተሰብን ማስተማር፤ ማንቃት፤ የሞራልና የዜግነት ግዴታ ሊሆንባቸውም ይገባል።

አርቲስት በአድናቂዎቹ ልብ ውስጥ የዘራው ፍሬ በአንድ ወይ በሌላ መልኩ ውጤት ማፍራቱ አይቀርም። የህውሀት ካድሬዎች ፖለቲካ አስተምረው፤ አንቅተው፤ ካሸፈቱት የትግራይ ወጣት፤ በዘፈን በጭፈራና በቀረርቶ የሸፈተው ሳይበለጥ አይቀርም።
ተወዳጅ አርቲስቶች ከአንድ ጠንካራ ፖለቲከኛ የበለጠ ድምጣቸው በአድናዊዎቻቸው ዘንድ ይሰማል።
ክቡር ለሆነው የሰው ልጅ ሰባዊ መብትና ነጻነት ጥብቅና የቆሙ የጥበብ ሰዎች እንደ ነጻ አውጭ አርበኛ ሲሞገሱ፤ ሲወደሱና ሲመለኩ ይኖራሉ።
በሌላ መልኩ አድርባይ ፤ እበላባይ አርቲስቶችን፤ አንባ ገነኖች፤ ህዝብን በዜማና በጥበብ እንዲያደነዝዙላቸው ማበረታታት ማስገደድም የተለመደ ነው። እንዲመለኩ እንዲዘመርላቸው፤ መልካቸው አምሮ እንዲሳልላቸው፤ የሚገዟት አገር በምስላቸው እንድትሸፈን ያስደርጋሉ። የተለመደ ነው። የመለስ ዜናዊ ፎቶ ከዚያች ቅዱስ ምድራችን ተለቅሞ ይልቆ ይሆን?
ወያኔ ወደ ስልጣን የመጣ የመጀመሪያዎቹ አመታት እንደነጻ ፕሬስ ጋዜጠኞች በርካታ አርቲስቶች ማለት ይቻላል፤ የአንድነትን ጥቅም፤ በዘር የመከፋፈልን ጉዳት፤ በዜማዎቻቸው ለማስገንዘብ ሞክረዋል። ከፊሎቹ ከልባቸው በራሳቸው ሰብእና ውስጥ ካላቸው ኢትዮጵያዊ ስሜት ተነስተው እንደቴዲ አፍሮ አይነቶቹ በሀገራቸውና በህዝባቸው ጉዳይ ላይ የማይናወጥ ጠንካራ ወገንተኝነት እንደያዙ ዘልቀዋል።
አንዳንዶች ደግሞ በወቅታዊ የህዝብ ብሶት ላይ ያተኮረ ስራ ማቅረብ ገበያ ያስገኛል ብለው በማመንም ሊሆን ይችላል፤ የህዝቡን ብሶት የሚኮረኩሩ ስራዎችን አቅርበው የተቸራቸው ድጋፍና ጭብጭባ ሳያባራ፤ ሶስት መቶ ሰላሳ ዲግሪ ተሽከርክረው፤ በአንዲት ቀን ጀንበር ወደ ካድሬነት የተለወጡ አሉ። ሰለሞን ተካልኝ ተገፋን ሲል በዘመረበት አፉ ነው ስለመለስ ዜናዊ ቅንድብ ማማር ማላዘን የጀመረው።
ገናናዋ የደቡብ አፍሪካ ተወላጅ ማሪያ ማኬባ እንደ አውሮፓውያኑ ዘመን አቆጣጠር 1963 ዓ ም ለተባበሩት መንግታት ድርጅት የደቡብ አፍሪካው የነጮች መንግስት ያሰፈነው የአፓርታይድ ስራት፤ በሀገሬው ተወላጅ ላይ እያደረሰ የነበረውን ስቃይ በመመስክሯ ነበር የገዛ አገሯን የዜግነት መብት ገፏት፤ ካገሯ እንድትሰደድ ያደረጋት አፓርታይድ። ማሪያ ለስርአቱ ያጎበደደችበት ጊዜ አልነበረም። በዜማዎቿ ህዝቡ ለነጻነቱ እንዲታገል ታበረታታ ትቀሰቅስ ነበር።
ከዚያ በኋላ ለሰላሳ አመታት በኖረችበት የስደት ዓለም፤ በዜማዎቿ ፤ በንግግሮቿ፤ አፓርታይድ ምን አይነት ስራት እንደሆነ፤ በደቡብ አፍሪካ ህዝብ ላይ ምን አይነት ግፍ እንደሚፈጸም ስትነግር፤ የደቡብ አፍሪካውያንን ባህሎችና ልምዶች ስታስተዋውቅ ኖረች።
ቁጥራቸው በቀላል የማይገመት ኢትዮጵያን አርቲስቶች ሀገራቸውን ጥለው በውጭው ዓለም ለመኖር ሲወስኑ ጥቂቱ፤ የስራቱን እኩይ ተግባራት እየኮነኑ የህዝባቸውን መከራና ስቃይ በማስተጋባታቸው የዘረኛው ህውሀት ቡድን ሰለባ በመሆናቸው ለስደት ተዳርዋል። ከነዚህም ታማኝ በየነ በዋናነት ይጠቀሳል። ሌሎችም የተሻለ ህይወትና ኑሮ ፍለጋ ያተርፈናል ወዳሉት አህጉር ተሰደዋል። ይሁንና እነዚህ አርቲስቶች ሀሳብን እንደልብ መግለጽ በሚቻልበት ሀገር ውስጥ የመኖራቸውን ያህል ኢትዮጵያ ውስጥ እየደረሰ ያለውን ሁለንተናዊ ጥፋትና የሰብአዊ መብት ረገጣ፤ በጥበብ ስራዎቻቸው በመዋጋት ረገድ የዜግነት ግዴታቸውን እየተወጡ ነው ወይ?
ከቅርብ አመታት ወዲህ ሀገር ቤት ያሉ አርቲስቶች እጅግ በሚያሳፍርና ለማመን በሚያዳግት መልኩ፤ የኢትዮጵያን ህዝብ ክደው፤ የወያኔ የፕሮጋንዳ እቃና አጫፋሪ ሆነው፤ የገዛ ሀገሩን ባንዲራውንና ወገኑን ክዶ፤ ስለ ዲሞክራሲ የተናገረውን፤ ስለመብት የተናገረውን፤ የጻፈውን ሁሉ በመጨፍጨፍና ወህኒ በማጋዝ አለም አቀፍ ዝና ላተረፈው መለስ ዜናዊ ፤ የወርቅ ብእር ሽልማት መስጠት ፤ የኢትዮጵያን መፍረስና የአንድን ዘር የበላይነት ተቀብሎ፤ በሎሌነት ለማደር ከመዘጋጀት ውጭ ምንም አይነት መልእክት ያለው ተግባር አልነበረም። ስመጥሩና እጅግ ተወዳጅ የነበሩ አርቲስቶች ዛሬ ወደ ነፈሰበት አዘንብለው፤ ስለወያኔ ስራት ና መሪዎች መልካምነት የምስክርነት ቃላቸውን ሲሰጡ መስማት ጥበብ በኢትዮጵያ ውስጥ መዝቀጧንና ተጠባቢውም በአድርባይነትና እበላባይነት ሰብእና ውስጥ መስጠሙን ያመለክታል።
በራሱ ሩጫና ጥረት የሚተዳደር አዝማሪ የህዝብ ግጥም እየተቀበለ ዜጎችን ማዝናናት ያልቻለበት ደረጃ ላይ መደረሱ፤ ያስደነግጣል። ልማታዊ ግጥም እንጂ መቀበል አለመቻሉ፤ ወያኔ የኢትዮጵያን ህዝብ ምን ያህል አካሉንም ህሊናውንም እንደገዛው አመላካች ነው። ይህ ቡድን እምን ድረስ ዝቅ ብሎ የኢትዮጵያን ህዝብ ለመቆጣጠረ እየሞከረ እንዳለ የሚያስገነዝብ ሁኔታ ነው።
ሀተታውን እዚሁ ላይ ላቁመውና ዋናው የርእሴ ጉዳይ ወደ ሆነው እንደ ማሪያ ማኬባ በተሰደደበት የባእድ አገር ፤ በሚያውቅበትና በሚችለው ሙያው እናት ሀገር ኢትዮጵያን የወረራት ህውሀት ዘረኛ አስተዳደር በሀገርና በህዝብ ላይ እያደረሰ ያለውን አደጋና ጥፋት በዜማው እየነገረ፤ እየመከረ፤ የሚበጀውን እያመለከተ ትግሎን ስለተያያዘው አርቲስት ሻንበል በላይነህ ስራዎች ላወሳ እሻለሁ።
ውድ አንባቢያን አርቲስቱ ባልፉት አመታት የተጫወታቸውን በርካታ ቀስቃሽ ዜማዎች ሁሉ በዚህ አጭር ጽሁፍ ውስጥ አካቶ ለማመላከት አይቻለኝም ። ለዛሬ በቅርቡ ካወጣቸው ሲዲዎች “ በቁም እንዋደድ እናም ሀይለስላሴ” የሚል መጠሪያ ከሰጣቸው ሁለት አልበሞቹ ውስጥ በሀገራችን ባለው ወቅታዊ እውነታ ላይ ያጠነጠኑ ቀስቃሽ ግጥሞቹን፤ ከየዘፈኑ የተወሰኑ ስንኞች እያወጣሁ ያሰውን ሁኔታ እንዴት ቁልጭ አድርጎ እንዳስቀመጠው ለማመላከት እሞክራለሁ፤ ሌሎች አርቲስቶቻችንም ወቅታዊውን ሁለገብ ትግል ለማገዝ በዜማዎቻቸው ህዝቡን ለነጻነት ማነሳሳት እንዲጀምሩ ጥሪ ለማቅረብ እሻለሁ። ከንግዲህ ኢትዮጵያውያን በሚችሉት ሁሉ ወደ ትግሉ በመቀላቀል የወያኔን ስርአት እስትንፋስ ማሳጠር ግድ ይላል።
ይሰማ ድምጻችን…. ግጥም አይገልጥም፤ ዜማ..ሻንበል በላይነህ
….እኛ አንበተንም፤ እኛ አንበተንም፤ ሙስሊም ክርስቲያኑ ልዩነት የለንም።
ዛሬም ቢሆን እንደበፊታችን፤ ተጠናክሮ ይህ አንድነታችን፤
ሙስሊም ክርስቲያኑ በለቅሶም በሰርጉም፤ አብረን እንኖራለ በክፉም በደጉም። …..
አዎ!.. “..ተነሱ ውጡና እስላም ወንድሞቻችሁን ስደቡ፤ እርገሙ፤ መንግስት ሊሆኑባችሁና ሊያጠፏችሁ ነው “ እያለ የኢትዮጵያን ክርስቲያኖች እያስፈራራና እየዛተ አደባባይ የሚያወጣ፤ በመንግስት ቅርጽ መደራጀት የቻለ የወንጀለኞች ቡድን፤ ምናልባትም በዛሬዪቱ አለማችን በአይነቱ የተለየ የሆነ፤ መንግስት የሚመስል የወንጀለኞች ቡድን ፤ ሀገር በተቆጣጠረበት፤ ሻንበል በላይነህ በምርዋ ድምጹ በጣፋጭ ዜማው ያንቆረቆረልን መልእክት ህዝባዊ እንጉርጉሮ መሆን ያለበትና ሁሉም ኢትዮዝፕያዊ ሊያንጉራጉረው የሚገባ የሙስሊም ክርስቲያኑን መተላለቅ ለሚናፍቀው ወያኔ ጠንካራ ምላሽ ነው።

ህዝበክርስቲያን፡ መስሊሙ፤
ሁሌም በውኑ፡ በህልሙ፤
ያስባል ስለሰላሙ ….
ችግሩ የኢትዮጵያን ህዝብ ከማሸበር ተግባሩ ያልታቀበው የወያኔ ቡድን ነው እንጂ፤ ህዝቡ ስለሰላሙ ያስባል። በአስራ አምስተኛው ክፍለ ዘመን ግራኝ አህመድ ሙስሊሙን ይዞ ያን ያክል ጥፋት ሲያደርስ፤ ሙስሊሙን የድጋፍና የሀይል ምንጭ አድርጎት ለራሱ የመንግስትነትን ስልጣን ለመቀዳጅት ተዋጋ እንጂ፤ ነብዩ ሙሀመድ ያላዘዙትን፤ እስልምናን በሰይፍ በኢትዮጵያ ውስጥ ሊያስፋፋ አልነበረም ጦርነቱ ፤ “አህባሽ የሚባለውን እስልምና ፤ እኔ ያመጣሁልህን ተቀበል ፤ ለሺዎች ዘመናት ይዘህ የተጓዝከውን እምነትህን ጣል” እያለ በኢትዮጵያዊው ሙስሊም ላይ ከጂሀድ ያልተናነስ ስራ እየሰራ ያለው ወያኔ ነው። ማሰር መግደል። ኢትዮጵያዊው ሙስሊም ክርስቲያን ወንድሞቹን ያሸ በረበት ዘመን የለም። አርቲስቶቻችን እንደሻንበል በላይነህ በዜማቸው ደግመው ደጋግመው ሊናገሩት የሚገባ እውነታ ነው።
አማራ… ግጥም፤ አይገልጽም። ዜማ፤ የህዝብ…
……ምነው ምን በደለ ደጉ ያገሬ ሰው፤ አረ የሰው ያለህ ፡አረሰው፡ አረ ሰው። እሳት ቢያንቀላፋ ገለባ ጎበኘው፤ ዘመን አረጀና ይሄ ቀን አገኘው። ከባህር ይሰፋል አማራ ማለት፤ ያንድነት ሀረግ ነው ኢትዮጵያዊነት ……
በፋሸሽት ወረራ ዘመን ተፈጸመ ያልተባለ ግፍ፤ አማሮች እስከወዲያኛው እንዲጠፉ፤ በሽታ ገብቷል ብለው የወያኔ ጤና ጥበቃ ሀላፊዎች ወጣት የአማራ ታዳጊዎችን በክትባት ዘመቻ እንዳይወልዱ ያመከነ አውሬ ቡድን የጁን ማግኘት አለበት። ይህ በጥይት ተጨፍጭፎ አላልቅ ያለ ህዝብ፤ እንደሌሎቹ ኢትዮጵያውያን እንደኦሮሞው፤ እንደትግሬው፤ እንደአፋሩ እንደ ደቡቡ እንደ ሁሉም….. ደሙን እያፈሰሰ ፤ ኢትዮጵያን ሲያቀና ዳር ድንበር ሲያስከብር ኖረ እንጂ፤ ወያኔ ሻእቢአና መሰሎቻቸው እንደሚያወሩት ተረት፤ ሌሎቹን ሲገዛና ሲጨቁን አልኖረም። ይልቁን ከማንም በክፋ መልኩ ሲረገጥ ነው የምናየው። የጎጃምን ድሀ አርሶ አደር፤ ከትግራይ ደሀ አርሶ አደር፤ የትግራይን ድሀ አርሶ አደር፤ ከሀረርጌ ድሀ አርሶ አደር ባጠቃላይ የኢትዮጵያን ድሀ ህዝብ አንዱን ካንዱ የተለየ የሚያደርገው የትኛው ኑሮው ነውና ነው አማራው ተለይቶ እንዲጠፋ የተፈረደበት? የህውሀት በሽተኞች አማራውን የበቀል ኢላማ ያደረጉበት ምክንያት እንደሎሎቹ ሁሉ ለኢትዮጵያ ቀናኢ በመሆኑ ነው። ወያኔ አማራን በማጥፋት ኢትዮጵያን የሚያጠፋ ሊመስለው ይችል ይሆናል፤ ግና ለኢትዮጵያ ደሙን ያፈሰሰላት ከሰሜን ምጽዋ ጫፍ እስከ ደቡብ ዶሎ፤ ከምስራቅ ፌርፌር ጫፍ እስከ ምእራብ ኢሎባቡር ጫፍ ያለ ህዝብ ሁሉ ነው። አሁንም ከወያኔ የማጥፋት ዘመቻ ያድናታል። ኢትዮጵያን ይታደጋታል።

ዘንድሮ… ግጥም፤ ተስፋዬ ለማ። ዜማ፤ ተስፋዬ ለማ
……ህጻናት ሲሸጡ ወተው በማደጎ፤ ያለቅሳል ባመቱ ወላጅ አደግድጎ…. ሻንበል በላይነህ በዜማው የነገረን የምናየው ነገር ነው። በማደጎ ስም ህጻናቶቻችንን እየቸበቸበ ያለው ወያኔ ህጻናቱ ካገር ከወጡ በሗላ የት ወደቁ ያለበት ጊዜ የለውም። በስርቆትና በዘረፋ ስለተጠመደ ስለዜጎች የሚያስብበት ገዜ የለውም። ሽያጩ ግን በስፋት እንደቀጠለ ነው። በየ አለሙ ያሉት ኢምባሲዎቹም ድለላውናንና ዶላር ማቀባበሉን እንጂ ስለኢትዮጵያውያን መብትም ሆነ ህይወት የሚያገባቸው ነገር የለም። ዓለም ደቻሳ ቤይሩት ወያኔ ኢንባሲ ፊት ለፊት ነበር ኡ ኡ እያለች በባእድ ጫማ ስትረገጥ መሬት ለመሬት ስትጎተት በዚያው የራሷን ህይወት ያጠፋችው። የኢትዮጵያ ኢምባሲ ተብሎ ወያኔዎች እዚያው ነበር አድፍጠው በዚያች ኢትዮጵያዊ ድሀ ላይ ይደርስ የነበረውን የሚመለከቱት። እነዚህን ነው ሀያ ሁለት አመት ተሸክመን የተቀመጥነው።
…..ጥያቄ ባነሳ መብቱን ያስከበረ፤ ጸረ ሰላም ሲሉት በህግ ሽብር፤ እውነቱን አውጥቶ ስለተናገረ፤ ስንቱ ጋዜጠኛ እስር ቤት ታጎረ… ዘንድሮ
ፍርሀት አሽነፈን…. ግጥም፤ ተስፋዬ ለማ። ዜማ፤ ተስፋዬ ለማ
….ፍራት አሽመድምዶን ጥሎን ባደባባይ፤ ክፉንም ደጉንም ሁነናል ተቀባይ፤ የቆረቆረንን ምቹ ስናስመስል፤ ስንጨስ እንኖራልን ስንጠቁር ስንከስል……
አዎ .. ኢትዮጵያውያን በባህላችንም በተፈጥሮአችንም፤ ለህግ የመገዛት፤ የማክበር፤ በይሉኝታ መገዛት መፍራት፤ ስለሚያጠቃን፤ አንዳንድ ጌዜ ስንገፋና መብታችን ሲገፈፍ፤ ይህ ተፈጥሮ ከልክ ያለፈ ትግስት እንዲኖረን ያደረገ ይመስላል። ለዚህ ስርአት ያሳየነው ከልክ ያለፈ ትግስት ፍርሀት ነው የሚመስለው። አርቲስት ሻንበል በበላይነህ ምናልባትም ይህንኑ ታዝቦ ሳይሆን አልቀረም በዜማው እየነገረን ያለው። ሆድ ይፍጀው ወይም የባሰ አታምጣ እያልን ይኸው ሀያ ሁለት አመታት ጉዳት ተሸካሚዎች ሆነን በዚያው ጉዞ ቀጥሏል።
….. በጥቅም ሲፈረድ፤ በወገን ሲሰራ፤ አይተን እያለፍን ስንጠብቅ ወር ተራ፤ ፍርሀት እንደውሀ ወኔያችን አፍሶት፤ ይዘን ኖራለን የማይወጣ ብሶት…
መለስ ስብሀት ሰራሹ የወያኔ ገዢ ቡድን ወደስልጣን ከመጣበት ጊዜ ጀምሮ በመንግስቱም ሆነ በግላ ተቋማት፤ ያሻውን ሲሰራ ስንቱን ሺህ ሰራተኛ በገፍና በግፍ እያባረረ የወደደውን የራሱን ምልምል እስከ አሁን ድረስ ሲሰገስግ፤ ሁሉም ተራው ሲደርስ ሜዳ ላይ እየተጣለ ከማልቀስ በቀር ዛሬ በወገኔ ላይ የደረሰ ነገ በኔ ነው ብሎ አምርሮ ስራቱን ለመዋጋት የተነሳ እስካሁን የለም።
የቀድሞው ሰራዊት….. ግጥም ይልማ ገብረአብ። ዜማ ሻምበል በላይነህ ….ጊዜ ተለውጦ ቀን እስከሚከዳው፤ አንጠፍጥፎ ቀምሶ ውሀውን ከኮዳው፤ ያገር መሰረቱ ህብረቱ እንዳይናድ፤ ኑሮውን አድርጎ በቀበሮ ጉርጓድ፤ ታግሎ ወድቆልናል ስላንድነታችን፤ ውለታው ይዘከር የሰራዊታችን። ሳያጓድል ያባት አደራ፤ ያስጠበቀ ያገር ባንዲራ፤ እንዳናጣ የባህር በር፤ ነፍሱን ከፍሏል ለኛ ክብር……
የወደቀ ዛፍ ምሳር ይበዛበታ እንደሚባለው ; የኢትዮጵያ ብሄራዊ ጦርሰራዊት መበተኑ ሳያንሰው ፤ ለወያኔ የፕሮፓጋንዳ ሰለባ እንደሆነ እስካሁን በመቆየቱ እድሜ ልኩን ሲዘመርለትና ሲሞገስ ሊኖር የሚገባው ጀግና ሰራዊት፤ ባልፉት ሀያ ሁለት አመታት እንደዋዛ ተዘንግቶ ቆይቶ ነበር። ሻንበል በላይነህ ምስጋና ይድረሰውና ዛሬም እንደትናንቱ የዚያን ክቡር ሰራዊት ገድል አንስቷል። ይበል የሚያሰኝ ነው። የኢትዮጵያን ሰራዊት ሀያል ክንድ አጣጥመው የሚያውቁት ገንጣይና አስገንጣይ እንዳላሸነፉት ልቦናቸው ያውቀዋል። ሰራዊቱን በአካልና በሞራል ከውስጥ ይገልላቸው የነበረው መንግስቱ ሀይለማርያም ባለውለታቸው ነው። በዚያ በውሸት ፕሮፓጋንዳቸው እውነት ለዲሞክራሲና ለእኩልነት የሚዋጉ መስሎት በገፍ እየሄድ ሲቀላቀላቸው፤ ያልተቀላቀለውም መሳሪያውን አውርዶ ባዶ እጁን የቆመ ወታደር በመትረየስ እያጨዱ ነበር ተሯሩጠው ድፍን ኢትዮጵያን እንደ ወባ ትንኝ የወረሯት። መልካሙ ነገር ኢትዮጵያውያን ጀግኖቻችንን መሸለም መጀምራቸው ነው። ያየር ሀይል፤ የምድር ጦር የባህር ሀይል ጀግኖቻችን አሁንም ሊዘፈንላቸው ሊሸለሙና ሊወደሱ ይገባል።

ታሪክ ይፍረደን፤ ግጥም፤ ተስፋዬ ለማ። ዜማ፤ ተስፋዬ ለማ
…የነበረው ቀርቶ ያልነበረው ሆነ፤ የሰራነው ሁሉ እንደቀልድ ባከነ….. ……… .የራሳችን ቋንቋ የራሳችን ፊደል፤ የራሳችን እምነት የራሳችን ባህል፤ የነሉሲ ሀገር፤ የሰው ልጅ መገኛ፤ በራሱ የተሟላ ማን ነበር እንደኛ……
እርግጥ ነው። በራሱ የተሟላ እንደኛ ማንም አልነበረም:: ምን ያደርጋል፤ በመካከላችን የበቀሉ፤ በዚችው ምድር ላይ የተፈለፈሉ፤ ለራሳቸው ታሪክ ባእድ ሆነው፤ አባቶቻቸው የባእድ ጠላት አሽከሮችና ባንዳዎች፤ ያ ጠላት በወላጆቻቸው እአምሮ ውስጥ ባሰረጸው እኩይ አስተሳሰብ ተኮትኩተው ያደጉ፤ ጊዜ ለነሱ አድልታ ኢትዮጵያ እጃቸው ላይ ወደቀች። በማግስቱም … የአድዋው ታሪክ ለአማራው፤ ለደቡቡ ምኑ ነው፤ የኢትዮጵያ ባንዲራ ጨርቅ ነው፤ እንኳን ከትግራይ ተወለድኩ፤ የሚል ሰው መሪ ተብሎ ባደባባይ የሚናገር፤ ሚኒሊክ ቤተ መንግስት መኖር የቻለ አጥፊ አየን። መልካሙ ነገር እግዚአብሄር ባጭር አስቀረው። የጀግኖቻችን ሀውልቶች ፈረሱ። በባንዳ ልጆች ስም ተተኩ። በዘመናት አብሮ መኖር የተገነባ የደምና የስጋ ውህደት እንዲለያይ የዘር አጥር ግርግዳ የሚገነቡ፤ በስጋ ፤ ኢትዮጵያውያን፤ በመንፈስና በገቢር ባእዳን የሆኑ ገዢዎችን ለማስተናገድ በቃን። የሻምበል በላይነህ ዜማ ይህንን ነው ልብ ብሎ ለሰማ የሚነግረው።
ኢትዮጵያ…. ግጥም፤ ይልማ ገብረአብ። ዜማ፤ ይልማ ገብረአብ
…….ኢትዮጵያ ህይወታችን፤ ኢትይጵያ ኩራታችን፤ ኢትዮጵያ እምነታችን፤ ያገር ፍቅር ጽናት የምንማርብሽ፤ በፈጠርሽው ትውልድ ይመርብሽ፤ ዛሬም ትላንትም የምልሽ ህይወቴ፤ ውዳሴ ነሽ ለኔ የዘላለም ሀብቴ…. ከዳሽ በሞትሽ ለማትረፍ፤ በሚኒሊክ ጅራፍ ልገረፍ….
ውድ አንባቢያን እነዚህ ሁሉ መልክቶች ሻንበል በላይነህ በቁም እንዋደድ በሚለው አልበሙ ውስጥ ያካተታቸው ስራዎቹ ናቸው። ሀይለስላሴ የሚል ርእስ የተሰጠው ሲዲም ብዙ ታሪካዊና ወቅታዊ መል እክቶች አሉት፤ በተለይም በከፍጠኛ ሁኔታ ወጣቶችን ለትግል የሚያነቃቃ መልእክቶችም አሉ። እራሱን ማዳመጡ የተሻለ ነው። የሻንበል በላይነህ ስራዎች ለአርቲስቶቻችን በአርአያነት የሚጠቀሱ ናቸው። ተመሳሳይ ስራዎች ከየአቅጣጫው ብቅብቅ ቢሉ የህዝባችንን ንቃት እጥፍ ድርብ ያሳድጉታል። ሻንበልም የነጻነት ቀን እስከሚመጣ በያዘው መንግድ እንደሚጓዝና ሌሎችንም እንደሚያስከትል ተስፋ አደርጋለሁ።
ኢትዮጵያ ለዘለአለም ትኑር
lkebede10@gmail.com

የደርብ ከፈለኝ አስተያየት በእኔ እይታ –መሠረት ከቴክሳስ

$
0
0

‘አህያውን ፈርቶ ዳውላውን’ በሚል ርእስ በተክለሚካኤል ላይ የስድብ ውርጅብኝ ያወረዱት ደርብ ከፈለኝን ሳስብ በእኛ በኢትዮጵያውያን ውስጥ በብዙ ሰዎች ዘንድ የማየው በሽታ ታወሰኝ። ይኸውም ታዋቂን፣ሀብታምን፣ባለስልጣንን እንደው ብቻ በማናቸውም መልኩ በማህበረሰቡ አይን ውስጥ የገባን ሰው ማሞካሽት፤ ቢሳሳት እንኳን ስህተቱን ስህተት ነው ብሎ ደፍሮ ከማረም ግለሰቡ ከተናገረው ይዘት ጋር በማይገናኝ ሁኔታ አቃንቶ እንዲህ ለማለት ፈልጎ እኮ ነው ብለው የሚሉ ብዙ ሰዎችን አውቃለሁ። እንዲህ አይነት ሰዎች ከባለ ጉዳዩ በላይ ተቆርቋሪ ሆነው ከስህተቱ እንዳይማር መንገድ የሚዘጉ፣እንደዚያ አይነት ሰው ስህተት ቢፈጽም እንኳን ይቅርታ መጠየቅ የማይገባው መሆኑን እስከመግለጽ ይደርሳሉ።

             ይህን መሰል አንድ እውነተኛ ታሪክ ላጫውታችሁ። በአሜሪካን አገር ውስጥ አንድ የአበሻው ብዛት ከሁለት ሺህ አይበልጥባትም በምትባል ከተማ ውስጥ አበሾች ተሰባስበው ቤተክርስቲያን ይተክላሉ። ቤተክርስቲያኗም የምትተዳደረው አቡነ ይስሐቅ በሚባሉት ጳጳስ ስር ነበር። አቡነ ይስሐቅ ነፍሳቸውን እግዚአብሔር በገነት ያኑርልንና በዘመናቸው የኢትዮጵያን ቋንቋ የማይናገሩ ህዝቦችን አስተምረው የእኛን ኦርቶዶከስ እምነት አለማቀፋዊ ይዘት ያላበሱ ትልቅ አባት ነበሩ። እሳቸው ከሞቱ በሁዋላ ቤተክርስቲያኗ ከአገር ውስጥም ከውጨውም ሲኖዶስ ሳትሆን ከምእመናን በተውጣጡ የቦርድ አባላት እየተመራች ባለችበት ሁኔታ ውስጥ የቤተክርስቲያኗ ካህን ምእመኑን ለመከፋፈል እራሳቸውን አንዴ የወሎ ሰው ነኝ ብለው ወሎዬውን ሲሰብኩ ሌላኛውን ጎጃሜነኝ ሲሉ ሌላውንም ሌላ እያሉ ምእመኑን እየፈተሹ ባሉበት ሂደት ውስጥ አንድ ቀን ያልታሰበ ዱብዳ ተፈጠረ ። ይኸውም ካህኑ ከአራት አባት ምአመናን ጋር የቆመችውን ሴት የተናገሩትን ለመድገም በሚያሸማቅቅ ቃላት ዘለፉዋት። መንፈሳዊው አባት ሲሳደቡ ምእመን አባቶች ቆመው ታዘቡ። በትዝብት ማለፉ አስተማሪነት የለውም በሚል በአደባባይ በደፈናው ስህተት መፈጸማቸውን አምነው ይህቺን ሴት በቤተመቅደስ ቆመው ይቅርታ እንዲጠይቁ ከ4ምእመናን ሶስቱ ጠየቁ። አራተኛው ግን ይህ ነገር በእኛው መሀል ይቅር፣ ሴትየዋን እኛ ይቅርታ ጠይቀን ለሌላም ሰው እንዳትናገር እናግባባት በሚል አቋም ይይዛሉ። የተቀሩት ሶስቱ ግን ይህ በተአምር አይደረግም ብለው ጉዳዩን ምእመኑ ፊት ይዘውት ቀረቡ። ብዙዉ ምእመን ካህን ቢያጠፋ እግዜር ይጠይቀው እንጂ ሰው ምን አገባው ባይ ሆነና ለካህኑ የቆመው ሰው ጉልበት አገኘ። እነኝህኞቹ እውነትን ይዘው ካህኑን ሞገቱዋቸው። ካህኑም ስለ እውነት ስንት ነገር እያስተማሩ ፊትለፊታቸው እውነት ሲያፈጥባቸው አልቻሉምና ልክናችሁ ልጆቼ ብለው ለይቅርታ ንስሀቸውን መናዘዝ ሲጀምሩ ከአራቱ አንዱ የሆነው ሰው ‘ልጅ እንጂ አባት ይቅርታ እንዴት ይጠይቃል’ በማለት ሌላውን ምአመን ምን ዝም ትላላችሁ በማለት ሲያነሳሳ ካህኑም ወዲያው ሀሳባቸውን ገልብጠው ጥፋተኛ አይደለሁም በማለት ጉባኤው በብጥብጥ ተበተነ። ይህቺ አጋጣሚ ለካህኑ የትልቌ እድል በር ከፈተችና ለእውነት ሲሙዋገቱ የነበሩት ምእመናንና ተከታዮቻቸው ሲቀሩ የተቀሩትን ይዘው ቤተክርስቲያኗን ለአባ ጳውሎሱ ሲኖዶስ የእጅ መንሻ አድርገው በማቅረብ እሳቸውም የጳጳስነት ሹመታቸውን በማግኘት ሂደቱ ተጠናቀቀ።

መቼም ይሄ ጥፋት ህሊና ለአለው ሁሌም ሲያሳፍር የሚኖር ነው። ዛሬ በዚያ አካባቢ ለአንድ ቤተክርስቲያን የማይበቃ ህዝብ በአለበት፣ ሁለት ቤተክርስቲያን ተሰርቶ ሰዉም ቂም ቋጠሮ ያንን ክፉ ቀን በሁለቱም ወገን የማይረሱት ታሪክ ሆኖ ተቀምጧል። የያኔው ቄስ የዛሬው ጳጳስ እድሜ ሰጥቷቸው ይህን ማስተዋል ከቻሉ የህሊና ቁስል እንደሚሆንባቸው አልጠራጠርም። የእሳቸው ተቆርቋሪ ነኝ ብሎ ትልቅ ስህተት ውስጥ የጨመራቸውን ሰው ግን ያ ሰይጣን ባያሳስተኝ ኖሮ እኮ እንደሚሉ አሁንም በድጋሚ አልጠራጠርም። ሰውየው ካህን ተሳስቷል ከሚለው ሃሳብ ተሻግሮ ይቅርተቀ ይጠይቅ  የሚለው ሃሳብ  አሳፋሪ አድርጎ በውስጡ በማመኑና እምነቱን ከእራሱ አልፎ ለሌሎችና ባለጉዳዩንም የሃሳቡ ተጋሪ በማድረጉ  እራሱ መሳሳቱ ሳይበቃው ካህኑንና ሌሎችንም ከእውነት ጋር አጣልቱዋቸው ለብዙዎች የተረፈ የታሪክ ጠባሳ ጥሎ አልፉዋል። ደርብ ከፈለኝ በጽሁፎት ላይ ማጋነን ባይሆንብኝ ከ90 በመቶ በላይ ትችቱ ተክለሚካኤልን መዝለፍ  ነው። አንባቢም ሆነ ተተቺ እንዲሁም ተቺ እርሶ ትችቱን ስር በያዘና በጥሩ ምክንያቶች የእራስዎትን እይታ ቢሰጡ መልካም ነበር። መቼም ዶ/ር ብርሃኑ እንደቄሱ ደጋፊ ከአገኘሁ ብሎ ሽምጥጥ አድርጎ የእርስዎ ደጋፊ ሊሆን እንደማይችል እገምታለሁ። የእኔ ጽሁፍ አላማ በተክሌ ጽሁፍ አስተያየት ለመስጠት ባይሆንም ዶ/ር ብርሃኑ ግን የተክሌ ሀሳብ የእሱ ብቻ አለመሆኑን ሊገነዘበው እንደሚገባ አሳስባለሁ። ባለራዕዩ፣  ምሁሩ ፣ የምርጫ 97 ሞተሩ፣የእስርቤቱ ታሪክ ጸሐፊው እንዲሁም የግንቦት 7 ፈጣሪው ብርሃኑ እንደ ሰው ለፍጹምነት ሲሮጥ ያልፋል እንጂ ፍጹም አይደለም። እንደ ሰው የሚጎለውን ፊትለፈት ነግረነው አድመጭ መሪያችን እንዲሆን ማድረግ ይኖርብናል።  መተቸትን ዛሬ በቅርብ ሆኖ ካላስለመድነው ነገ ስልጣን የመያዝ አጋጣሚው ቢፈጠርና  አውሬ ሆኖ ቢበላን ጥፋቱ የእኛ እንጂ የእሱ አይሆንም። ለማንኛውም ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ እባክህን አስተያትህን ስጠን። ካልሆነ ግን ኢሳት ላይ ጠይቁት ከተባለ ይህቺ ጥያቄ የእኔ ናት።

መሠረት ከቴክሳስ

 

Pen

 

ሕዝብን የሚያሸብር ሥርዓትና የህዝቡ መከራ -አበራ ሽፈራው /ከጀርመን/

$
0
0

አበራ ሽፈራው /ከጀርመን/

ዛሬ አለማችን በከፍተኛ ስልጣኔ ላይ ትገኛለች። በዚህም ስልጣኔ ውስጥ በኢንተርኔትና ተያያዥ የመገናኛ ዘዴዎች ተጠቅሞ የሰው ልጅ የሚፈልገውን መረጃ መፈልግ፣ማግኘት፣መለዋወጥና ማሳወቅም ሆነ ማወቅ የሚችልበት ጊዜ ላይ ደርሰናል።

ጊዜው ለውሸታሞች ፣ ለአታላዬች፣ ለግፈኞች እና ለበዝባዦች የሚመች አይደልም፤ ዓለም መድረስ ወደሚፈልግበት እየሔደ  ነው፤ጊዜው ወደፊት መሄድን እንጂ እንደኃለኛው ዘመን ማሰብን አይፈቅድም፤ ስለዚሀ ከጊዜው ጋር አብሮ መሄድ ካልሆነም ውሸታሞች ውሸታቸውን ሊድብቁ የሚችሉብትን አዳዲስ መሳሪያዎችን መፈብረክ ይጠይቃል።አለመታደል ሆነና ህወሓቶች  ስለእነሱና ስለተግባራቸው ማንም የሚያውቅ አይመስላቸውም። ትልቁ የሚያውቁትም ቃታን እየሳቡ ሰውን መግደል ብቻ መሆኑን ድርጊታቸው እያሳየን ነው፤ በዚህም ድርጊታቸው እንደ ትልቅ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለሙያዎች እራሳቸውን ከመሪዎቻቸው ጀምሮ ሲያጋንኑ፣ ከበሮ ሲያስደልቁ ኖርዋል አሁንም በሰብዓዊ ፍጥረት ላይ ግድያን መፈጸም፣መስረቅ፣መንጠቅ፣ማሸማቀቅ፣እያሰሩ ማሰቃየት፣በአጠቃላይ ግፍን መፈጸምና ማሸበር እንደትልቅ ሙያና ተግባር ተያይዘውታል።

ህወሃት /TPLF/ እ.ኤ.አ ከ1976-1991 በሰው ልጆች ላይ በፈጸማችው የሽብር ወንጀሎችና ጥቃቶች በአሸባሪነት ተመዝግቦ የነበረ ቡድንም ነበር። ህወሓት ሽብርን ለመፈጸም ለ39 ዓመታት ያካበተው ልምድ ቢኖረውም ከዚህ በላይ መሽበር ግን የህዝቡ ግዴታ ሊሆን አይግባም።

ህወሓት ዛሬ ሰላማዊ የፖለቲካ ትግልን ሽብር፣የሃይማኖት ነጻነት ጥያቄን ሽብር፣ጋዜጠኝነትን ሽብር፣መደራጀትን ሽብር ፣ሃሳብን በነጻነት መግልጽን ሽብር በማለት ህዝብን ሲያሸብር ሲታይ ህወሓት ስሙንና ተግባሩን ለሌላ ለመስጠት የፈለገ ይመስላል።

በየጊዜዉ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬድዮ ድርጅት አማካኝንት የሚነዙትን ፕሮፓጋንዳ ላየና ለሰማ ሁሉ ሽብርተኝነት ህወሃትን ያስመረረው ይመስላል። ይልቁንም የኢትዮጵያ ህዝብ በህወሃት መሸበሩንና መማረሩን፤ የሽብርተኝንት ታሪክም የህወሓት የራሱ የ39 ዓመታት ታሪክ እንጂ የኢትዮጵያ ህዝብ ታሪክ እንደልሆነ ለህወሓት ለራሱ ሊነገረው ይገባል።

  1. 1.    ህወሓት መንግስት ከመሆኑ በፊት የፈጸማቸው የሽብር ተግባራት ምን ነበሩ ?

ሀ. ህወሓት አሸባሪ ድርጅት የነበረና የተመዘገበም መሆኑ፡-

በዩ.ኤስ.ኤ አሜሪካ በአገር ውስጥ ደህንነት መስሪያ ቤት አማካኝንት በሜሪላንድ ዩንቨርስቲ በአለም አቀፍ ደረጃ የአሸባሪዎችን እንቅስቃሴና ድርጊታቸውን የሚመዘግበውና የሚተነትነው የመረጃ ማዕከል ማለትም The National Consortium for the study of Terrorism and Responses to Terrorism/START/ ለመረጃ መሰብሰቢያ ባዘጋጀው ዳታ ቤዝ  ወይም  GTD/Global Terrorism Data Base/ ክፍት በሆነው የመረጃ ፍልሰቱ ውስጥ እ.ኤ.አ ከ1976-1991 ድረስ አሥር/10/ ልዩ ልዩ የሽብር ጥቃቶች በህወሓት/TPLF/ መፈጸማቸውን መዝግባል፤ በነዚህ የሽብር ድርጊቶቹ ህወሓት አሸባሪ ድርጅት ተደርጎ ተመዝግባል። ይህ የመረጃ ማዕከል ህወሓት የፈጸማቸውን የሽብር ድርጊቶች የዘረዘረ ሲሆን በዚህ መረጃ ላይ ድርጊቱ የተፈጸመበት ቀን፣ ቦታ፣የአደጋው ብዛት፣ የአደጋው አይነት፣የተጠቀማቸውን የመሳሪያ ዓይነት ለመመዝገብ ሞክሯል፤በዚህ መረጃ መሰረት በራያ ቆቦ፣በትግራይ ቦታዎች፣በላሊበላ፣በጅሬ፣በኮረም፣በወርቅ አምባ፣በአክሱምና በሌሎች ቦታዎችም የሽብር ድርጊቱ የተፈጸመ መሆኑን ጽፋል፤በነዚህም ጥቃቶች የሃይማኖት ተቃማትና መሪዎች፣በግለሰብ ህይወት እና ንብረት ላይ፣ በመንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ላይ፣በንግድ ተቃማት ላይ ፣በጋዜጠኞች እና ሚዲያዎች ላይ ሽብሩ መፈጸሙን ዘርዝሯል። ስለዚህ ህወሓት አሸባሪ ድርጅት እንደነበረና ተግባሩም ሽብር እንደነበረ ለማወቅ ይቻላል። ለበለጠ መረጃ http://www.start.umd.edu/start/  ይመልከቱ።

 

ለ. ህወሓት ልዩ ልዩ ሽብሮችን ሲፈጽም እንደነበረ አባሎቹ የነበሩ መመስከራቸው፡-

የህወሃትን እኩይ ተግባር በማጋለጥ የሚታወቁት አቶ ገብረመድህን አርአያ ስለ ህወሓት ያለፈው ታሪክ ላይ በጻፋቸው ጽሁፎች ላይ ህወሓት ግልጽ አሸባሪ መሆኑን በተደጋጋሚ ከመግለጻቸውም በላይ አሁንም ካዩትና ከሰሙት እዉነታዎች ተነስተዉ ይህንን አሽባሪ ድርጅት እያጋለጡም ይገኛሉ።

ህወሓት ከምስረታው ጀምሮ የተነሳው የራሱን የህወሓትንና የኢትዮጵያን ህዝብ ጥቅም ለማስጠብቅ ሳይሆን ጥቂቶች በስውር ይዘዉት የተነሱትን ስውር የዘረኝነት፣የብዝበዛና የጭቆና ዕቅዶቻቸውን ከግብ ለማድረስ እንደህነ ተግባራቸው ያሳየና፤ ይህንንም ግባቸውን ለመፈጸም የትኛውንም ሽብር ከመፈጸማቸው ጋር ተያይዞ ህወሓቶች በዓለም ከሚታወቁ የሽብርተኛ ቡድን ተርታ ተሰልፈው የነበረ ቢሆንም ከቀዝቃዛው ጦርነት ማብቃት ጋርና ከደርግ መንግስት መንኮታኮት ጋር ተያይዞ አገራችን በአሸባሪዎች እጅ ወደቀች፤ ደርግና ባለማሎቹም እንዲሁም ዋና ዋናዎቹም የዓለም መንግስታትም ህዝቡንና አገራችንን አሳልፈው ለሽብርተኞች  ሰጡ ። ይለወጣል ብለው ብዙዎች ቢጠብቁትም ተግባሩ ያለቀቀው ህወሓት/ኢህአዴግ መንግስት ከሆነም በኃላ ከቡድናዊ ሽብርተኝንት ወደ መንግስታዊ ሽብርተኝነት ተሸጋገረ።

  1. 2.   የህወሓት/ኢህአዴግ  የመንግስት ስልጣን ከያዘ በኃላ ወደ መንግስታዊ ሽብርተኝነት መቀየር /State Terrorisim/

ሀ . ለመሆኑ የመንግስት ሽብርተኝንት/ State Terrorisim/ ምንድ ነው? 

ጸሃፊዎች የሽብርተኝነት መሰረታዊ ዓላማ ሽብርተኞቹ የሚፈልጉትን ፖለቲካዊ፣ኢኮኖሚያዊና ሃይማኖታዊ ግቦችን ተግባራዊ ለማድረግ ልዩ ልዩ መንገዶችን ተጠቅመው በህዝቦች ላይ ከሚገባው በላይ ፍርሃትን በመፍጠርና በማስገደድ ዓላማቸውን ከግብ ማድረስ እንደሆነ ይገልጻሉ።

በ acadamia.org ላይ የመንግስት ሽብርተኝነትን እንደዚህ ጽፎታል፡- State terror refers to the use or threat of violence by the state or its agent or supporters,particularly against civilian individuals and population,as a means of poletical intimidation and control.

የፖለቲካ የበላይነትን ለመያዝና ጫናን ለመፍጠር በተለይም በሰላማዊ ግለሰቦችና ህዝቦች ላይ ተገቢ ያልሆነን ጥቃትን በራሱ በመንግስት፣በተወካዮቹና በደጋፊዎቹ  ሲፈጸም ይህንን ጥቃት መንግስታዊ ሽብር ብሎታል።

እንግዲህ ህወሓት/ኢህአዴግ  ምንም እንካን የመንግስትን ሥልጣን የያዘ ቢሆንም ሌሎች አሸባሪ ድርጅቶች የሚፈጽማቸውን ተግባራት በግልጽና በአደባባይ ይፈጽማል። ከነዚህም ውስጥ ፍንዳታን ይፈጽማል ፣ያፍናል፣ህጋዊ ያልሆኑ እስራትን ይፈጽማል፣በሰብዓዊ ፍጥረት ላይ የማይፈጸሙ ድብደባዎችን፣ በወንዶችም ሆነ በሴቶች የመራቢያ ብልቶች ላይ አደጋን ማድረስ፣አካለ ስንኩል ማድረግ፣ ቤተሰቦች እንዲለያዩ ማድረግ፣ ስውርና የአደባባይ ላይ ግድያዎችንና ሌሎችም ተግባሮችን ይፈጽማል።ከዚህም ድርጊቱ አንጽር ህወሓት/ኢህአዴግ  ከአሸባሪነት መገለጫዎች የዘለሉ ተግባሮችን የሚፈጽም ቡድን መሆኑን ያሳያል።

ህወሓት/ኢህአዴግ  በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚፈጽመውን የሽብር ጥቃቶችን ኢትዮጵያውያን በግልጽ የሚያውቁት ጉዳይ መሆኑ ፣የልዩ ልዩ ሃገራት መንግስታትና በኢትዮጵያ የሚኖሩ የልዩ ልዩ ሃገራት አምባሳደሮችም ሳይቅሩ በግልጽ የሚያውቁት መሆኑና ይህንንም የሚያግዙ የተለያዩ መረጃዎች እየወጡ መሆናቸው፤በተለይም የዩ.ኤስ.ኤ አሜሪካንና ሌሎችንም መረጃዎችን በመሰብሰብ እና በማጋለጥ የሚታወቀው ዊኪሊክስ ይፋ ባደረጋቸው መረጃዎች መሰረት እነዚህ እውነታዎች ግልጽ እየሆኑ መምጣታቸውና በተለይም ህወሓት የራሱን የሽብርን ጥቃት ለመፈጸም እንዲያግዘው ኢትዮጵያ ውስጥ የሽብር ጥቃት እንዳለ ለማስመሰል ሲጠቀምባቸው የነበሩትን የማታለያ እንቅስቃሴዎች ማለትም የሽብር መሳሪያዎችን በራሱ ወታደሮችና የደህንነት ሰዎች በልዩ ልዩ ቦታዎች በማስቀመጥ መልሶ በራሱ የደህንነት ሰዎች እንደተገኙ በማስመሰል ያደርገዉ የነበረውን ተግባር አጋልጧል፤ እነዚህም ድርጊቶቹ  አስቀድሞም ብዙዎች  የነበራቸውን ጥርጣሬም አጠናክሮታል።

 

ለ. ህወሓትኢህአዴግ የፈጸማቸው የሽብር ጥቃቶችስ ምንድ ናቸው?

ህወሓት/ኢህአዴግ የመንግስትን ሥልጣን ከያዘ በኃላ መጠነ ሰፊ የሽብር ጥቃቶችን በህዝቡ ላይ በተለያዩ ጊዜያትና ቦታ የፈጸመ ሲሆን ዋና ዋናዎቹን በጥቂቱ እንመልከት፡-

  1. በወልቃሪት ጠገዴ ህዝቦች ላይ የተፈጸሙት የዘር ማጥፋት ዘመቻና የዚህንም ህዝብ ህልዉና በማጥፋት የራሱን መስፋፋት ከግብ ለማድረስ በህዝቡና በትውልዱ ላይ የተወሰደዉ የዘር ማጥፋት ተግባር እጅግ ዘግናኝ ተግባር የሆነና ጉዳዩ ገና መፍትሄ ያልተገኘለት ይልቁንም ገና ብዙ ቀውስን ሊፈጥር የሚችል ተግባር መሆኑም እራሱም ህወሃትም ያልተረዳው ግፍ ነዉ።ለበለጠ መረጃ http://ethio-wolqait.blogspot.de/. እና ሌሎችንም ተያያዥ ጽሁፎችን ይመልከቱ::
  1. በጋምቤላ በአኟኮች ላይ እ.ኤ.አ በዲሴምበር 13/2003 በጋምቤላ ከተማ የተደረገው የጅምላ ግድያ/Gonocide/ 424 ስዎችን በጅምላ በመግደል ታሪክ የማይረሳው የመንግስት ሽብር የተፈጸመ ሲሆን ብዙዎችም አገራቸውን ጥለው እንዲሰደዱ ተደርገዋል፣የአኟክ ሴቶች በወታደሮች ተደፍረዋል፣በመቶዎች የሚቆጠሩ ቤቶች ወድመዋል፣የሚመገቡአቸው ምግቦችና የቤት እንሥሣቶችም እንዲወድሙ ተደርጓል።ይህ ሽብር  ህወሓት በዚህ ክልል ውስጥ ለመስፋፋት ብሎ በህዝብ ላይ የተፈጸመ ግልጽ ሽብር ነው።ለዚሀም ድምዳሜ ላይ ያደረሰኝ ጉዳይ አብዛኛው የጋምቤላ ሰፋፊ መሬቶች በህወሃቶችና የጥቅም ተጋሪዎቻቸው ቁጥጥር ውስጥ መሆኑና እየተበዘበዘ መሆኑ ነው። በዚሁ ክልል  ስለተፈጸመው ጅምላ ግድያና ህወሓት  በዚሁ ክልል ስለሚፈጽማቸው የሃብት ብዝበዛ ለማውቅ ከፈለጉ የአኟክ የፍትህ ካውንስልን ዌብ ሳይት “http://www.anuakjustice.org/”  ይመልከቱ።
  1. የሲዳማ ህዝቦች ሰላማዊ ጥያቄዎች በማንሳታቸው እና ህገ-መንግስታዊ መብቶቻቸውን ተግባራዊ ለማድረግ በመነሳታቸው ብቻ ከ 11 ዓመታት በፊት እ.ኤ.አ ሜይ 24/ 2002 በአዋሳና አካባቢው ከ100 በላይ የሲዳማ ተወላጆችን በጅምላ በመግደልና ከ250-300 የሚሆኑትን በማቁሰል የተፈጸመው ዘግናኝ ሽብር ለታሪክ የማይረሳና የህወሓትን ግልጽ ሽብርተኝነት የሚያሳይ ሌላው ሀቅ ነው። ለበለጠ መረጃ http://sidamaliberation-front.org/ ይመልከቱ።
  1. በኢትዮጵያ አቆጣጥር ከ1997 ዓ.ም ምርጫ በኃላ በህዝብ ምርጫ የተሸነፈው ህወሓት/ኢህአዴግ ከህጻናት እስከ አዋቂ በጠራራ ጸሃይ በመቶዎች የሚቆጠሩትን ንጹሃን ግንባር ግንባራቸውን ብሎ በመግደል፣ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩትን አካለ ስንኩል በማድረግ፣በሽዎች የሚቆጠሩትን ደግሞ በእሥር ቤቶች ውስጥ በማሰርና በማሰቃየት በኢትዮጵያ ህዝብና በዓለም ማህበረሰብ ፊት ግልጽ ሽብር የፈጸመ ቡድን መሆኑ የቅርብ ግዜ እውነታዎች ናቸው።
  1. በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ውስጥ በተወሰኑ በኦሮሞና በትግራይ ተማሪዎች መካከል በተደረግ ግጭት ግልጽ በሆነ መድሎና በማን አለብኝነት በኦሮሞ ተማሪዎች ላይ ከትምህርት ገበታቸው እንዲባረሩ ተወስኖ የነበረውን ውሳኔ ሰንመለከት እጅግ የሚያሳዝን ተግባር መሆኑና ድርጊቱ በአዲሱ ትውልድም ላይ የተቃጣ ሽብር ከመሆኑም በላይ ኢትዮጵያውያን በአገራችን በግልጽ መድሎ ውስጥ መሆናችንን ያሳያል።
  1. በኦሮሞ ህዝቦች ውስጥ የሚደረጉትን ትግሎች በሙሉ ከኦነግ ጋር በማያያዝ የኦሮሞ ህዝቦች በእስር ቤቶች ውስጥ እንዲማቅቁ መደረጉና አብዛኛው የአገሪቷ እስር ቤቶች ኦሮሚኛ የሚነገርባቸው እስከ መሆን መድረሳቸውን ከፖለቲከኞች አፍ መስማታችን እጅግ ከባድ ችግሮች በህዝቡ ላይ መኖራቸውንና በኦሮሞ ህዝብ ላይ ሽብር እየተፈጸመ መሆኑን ያሳየናል።
  1. ህወሓት/ኢህአዴግ ሊፈጽመው የሚፈልገውን ሽብር በሽብር ህግ ድጋፍ እንዲደረግለት በህዝቡ ሳይሆን ለህወሓት የብዝበዛና የጭቆና መሳሪያነት በሚያገለግለው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አማካኝነት አጽድቆ የሽብር ጥቃቱን እየፈጸመ ሲሆን በዚህ ጥቃትም ልዩ ልዩ አካላት የህወሓት የሽብር ጥቃት ስለባዎች ሆነዋል። በዚህም ውስጥ ጋዜጠኞች፣የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፣ የነጻነት ተማጋቾችና ልዩ ልዩ ግለሰቦች በሙሉ በዚሁ ጥቃት ውስጥ ወድቀዋል።

ከጋዜጠኞች መካከልም፡- ርዮት አለሙ፣ውብሸት ታዮ፣እስክንድር ነጋ፣ በተለያዩ ጊዜያት በፍርድ ቤት የሚመላለሰው ተመስገን ደሳልኝ እና ሌሎችም ከሃገር ውስጥ ፣ የስውዲን ጋዜጠኞች ጀሃን ፕርሰን/Johan person/ እና ማርቲን ሽብዮ/Martin Schibbye/ ከውጭ ይገኙባቸዋል።

ከፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላትም ውስጥ አንዱዓለም አራጌ ፣በቀለ ገርባ፣ኦርባና ሌሊሳና ሌሎች በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ በእሥር ቤቶች የሚማቅቁ ይጠቀሳሉ።

በተለይም ተዋቂ ጋዜጠኞችን በሽብርተኝነት ሰበብ አስሮ ሌሎች በአገራቸው በሚደረገው የነጻነት እንቅስቃሴ ላይ ምንም እንዳይናገሩ በማድረግ በነጻው ሚድያ ላይ ግልጽ የመንግስት ሽብር እንዳለ ሁሉም የሚያውቀውና እ. ኤ. አ ከ2007-2012 ድረስ ብቻ 49 የሚሆኑ ጋዜጠኞች በዚህ የህወሓት የሽብርተኝነትን ድርጊት በመፍራትና በግዳጅ ከሃገር መሰደዳቸውን ለጋዜጠኞች መብት የሚከራከረው ሲፒጄ/Commitee to Prtect Jornalists / በተለያዩ ጊዜያት ገልጸዋል፤በዚህም ምክንያት አገራችን ለጋዜጠኞች ህይወት አደገኛ አገር መሆናንና ከሱማሊያና ከኢራቅ ቀጥላ  ለጋዜጠኞች የስደት ምክንያት በመሆን ታዋቂ ሆናለች ።

  1. በተለያዩ ጊዜያት በአፋር፣በሶማሊያና በጋምቤላ ክልሎች የህወሓት የመሬት መስፋፋትን ተግባራዊ ለማድረግ በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ የእነዚህን ህዝቦች የመሬት ሃብት ተጠቃሚነትን በመንጠቅ የህወሓት የብዝበዛ ቡድን አባላትና ጀሌዎቻቸው በህዝቦች ህይወት ላይ ተደጋጋሚ አደጋ በመፍጠርና በማፈናቀል አስከፊ ተግባር እየተፈጸመ ያለው በዚሁ ተስፋፊ  የህወሓት/ኢህአዴግ ቡድን አሸባሪነት መሆኑም ሊሰመርበት ይገባል።
  1. በአማራ ተወላጆች ላይ ከደቡብ ከጉራፈርዳ፣ከቤንሻንጉል ጉምዝና ከሌሎችም ክልሎች በማፈናቀል፣መሬት በመንጠቅና በማሳደድ የዘር ማጽዳትን ተግባርን የሚያቅደው እራሱ ህወሓት መሆኑንና ከትግሉ ጀምሮ ይዞት የመጣው በማኔፌስቶውም ላይ በግልጽ ያስቀመጠውና እየተገበረ ያለው ተግባር ነዉ፤በዚህም ብዙ ጭቁን አማሮች የሚከላከልላቸው አጥተው የዚሁ የሽብር ጥቃት ሰለባ ሆነው ተቀምጠዋል።
  1. ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በተለይም ከአንድ ዓመት ወዲህ በሙስሊም ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ላይ የሚፈጸመው የአደባባይ ላይ ድብድባ፣እስራትና ግድያዎች የህወሓት/ኢህአዴግ ሌላው ህዝብን የማሽበር ተግባሩ አካል እንደሆነ ብዙዎች ይስማሙበታል።
  1.  በሃገር ውስጥ ባሉ ሰላማዊ ትግልን አማራጭ ትግል በማድረግና ህግን ተከትለው የሚታገሉትን የተቀዋሚ ፓርቲዎች አመራርና አባላት ላይም እየደረሰ ያለው ወከባና እንግልት ሰላማዊ ትግሉን እጅግ መራራ አድርጎታል፤ለዚህም ማስረጃ ይሆን ዘንድ በቅርቡ በሰማያዊ ፓርቲ ላይና በአንድነት ፓርቲዎች አመራሮችና አባላት ላይ እየደረሰ ያለው ግፍ ህወሓት/ኢህአዴግ በፍጹም ማን አለብኝነት መቀጠሉንና ሰላማዊ ትግሎችንም ጭምር ለማጥፋት መቀጠሉ ይህ ሥርዓት በግልጽ በመንግስታዊ ሽብርተኝነት መቀጠሉን ግልጽ አድርጎልናል።
  1. 3.   ህወሓት/ኢህአዴግ የሽብር ጥቃትን ለምን ይፈጽማል ?

ወሓት/ኢህአዴግ በየትኛውም የታሪክ አጋጣሚ ኢትዮጵያዊነትን የተላበሰና ለእውነተኛ ዲሞክራሲና ፍትህ የቆመ ቡድን ሳይሆን በጥቂቶች ጠባብና ዘረኞች የተዋቀረ የማፍያ ቡድን መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ያውቃል። የህወሓት ዓላማና ግብ በእርግጥም የነጻነትና የዲሞክራሲ ሳይሆን ጥቂቶች የአገሪቷን ወታደራዊ፣ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መዋቅሮችን በሙሉ ተቆጣጥረው ለዓመታት የተመኙትን የኢኮኖሚና የመሬት መስፋፋትን ዕውን ለማድረግ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ አካልና፤በኢትዮጵያ ህዝብ ደምና ሀብት ለመክበር በሚቋምጡና በሚተገብሩ የህወሓት መሪዎችና ጀሌዎቻቸው አማካኝነት ይህንን ስውር ተግባር ለማስፈጸም የሚፈጸም የሽብር ተግባር ነው።

የዚህን እውነታዎች ለማወቅ ለሚፈልጉ ሁሉ አሁን በተጨባጭ የሚታየውን እውነታን ማየት ይቻላል።አጠቃላይ የኢኮኖሚው ክፍል በሙሉ ማለት ይቻላል በህወሓት ቁጥጥር ስር መውደቁና፤ የወሓት የንግድ ድርጅቶች ሙሉውን የአገሪቷን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎችን በሙሉ ለመቆጣጠር ሩጫ ላይ መሆናቸውና፤ እነዚህን ሁኔታዎችን የሚያመቻቹ የመንግስት መዋቅሮች በእነዚሁ በህወሓት ሰዎች እጅ ቁጥጥር ስር መዉደቁ ግልጽ ማስረጃ ሆኖ ይገኛል፤ለምሳሌ ኢፈርት በሁሉም የአገሪቷ የንግድ ሴክተሮች ተጽዕኖን እንዲፈጥርና ሌሎችን ከገበያ ውጭ እንዲሆኑ የሚያደርገው እንቅስቃሴና በብሄራዊ ባንክ፣በግሙሩክ፣በአየር መንገድ፣በአገር ዉስጥ ገቢ መስሪያ ቤቶች፣በወታደራዊ ተቋማት፣በፖሊስና ደህንነት መስሪያ ቤቶች ተሰግስገው አገሪቷን ለመበዝበዝ የሚያስችሉአቸውን ሁኔታዎች በቁጥጥር ውስጥ ያስገቡ በመሆኑ፤ ይህንን ብዝበዛ የሚቃወምም ሆነ የሚነካ ሃይል በሙሉ የጥቅሞቹ ተቀናቃኝ አድርጎ በመቁጠሩና፤ ይህንን የህወሓትን ቡድን ስውር ዓላማን ለማስፈጸመ መንግስታዊ ሽብርን አንዱ አማራጭ አድርገው የያዙት መሆኑ፤ ህወሓትን የሚያሳስበው የፍትህና የዲሞክራሲ ጉዳይ ሳይሆን ይህንን የብዝበዛ መዋቅራቸውን የሚነካ ሃይል ሁሉ በአሸባሪነት በመፈረጅ የብዝበዛ ተግባራቸውን ከግብ ለማድረስ የመንግስት ሽብርተኝነትን  እያቀጣጠሉ መሆኑ ነው።

  1. የህወሓት/ ኢህአዴግ የሽብር ተግባራት በህዝቡ ላይ የፈጠራቸው ችግሮች ምንድን ናቸው ?

 

የህወሓት/ኢህአዴግ ቡድን በሚፈጥራቸው የሽብር ተግባራት የተነሱ በህዝቡና በአገሪቷ ላይ የፈጠሩት ተጽዕኖዎች የሚከተሉትን ያካትታሉ፡-

  1. በህዝቡ ላይ ፍርሃት መንገሱና በብዙዎች ላይ የስለልቦናም  ችግር ያስከተለ መሆኑ፤
  2. ስደትና በስደትም የተነሳ ወጣቶች በጎረቤት አገራትና በየበረሃው ለሞት መዳረጋቸው፤
  3. እስራትና ሞት፤
  4. ግልጽ የህወሓትንና የጥቅም ተጋሪዎቻቸውን ልዩ ልዩ ብዝበዛዎችን ከፍርሃት የተነሳ በዝምታ ማየት፤
  5. በህዝቡ ላይ ሰብዓዊ ጥሰቶች በብዛት እየተፈሰሙ መምጣታቸው፤
  6. የመሬትና የተፈጥሮ ሃብቶች ብዝበዛ መቀጠሉ፤
  7. የሃገሪቷ ሃብቶች በጥቂቶች እጅ እየወደቁ መምጣታቸው፤
  8. ህዝቡ መብቶቹን እንዳይጠይቅ መገደዱ፤
  9. የስራና የትምህርት እድሎች መድሎዎች መፈጠራቸው ይህንንም መድሎ በዝምታ ለመቀበል መገደድ፤
  10. የስራና የመኖሪያ ቦታዎች ችግር መፈጠሩ፤
  11. የሙስና መስፋፋት መባባሱ፤
  12. የህግ የበላይነት ቀርቶ የህግ  መድሎ መፈጠሩ፤
  13. ግልጽ የንግድና የስራ ቦታዎች መድሎ መኖሩ፤
  14. ህዝቡ ከተቀዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር እንዳይቀላቀልና መብቶቹን እንዳያስከብር መሆኑ፤
  15. በንሮ ውድነት መማቀቅ፤
  16. ህዝቡ በሃገሩ ላይ የበይ ተመልካች መሆኑ፤
  17. የንብረት መነጠቅ ችግሮች መደራረብና ሌሎችም:-

 

  1. 5.   ከፖለቲካ ፓርቲዎች ፣ከስቪክ ማህበራትና ከኢትዮጵያ ህዝብ አጠቃላይ ምን ይጠበቃል ?

ህወሓት/ኢህአዴግና የጥቅም ተጋሪዎቹ ይዘው የተነሱትን የኢኮኖሚ፣የንግድና የመሬት መስፋፋት ከግብ ለማድረስ በሚያደርጉት የብዝበዛና የዝርፊያ እንቅስያሴ ዉስጥ ማናቸውንም ሰላማዊና ህጋዊ ትግሎች ሳይቀሩ በሽብርተኝነት ሰበብ መግደል፣ማሰር፣ማሳደድ፣ማሸማቀቅና ማስፈራራት የህወሓት የየዕለት ተግባር ሆኗል። ይሁንና ይህንን ሁኔታ ለመለወጥ እራሳችን ለመታገል ካልቆረጥንና መሰዋዕትነትን ለመክፈል ካልተነሳን ችግሩ ማብቂያ እንደማይኖረው ሊሰመርበት ይገባል።

በሃገራችን ታሪክ ህዝብንና አገርን በማሽበር በኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን በዓለም የሽብርተኝነት መዛግብት ውስጥ የተመዘገበውን ይህንን ሽብርተኛን የህወሓትን ቡድን ከድርጊታቸው እንዲያቆሙ ማድረግ ወይም እራስን የመከላከል ተፈጥሮአዊና ህጋዊ መብቶችን ተጠቅሞ ወደ መከላከል መግባት፣ የህወሓት ፍጹም አምባገነንነት እንዲያበቃና የአገራችንና የህዝቦቻ ነጻነት እንዲረጋግጥ ማድረግ ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም።

በእርግጥም ህዝብን በማሸበር ህወሓት ለዓመታት በህዝቦች መብቶችና ህይወት ላይ የሚፈጽማቸው የሽብር ጥቃቶች እንዲያበቁ አስፈላጊዉ ሁሉ ባለመደረጉ ዛሬ ህዝባችን በመከራ ውስጥ መሆኑ ለሁሉም የተሰወረ አይደለም።ትግሉ አሁን የመንግስት ስልጣን ይዘው በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ግፍን ከሚፈጽሙ የመንግስት ሽብርተኞች ጋር እንጂ ከህገ መንግስት ጋር አይደለም፤ህግ በትክክል እየተጣሰ ያለው በእነዚህ እኩይ ተግባርን በሚፈጽሙ የህወሓት/ኢህአዴግ በዝባዥ ሥርዓትና የሥርዓቱ መሪዎች ነው፤ ይህንን አስከፊ ሥርዓት ለማስወገድ መነሳት፣ መታገልና አስፈላጊውን መስዋዕትነት ከፍሎ በድል ማጠናቅቀ ጊዜ የሚሰጠው ጉዳይ አይደለም።

 

በሃገራችን የበይ ተመልካች ሆነን መቀጠል ያብቃ፤ጥቂቶች ብዙሃኑን የሚዘርፉበትና የሚጨቁንበት ሊያበቃ ይገባል፤የተወለድንባቸውና ያደግንባቸው ቦታዎች የራሳችን እስር ቤቶች ሊሆኑ አይገባም፤ወታደሩ፣ፖሊሱና የደህንነት ሀይሉ ኢትዮጵያውያንን የሚወክል መሆን ይኖርበታል እንጂ ለጥቂት ዘረኞች ቅጥረኛ ሆኖ የሚያገለገለበት ጊዜ ሊያበቃ ይገባል።

 

ህወሓት/ኢህአዴግን መታገልና ማስወገድ የተቀዋሚ ፓርቲዎች፣የስቪክ ማህበራት፣ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎችና ለእውነት የቆሙ ጋዜጠኞች ብቻ ሳይሆን የሁሉም ኢትዮጵያዊ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ ሁሉ  ትግል ሊሆን  ይገባል።

 

 

ለዚህም ይረዳ ዘንድ የሚከተሉት ሁኔታዎችን ማየት ይኖርብናል ብዮ አስባለሁ፡-

 

 

  1. ነጻነቱን የተነጠቀዉ ሁሉም መሆኑና ነጻነቱን ማስመለስ የሁሉም መሆኑ፤ ስለሆነም ትግሉም የሁሉንም ተሳትፎና መስዋዕትነትን የሚጠይቅ በመሆኑ ሁሉም በመረጠዉ የትግል መንገድ ወደ ትግሉ መቀላቀል ይጠበቅበታል።ድልን የሚጠብቅ ሁሉ የትግሉም አካል ሊሆን ይገባል፤
  2. የህዝቦች መቀራረብና በጋራ ጠላት ላይ የጋራ ትግልን ማፋጠን ለነገ የማይባል መሆኑ፤
  3. የተማሩና የህዝባቸው ሮሮ የሚሰማቸው ሁሉ ዛሬ ህዝቡ የሚፈልጋቸው በመሆኑ ያስተማራቸውን ህዝብ ለማገልግል የሚቆርጡበት ጊዜ መሆኑ፤
  4. የፖለቲካ ፓርቲዎች ልዩነቶችን በማጥበብና ለትዉልዱ በማሰብ በጋራ ጠላት ላይ በጋራ መነሳት መቻልና ለህዝቡ የትግል ፍላጎት መዳረሻ ሊሆኑና ሊያታግሉ ይገባል፤
  5. የስቪክ ማህበራትም ያላቸዉን ትስስር በማጠናከር ትግሉን ማገዝ ይኖርባቸዋል፤
  6. አዲሱ ትውልድም ለራሱ ሲል ወደ ትግሉ መቀላቀል ይኖርብታል፤
  7. በውጭ የሚገኙም የዚህን ዘረኛና አሸባሪ መንግስታዊ ቡድን ተግባር በማጋለጥና በዲፕሎማሲው ዘርፍ አስፈላጊውን እንቅስቃሴ በማድረግ ዕርቃኑን ማስቀረትና አገራትና መሪዎቻቸው ከተጨቆነው ህዝብ ጋር እንዲወግኑ ጥረት ማድረግ፤
  8. በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል፣ በስቪክ  ማህበራት መካከል፣ በሰብዓዊ ድርጅቶች መካከል በሃገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉት የእርስ በእርስ ግንኙነቱን በአህጉራት መካከልና በዓለም አቀፍ ደረጃ በማጠናከር የህወሓትን የመከፋፈል አቅምን መስበር መቻል፤
  9.  በውጭ ያሉ ምሁራንም የተለያዩ ሙያዊ ድጋፍ እንዲያደርጉ ማበረታታትና ተነሳሽነት መፍጠር፤
  10. የህወሓት የንግድ ድርጅቶች ምርቶችን ባለመግዛትና የንግድ አገልግሎቶቹን ባለመጠቀም ጭምር የህወሓትን የብዝበዛ መስመሮች መዝጋትና
  11. ልዩ ልዩ ትግሎችን  በሃገር ውስጥና በውጭ ማቀጣጠልና ተግባራዊ ማድረግ ግድ ይላል።

 

እነዚህንና ሌሎች ተግባራትን በመፈጸም ይህንን ሽብርተኛ ቡድን ከሃገራችንና ከህዝባችን ላይ ማንሳት ይጠበቅብናል።

 

 

  1. 6.  ማጠቃለያ

 

ከላይ ከተዘረዘሩትም ሆኑ ሌሎች በዚህ ጽሑፍ ካልተጠቀሱ የህወሓት/ኢህአዴግ ተግባራት ስንነሳ ግዜው መሰባሰባችንን ይጠይቃል። ከራሳችን ይልቅ ለደሃው ህዝባችን ልናስብና የመከራውን ግዜ ልናሳጥር የሚገባን ሰዓት ላይ ነው ያለነው፤ ስልሆነም አስፈላጊውን ሁሉ ማድረግ ይጠበቅበናል።

 

ህወሓት/ኢህአዴግ በሰላማዊ ትግል ላይ ባሉ የሰላማዊ ትግል አራማጅ ፓርቲዎች ላይም  ሳይቀር መንግስታዊ ሽብርን ቀጥል። ይህንን የፓርቲዎችን ትግል ማገዝና ችግራቸውን መጋራት ለነገ የሚባል ሳይሆን ዛሬ የሚተገበር ተግባር ነዉ። በሩቁ ሆኖ ፓርቲዎቹ ብቻቸውን እንዲታገሉ  መፈልግ ትግሉን ይጎዳዋል እንጂ አይጠቅመዉም፤ ስለሆነም ትግሎችን መደገፍና ከውጤት ላይ ማድረስ የሁሉም ተጠቂ ሁሉ ሃላፊነት ነው ።

 

በመጨረሻም አንድ ነገርን ሳልል አላልፍም ይኽውም ትግሎቻቸን ግቦቻቸውን እውን የሚያደርጉ ግለሰቦችን፣ ቡድኖችንና አስተሳሰቦችንና ፖሊሲዎቻቸውን ማየት ይኖርባቸዋል ፤ እነዚህም ቢሆኑ የብዙሃኑን ተሳትፎ ይጠይቃሉ ። ይኽንን ያልኩባቸው ምክንያቶችለመመልከት ያህል በዓለማችን እንደሚታየው አብዛኞች ትግሎች ግባቸውን እንዲስቱ የሚደረጉበት አጋጣሚዎች ተፈጥረዋል፤ ትግሎች በልዩ ልዩ ምክንያት በድሎቹ ዋዜማና አስቀድሞ የራሳቸው ስውር ግብ ባላቸው ግለሰቦችና ቡድኖች እጅ በመውደቃቸው ብዙ መስዋዕትነት የተከፈለባቸው ትግሎች ግቦቻቸውን እየሳቱ ሌሎች ትግሎችን የሚጠይቁበት ሁኔታዎች ታይተዋል።ለምሳሌም በሃገራችን የተደረጉት የተማሪዎች ትግል በደርግ እጅ መውደቅና የኢህአዴግ ትግል በጥቂቶች የህወሓቶች እጅ መውደቁ፣አሁን በአረቡ ዓለም የሚደረጉ ትግሎችንም ስንመለከት ደግሞ እንዲሁ ብዙ መስዋዕትነት ከተከፈለባቸው በኃላ ባልታሰቡና ወይም ያልተጠበቀ ግብ ባላቸው እጅ እየወደቁ ሌላ ተጨማሪ መከራን ሲፈጥሩ ተስተውላል፤ስልሆነም ትግሎች ግቦቻቸውን የሚተገብሩ ሰዎችንና ቡድኖችን ማንነት ማወቅ ይኖርባቸዋል ለዚህም የብዙሃኑ ተሳትፎዎች ወሳኝነት ይኖረቸዋል

 

 

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ።

 

 

 Pen-4

aberashiferaw.wordpress.com

ኤርትራን በአቋራጭ (ከኤፍሬም እሸቴ)

$
0
0

በሰሜን ምዕራቧ የአሜሪካ ከተማ በሲያትል ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን የሚርመሰመሱበት አንድ ሰፈር አለ። ንግድ ቤቶቹ፣ ጋራዦቹ፣ ሬስቶራንቶቹ እና እዚያ አካባቢ የሚቆሙት መኪናዎች አብዛኛው የኛ ሰዎች ንብረት ናቸው። ከመንገዱ አንዱ ኮርነር ላይ “ስታርባክስ” ቡናመጠጫ ደረቱን ሰጥቶ መንገዱን ቁልቁል ይመለከታል። ወደ ውስጥ ሲገባ አንዱ ጥግ “የኢትዮጵያውያን ጥግ” ነው፤ ሌላው ደግሞ “የኤርትራውያን ጥግ”።

 

አንድ ኢትዮጵያዊ ሲገባ እግሩ የሚመራው ወደራሱ አገር ጥግ ነው። መቀመጫ ባይኖርና በኤርትራው ጥግ በኩል ባዶ ቦታ ቢገኝ፣ ወደዚያ ለመሔድ አይሞክርም። ድንበር አይሻገርም። አንድ ኤርትራዊም እንዲሁ ወንበር ቢሞላበት ወደ ኢትዮጵያው ጥግ ለመሔድ አይሞክርም። ይህንን የሚነግረኝ ወዳጄ እየሳቀ ነው። ስታርባክሱ የባድመ ግንባር (ጦርነት የሌለበት፣ ነገር ግን ወታደሮቹ የተፋጠጡበት) አሊያም የአሰብ ቡሬ ግንባር መሰለኝ። ለመግባት አልፈለግኹም።

 

ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን በየሄዱበት ድንበርተኛ ሆነው መኖር ይፈልጋሉ ልበል? የተለያየን አገሮች ነን ብለው እንደሚለፍፉት ሳይሆን ተለያይተውና ተቆራርጠው ለመኖር አይፈልጉም።  ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ። የሚገርመው ግን ድንበርተኛ መሆን ሲፈልጉ ባድመ ግንባርንም አብረው እየገነቡ ነው። ጦራቸውን ሰድረው። የአበባ መስክ ያለበት ድንበር አይመቻቸውም – ሁለቱም። “አብረው ለመኖር የማይችሉ፣ ተለያይተው ለመኖርም የማይችሉ” የተባለው ለእነርሱ ሳይሆን አይቀርም። ይህንን የሚያፈርስ ገጠኤርትራን በአቋራጭ

መኝ ያገኘኹት ደግሞ ከሰሞኑ ወደ ሰሜን ካሊፎርኒያ ጠቅላይ ግዛት ሳን-ሖዜ ከተማ በሔድኩበት ወቅት ነውና ገጠመኙን በደስታ (ከልቤ ደስስስስ እያለኝ) ላጫውታችሁ።

 

በሰሜን አሜሪካ የተለያዩ ስብብሰቦች አሉ። ከሰፈር ልጅና ዕድር ጉባኤ እስከ ሃይማኖትና ፖለቲካ፣ ከብሔረሰብ ስብስብ እስከ ስፖርት ቡድኖች ድረስ። ከነዚህ ውስጥ በአሜሪካ የሚገኙ ወጣቶች ያቋቋሙትና ባለፈው ሳምንት 13ኛ ዓመቱን ያከበረው “የሰሜን አሜሪካ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጉባኤ” አንዱ ነው። ከመላው አገሪቱ የሚሰባሰቡ ወጣቶች የሚካፈሉበት የሦስት ቀናት ኮንፈረንስ አካሂዷል።

 

ዝግጅቱን ያዘጋጁት በሳንሆዜ እና በአካባቢው የሚገኙ ወጣቶች እና እነርሱ የሚያገለግሉባቸው አብያተ ክርስቲያናት ናቸው። ኋላ ግን እንደሰማኹት ዝግጅቱን አብረው ያከናወኑት ከሳንሆዜ ወጣ ብለው ከሚገኙት ከተሞች (ለምሳሌ ከኦክላንድ) የመጡ ኤርትራውያን ወጣቶች ጭምር መሆናቸውን ተረዳኹ። ለካስ አለማወቄ ነው እንጂ እዚያው አብረውኝ ከሚውሉት መካከል አንዳንዶቹ ኤርትራውያን ነበሩ። አንዱ ወጣት መልከ መልካም ልጅ ራሱን አስተዋውቆ እስኪነግረኝ ድረስ አላወቅኹም ነበር።

 

አማርኛው ለክፉ አይሰጥም። በእጁ የያዘው መጽሐፍ የአማርኛ ነው።

“የት ለመድክ አማርኛ” አልኩት።

“እዚሁ ነው የለመድኩ”።

“ስንት ጊዜ ፈጀብህ?”

“አንድ ስድስቲ ምናምን ወር ይሆናል”።

 

ዲያቆን ነው። የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ይማር ነበረው ከአንድ ኢትዮጵያዊ መሪጌታ ኖሯል። እሳቸውን ሁል ጊዜ “ደህና ነሽ” ይላቸው እንደነበር “ነሽ ለሴት፣ ነህ ለወንድ” እያሉ እንደሚያርሙት እየሳቀ ነገረኝ። ገና ለጋ ወጣት። 19 ዓመቱ ነው። በዚህ ዓመት የመጀመሪያ ዓመት ትምህርቱን ተከታትሏል። ወደ ሁለተኛው ተሸጋግሯል። በዕድሜ እኩያ ከሚሆኑት ኢትዮጵያውያኑ ጋር ቶሎ ተላምዷል። ወጣት አይደል?

 

ሌላው ወጣት ወደ ሃያዎቹ አጋማሽ ነው። እዚሁ አሜሪካ ያደገ ሳይሆን የስደትን መከራ ቀምሶ የመጣ ስክን ያለ ልጅ ነው። እንደ ሌሎቹ ስደተኛ ወገኖቹ በሱዳንና የመን አልተጓዘም። በከባዱ የኢትዮ-ኤርትራ ድንበር አልፎ ኢትዮጵያ በሰላም ለመግባት የቻለ “ዕድለኛ ልጅ”። ቃሉን ተውሼ እንጂ “ዕድለኛ ልጅ” ያለው ራሱ ነው። አማርኛ ጥሩ አድርጎ ይናገራል። “መጻፍ ነው ችግሬ”  ብሎኛል። ታሪኩ ደግሞ ልብ ይነካል።

 

ወጣቱ ብሔራዊ ውትድርናውን ጨርሷል። ከአንዱ የጦር ግንባር ወደ ሌላው ጦር ግንባር ሲዟዟር አሳልፏል። ጦርነት ባይኖርም። “ዓይንህን ለአፍታ እንኳን ከምሽጉ እንድትነቅል አይፈቀድም” ብሎኛል። “አንድ ቦታ አያስቆዩንም። መቀያየር ነው። አንዴ ቡሬ፣ አንድ ባድመ፣ አንዴ ….”። ከዚያ ሲመርረው አገሩን ጥሎ ለመሰደድ ወሰነ።

 

“አገሩ ውስጥ ወጣት የሚባል የለም’ኮ። አንድ ልጅ 16፤ 17፣ 18 ዓመት ከሆነ የሚያስበው መጥፋት ነው። አባት ከሆንክ ግን የት ትሔዳለህ። መማረር ብቻ። ሰዉ አይናገርም። ዝ…..ም ብቻ”። (‘ም’ን ላላ አድርጎ እየጠራት።)

 

ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ ሽሬ አካባቢ ወደሚገኝ የስደተኞች ካምፕ እንዲገባ ተደረገ። እርሱ ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ብዙ የአገሩ ሰዎች ጋር። ለአራት ዓመታት ኖረ።

 

“ምን ታደርግ ነበር?” ጠየቁት።

“ለእኔ ስኮላርሺፕ ማለት ነበር። አማርኛ ተማርኩ። መጻሕፍት ማንበብ ቻልኩ። የሚገርምህ ወደ አሜሪካ ስመጣ ሻንጣዬ 50ኪሎ ይመዝናል። 48ቱ ኪሎ መጽሐፍ ነው።”

“ሌሎቹስ ጓደኞችህ ምን ይሠሩ ነበር?”

“ሌሎቹም ዝም ብለው አልተቀመጡም። ቅኔ፣ ዜማ፣ መጻሕፍት ለመማር ወደ ጎጃም፣ ወደ ጎንደር፣ ወደ ሸዋ ሄዱ።”

“ኢትዮጵያ መጥተህ አታውቅም አይደል ከዚያ በፊት?”

“አላውቅም። ናጽነት ከመጣ በኋላ ደግሞ ችግር ሆነ። ኢትዮጵያ ማለት ሰይጣን ማለት ነበር የሚመስለኝ።”

ገታ አደረገና አንገቱን ነቀነቀ። እኔም “ለምን እንደዛ አሰብክ ምናምን” ወደሚል ጥያቄ ውስጥ መግባት አልፈለግኹም። ከሚናገረው ይልቅ በአካላዊ እንቅስቃሴው የሚያሳየው ብዙ ይናገር ነበር።

 

ወጋችንን ሳናጠናቅቅ የራት ሰዓት ደረሰና ወደ ማዕዱ ታደምን። ቀስ በቀስ ጠረጴዛችን ሞላች። ሁሉም ኤርትራውያን ናቸው። ወንዶችም ሴቶችም። ገና ወጣቶች። ሁሉም አማርኛ ይሰማሉ፣ ይናገራሉ። የተማሩት ግን በቅርብ ነው። አንዲቱ ልጅ ብቻ ገና አማርኛ አልተማረችም። አንዱ ኢትዮጵያዊ እየሳቀ “ጆሮሽን ቢቆርጡሽ አትሰሚም ማለት ነው?” አላት። ሌሎቹ የአገሯ ልጆች ሳቁ። ትርጉሙ ሲነገራት እሷም ሳቀች። የዛሬ ዓመት እሷም አማርኛ የምትችል ይመስለኛል።

 

“አማርኛ መማር ይሄን ያህል ቀላል ነው ማለት ነው?” አልኳቸው። አዎንታዊ መልስ አገኘኹ። በውስጤ “ለምን ትግርኛ አልተማርኩም ነበር? የመማር ዕድል ነበረኝ? ልማረው የምችለው ሌላ የአገራችን ቋንቋ  ነበር?” እያልኩ አሰላሰልኩ።

 

“አስመራ፤ ቤት ሙዚቃ ውስጥ አማርኛ ዘፈን እኮ መክፈት አይቻልም” አለኝ ቅድም ታሪኩን ያጫወተኝ ልጅ። ለካስ ክልከላው ጠንከር ያለ ኖሯል። ግን አልሰራም። ወጣቶቹ የፖለቲካ ድንበርን በፍቅር እየተሻገሩት ነው። ለብዙ ዘመናት ሲዘራ የነበረው የጥላቻ ዘር በጥቂት ግንኙነቶች ሲመክን ማየት እጅግ ያስደስታል። ወጣቱ በትግራይ ስላጋጠመው መልካም ነገር ሁሉ ተናግሮ አይበቃውም።

 

“አዲስ አበባ የቆየኹት አንድ ሳምንት ብቻ ነው። አሜሪካ ልመጣ ስል።” . . . ትንሽ ቆየት ብሎ ቢያየው ተመኘኹ። አዲስ አበባ የብሔረሰቦች ሁሉ መናኸሪያ፣ የኢትዮጵያዊነት ናሙና ማሳያ። ክትፎውን ቢበላ፣ ጠጁን ቢጠጣ፣ ከወያላው ጋር ቢላከፍ፣ ቆጮውን ቢሞክር፣ ቡላውን፣ ጨጨብሳውን፣ ዶሮ ወጡን …። “አብሮ የበላን ቅዱስ ዮሐንስ አይሽረውም” ይሉ የለ አባቶቻችን?

 

የሄድንበት ኮንፍረንስ እሑድ ማታ ሲጠናቀቅ ከሲያትል በመጡ ወጣቶች እና በሳንሆዜ አካባቢ በሚገኙበት መካከል ትልቅ የጨረታ ፉክክር ተጀምሮ ነበር። የሳንሆዜዎቹ ቁጥራቸው አነስተኛ በመሆኑ ውድድሩ ሲከብዳቸው ኤርትራውያኑ ወጣቶች ያግዟቸው ጀመር። በዚያ ውስጥ የምመለከተው የተለያዩና ለጦርነት የሚፈላለጉ ድንበርተኛ አገሮች ሳይሆን ወጣትነትና ፍቅር ያስተሳሰራቸው ፍጡራንን ነበር። ጠቢቡ ሰሎሞን እንዳለው ሆነ፤ “የጐመን ወጥ በፍቅር መብላት የሰባ ፍሪዳን ጥል ባለበት ዘንድ ከመብላት ይሻላል።” (መጽሐፈ ምሳሌ 15፥17)

Moving-picture-Ethiopia-flag-flapping-on-pole-with-name-animated-gif

ይቆየን – ያቆየን

ምን;፤ ፤ አለ;; ? ሕዝቡ;; ምን፤ ፤አለ ? (በ ሎሚ ተራ)

$
0
0

(በ ሎሚ ተራ)

“”አግሬን ለሰው ;;—– አግሬን ለሰው;;፦—– አልሰጥም አለ።
ከሻአቢያ ጋር ለሚያብረው ጦር,,—–አልከትም አለ። 
ባገሬ—-መሬት,,—የሰላሙ—-ትግል——ይፋፋም  አለ።!!””

          እንኳን ለአዲሱ አመት አደረሣችሁ፤! ! ! ! መጪው አመት ወያኔን የምንገላገልበት፤።  ከሻአቢያ ጋር ያበሩትና  ለማበር ያኮበኮቡት ሁሉ ልቦና የሚገዙበት ፤። ከሁሉ በላይ በሀገር ወሰጥ ሀይላችውንና ጉልበታችውን፤  እውቀታችውንና ጥሪታቸውን ሳይቀር በማሰባሰብ ፊት ለፊት ከወያኔ ጋር ጉሮሮ ለጉሮሮ በመተናነቅ ላይ ላሉት ታጋይ የፖሎቲካ ድርጅቶች፤ በእሰር ላይ ለሚማቅቁት ቆራጥ ታጋዮች፤ እንዲሁም ለሰፊው የ ኢትዮጲያ ሕዝብ አምላካችን ጉልበትና ብርታት ይሁናችሁ። እሱ  ይታደጋችሁ ። ይከተላችሁም።… ለድልም ያብቃችሁ።

በዬ መጣጥፌን መጀመሩ ሳይበጀኝ አይቀርምና ፤እንዲህ በሚል መዘሙር እየዘምርኩ ወደሚክተለው መልክቴ አልፋለሁ።   እንዲህ-፤ “”  በአዲሰ ዘምን ;;;;;;አዲሰ ነግር፤ ;;;; የ ኢትዮጲያ ;;;; ሕዝብ ;;;;;;፤እንዲከበር””። ይኸንን ከላይ የሞከርኩትን አገራዊ ወኔ ቀሰቃሽ ፉከራና ዝማሬ ለመግብያ ያኸል የተጠቀምኩት ዝም ብዬ አይደለም።  ከዚኸ ቀደም ብዬ ለንባብ ባቀረብኩት ጽሁፍ፤ “በየቀኑ ከመሞት አንዴ መሞት አይሻልም??” በሚል ያለፉትን የትግል ይዘት በተመለክተና በ አሁኑ ወቅት ላገራችን የሚያሰፈልጋት ምን አይነት የትግል አቋም እንደሆነ ለማመላከት በቀጥተኛ ቋንቋ በመጠቀም የግል እይታዬን በ አጭር ቃል አሰቀምጫለሁ።”” ዝርዘር ኪሰ ይቀዳል እንዲሉ፤”።

ታዲያ በርካታዎች የምሰጋና፤ በርካታዎችም በግል ኢሜል መልዕከት በመላክ፤ የተለመደውን የሰድብና የነቀፌታ ውርጀብኛ እንደ ዶፍ አውርደውታል። አኔም አንድቀን ይህንኑ የሰድብ ውርጅብኛ ከነመረጃው ለጽሁፍ እሰካበቃው እንዲታገሱኝ ከመማጽን በሰተቀር እንደ ተሳዳቢዎቹ ወርጄ የሰድብ መልሰ ምት፤ እንደማልሰጥ ቃል ከራሴ ጋር በመግባት፤ ሰለሃገሬ ግን ቢያንሰ የሚገባኝንና በተጨባጭ የተረዳሁትን እውነታ በምችለው ሁሉ ከማቅረብ  እንደማልቦዝን በድጋሚ ቃል እገባለሁ።

እኚህ ኮነሬል መንግሰቱ ሃይለማሪያም እንኳ አቢዮቱን ባፋፋሙበት ወቅት እንዲህ ብለው ነበር ;እንዲህ፤-

“”ሻአቢያ የሚባል ባልኖረ ወያኔ የሚባል ባልተፈጠረ ነበር ያሉት። “”

እውነት ብለዋል። ዛሬ ወያኔን አሽሞንሙኖና በአንቀልባ አዝሎ ኢትዮጲያዊያንን ለሰደትና ለመከራ  ምድሪቷን ለውጭ ዜጎች መፈንጫ የዳረገውን ወያኔን የፈበረከልን ማን እንደሆነ እያወቅንና ታላላቅ የሀገር መከታ የሆኑትን በርካታ የጦር መሪና አዛዦችን ውጦ ከሰቀረው ሻአቢያ ጎን ተሰልፍን ልንታገል ቆርጠናል፤።  ምሁራኖችም ጫካ ገብተዋል። ሌላ በርካታዎችም በተጠንቀቅ ላይናችው። የሚለውን መልዕክት ባደባባይ ማሰተጋባት ግን ምን ያኸል ታማኝነት እና ተቀባይነት እንደሚኖረው ጫካ የገቡት ምሁራኖች አንዴ ገብተዋልና እነሱን ከጫካ የምሁርነት ገለጻ አደርጉልኝ ብዬ አልጠይቅም። ሆኖም ለነሱ እንደሌሎቹ ቀልጠው እንዳይቀሩ ወገኖቼ ናችውና መጸለዬን አላቋርጥም።

እባካችሁ ከሰሜታዊነትና ከድርጅት አፍቃሪነት ወጣ ብለን በጽሞና እና በቅን ኢትዬጲያዊነት መንፈሰ  ጉዳዩን አንመርምረው  ? ?  አሁንም እየከነከነኝ ያለው ነገር ለምን ድርጅቶች ወያኔን ለመጣል ጦር አነሱ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ። ነገር ግን ፤እንዴት ሆኖ ነው ? ሻአቢያ ለኢትዮጲያ አንድነት መጠናቀርና ወያኔ እንዲወገድ ትብብር የሚያደረገው? ? እሰቲ  ወደሆላ ተመለሱና፤ ሰንቶቹ የወያኔ መሪዎች የ ኤርትራ ተወላጆች፤ ሰንቶቹ ደግሞ የትግራይ ተወላጅ እንደሆኑ ፋይል አገላብጡ። በተጨማሪም፤—

በ 22 ቱ አምት የመከራ ዘመን ባለ እራዕዩ  መሪ (ድንቄም)  ምን ያኸል ለኤርትራ ተቆርቋሪ እንደነበሩና እንዴትም አይነት ደባ ተሰርቶ ኤርትራ እንደተገነጠለች እንደገና የ ክቡር Colonel Goshu Wolde – Historical Speech –( On the fate of Ethiopia and Eritrea’s Referendum) ይመልከቱ ። የማይዘነጋውን የባድሜ ጦርነትንም በጥንቃቄ መርምሩ፤ የተደረገው ግፍ እኮ እንዲህ በቀላሉና በግርግር መታለፍ ያለበት አይደለም፡።  ይኽንን ሁሉ የፈጠጠ ጉድ እያየን አሜን ብላችሁ ተቀበሉ። ብሎ አቤቱታ ማብዛት ተገቢ ነው ትላላችሁ? እንደ ዜጋሰ እንዲሕ አይነቱን ጉዳይ በጥሞና መመርመርና ማጤን አይገባም ትላላችሁ? መንግሰቱ ሐይለማሪያም ሐይለሰላሴን ከሰልጣን እንዲወረዱ ሲያደርግ የሕዝብ ድጋፍ ነበረው፤። መጨረሻው ባያምርም።

ወያኔ አገር ሲቆጣጠር ግን የሕዘብ ድጋፍ ሳይሆን የሻቢያና የ ዌሰተርን ባንዳዎች ድጋፍ ብቻ ነበር የነበረው፤ አሁንሰ የሕዘብ ድጋፍ አለው እንዴ ? መልሱን መቼ አጣችሁት። የሱ ደጋፊ አሁንም ሆድ አደሮቹና አሰመሳዬቹ ሻአቢያዎች ናቸው። የተከበራችሁ ኢትዮጲያዊያን ወገኖቼ ሆይ ገና የተደገሰልን ድግሰ እንዲህ በቀላሉ አውረተን የምንዘልቀው እንዳልሆነ     ግን አንድ ነገር እርግጠኛ እንሁን። በጦሩ ውሰጥ የነበሩትን እውነተኛ ላገራችውና ለሕዘባቸው ተቆርቋሪዎቹን ወያኔ በሰመ ባድሜ ጦርነት ብሎ ከሻአቢያ ጋር ተመሳጥሮ በግፍ ከፊት እንዲሰለፉና እንዲማገዱ አደረጋቸው። እረ ሰንቱ።

ወገኖቼ ፤ መርሳት የሌለብን በተለያዩ አገሮች በተደረጉ ትግሎች በአገር እውሰጥ እየሞቱና እየታሰሩ በዙ መከራና ሰቃይም ደርሦባቸው እኔ መሰዋእት ሆኜ ቀሪው ትውልድ ነጻነቱን ያግኝ በሚል ንጽሁ የዜግነት መንፈሰ መሰዋት ሆነው ነው በመጨረሻ ነጻነት ያገኙት። ለምሳሌ የ ሳውዝ አፍሪካን  አፓርታይዱን ሥርአት ለ ናሙና ማንሳት እንችላለን የማነዴላን እና በርካታ አገር ወዳድ ዜጎች መሰዋትንት። ሌላኛው ደግሞ በቅርቡ 50 አመቱን ያከበረው አሜሪካዊው ማርቲን ሉተር ኪነግ ነው።

እኔ በበኩሌ ወያኔ ፈራርሦ ያበቃለት ሥርአት ነው። የሚወድቀውም እሰካሁንም ባገር ውሰጥ በቆራጥነት በመታገል እንደነ ማንዴላና ማርቲን ሉተር ኪንግ በሰላሙ ትግል ፍዳውን ያሰቆጠሩት ቆራጥ ኢትዬጲያዊያን ማንዴላዎችና ማርቲን ሉተር ኪንጎች ናቸው። ይልቁኑ ይኸንኑ ያገር ውሰጥን ትግል በሙሉ ሃይላችን በመደገፍና በማበረታታት የወያኔን ክርሰ መቃብር ማቅረብ እንጂ እንደገና ወያኔ እንዲንሰራራ ከሻአቢያ ጋራ መወገን መፍትሄ ነው ብዬ አላምንምና መላው አንባቢያንን አንዲሁም በሻቢያ ደጋፊነት ወያኔን እንጥላለን ብለው ለሚያምኑ ድርጅቶችም ጭምር የምማጸነው ቆም ብለው እርምጃቸውን እንዲመረምሩ ብቻ ነው።

 

እውንቱ እኮ የኢትዮጲያዊያን አንድነትጠንክሮ ወያኔ ከተወገደ ወዲያ ኢትዮጲያዊነት ለምልሞ ዲሞክራሲ ሰፍኖ እትዮጲያ ያለባሕር በር ትቀመጥ የሚል እትዮጲያዊ ይኖራል ትላላችሁ? ? አይመሰለኝም። ታዲያ በዚህ መንገድ ዳር ድንበራችን ቀይባሕር አይመሰላችሁም ? ? ይህንን ደገሞ ወያኔም ሻአቢያም ጠንቅቆ ያውቀዋል ። ታዲያ በዚህ ሂሳብ እንዴት ሆኖ ነው ወያኔ ደጋፊና ተባባሪ የሚሆነው ተላላችሁ ? ወይሰ የኔ ሂሣብ የተሳሳተ ነው ? ? መልሱን እናንተው መልሱ። እግዚ አብሔርም ማሰተዋልን ይሰጠን እያልኩ ያዲሰ አምት ምኞት መግለጫዬን በዚሁ እደመድማለሁ። በቸር ይግጠመን ቸር ወሬም ያሰማን። !!

 

ኢትዮጲያና ኢትዬጲያዊነት ለዘላለም ይኖራል። ወያኔ ግን በተባበረ የ ኢትዮጲያዊያን ጠንካራ ክንድ ይወገዳል!!

 2005-kinijit-demonstration-picture

 

የመጨረሻው ኑዛዜ –በልጅግ ዓሊ

$
0
0

አርባ ቀኔ ሆነ ከተለየኋችሁ፣
ድምጼን ከሰማችሁ ዓይኔንም ካያችሁ፣
ከጠየቃችሁኝ ካነጋገርኳችሁ፣
አርባ ቀኔ ሆነ ከሄድኩኝ ትቻችሁ።

 

ምን አደረጋችሁ እኔ ከተለየሁ፣
ጉልበቴ ከከዳኝ ትንፋሼንም ካጣሁ፣
ዝናብ ካረጠበኝ፣
ፀሐይም ከመታኝ ፣
ከተለየኋችሁ አርባ ቀኔ ሆነኝ ።

ለአርባው ፍትሃት በሚዘጋጀው ዝግጅት ላይ ውድ ባለቤቱ እንድታነብለት ያሰበውን ግጥም የመጀመሪያውን ክፍል ጽፎ አረፍ አለ። አልጋ ውስጥ ሆኖ ሰው ያለ አይመስልም። ስጋው ከላዩ አልቆ አጥንቱ ብቻ ቀርቷል። ፈገግታው ግን ያው ነው። አንዳንዴ ሃሳብ ይዞት ጭልጥ ይላል። ምን እያሰበ ይሆን ? ባለፈው ወር ዶክተሩ ነቀርሳ(ካንሰር) እንዳለበት ሲነግረው ምንም የመደንገጥ ሁኔታ አላሳየም። እንዲያውም በደስታ ነው የተቀበለው። ለነቀርሳ የሚሆነውን መዳህኒት ትጀምራለህ ሲባል ሳያቅማማ ነበር እሺ ያለው። መዳህኒቱ ጎፈሬ የነበረውን ጸጉሩን መድምዶ ባዶ ራስ አድርጎታል። ፊቱን በመስታወት ሲመለከተው “ጣዕረ ሞት መስያለሁ አይደለም እንዴ ?” ብሎ ራሱን ጠየቀ። መልስም ሳይጠብቅ  በፈገግታ አለፈው። ተመልሶ ያወጣና ያወርድ ጀመር።

እንዴት ሕይወት አጭር ናት? ያሳለፈው የሕይወት ዘመኑ በሙሉ መጥቶ ድቅን አለበት። ዓይኑን ጨፍኖ ወደ የወጣትነት ሕይወቱ ነጎደ። የአደገበት ቄዬ ሁሉ ትዝ አለው። ሀ . . . ሁ  ያስቆጠሩት ቄስ አሰባቸው። አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቱን አስታወሰ። ሁለተኛ ደረጃ ላይ ሲደርስ ሁሉም ነገር ትዝ አለው። ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሳለ ነበር ከኢሕአፓ የተዋወቀው። አስራ አንደኛ ክፍል . . . ።  ጓደኞቹ ሁሉ ወደ የኢሕአፓ፣የወጣቶች ክንፍ  ኢሕአወሊ (የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ወጣቶች ሊግ) ገብተው ነበር። ይህ ጭቁን ሕዝብ፣  ይህ ደሃ ገበሬ ከጭቆና ነፃ መሆን አለበት ብለው አስረዱት። በመጀመሪያ በወጣት ማኅበር መሳተፍ ጀመረ። እያደር እየገባበት ሄደ። የኢሕአፓ የወጣቶች ክንፍ(ኢሕአወሊ) ውስጥ አባል ሆነ። አንድ ላይ ሆነው  ትግላቸውን ቀጠሉ። ቀይ ሽብር ተጀመረ። በመጀመሪያ ብዙዎቹ ታሰሩ። ጓደኞቹ እስር ቤት ሆነው መልዕክት ላኩበት ። “ከሐረር ጥፋ። በጣም እየፈለጉህ ነው ። የት እንዳለህ አልነገርናቸውም። ግን አንተን ለማግኘት የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም ። ስለእኛ አታስብ። ነፍስህን አድን………….”

መልዕክቱን እንደሰማ እሱን ላለማገለጥ ብለው የተሰቃዩትን እያሰበ  ስቅስቅ ብሎ አለቀሰ። ። እጁን ሰጥቶ እነርሱን ለማዳን አሰበ። እጁን ቢሰጥም ልዩነት እንደሌለው ተረዳው። ሐረርን ለቆ ጉዞውን ቀጠለ። አዲስ ማንነት፣ አዲስ መታወቂያ፣ አዲስ የይለፍ ወረቀት ተዘጋጀለት። ወደ ሱማሌ . . . ። ያለመደው በረሃ እግሩን አቃጠለው። ውሃ ጥማቱ . . .  ረሃቡ . . .  ስቃዩ . . .  ሁሉም ያሳለፈው ችግር በሙሉ አሁን ትዝ አለው። “ያኔ ነበር መሞት የነበረብኝ” ብሎ አጉረመረመ። ወረቀቱን አንስቶ  ግጥሙን ቀጠለ።

ትንሽ ጊዜ ስጠኝ ትንሽም ታገሰኝ፣
ብዬ ብጠይቀው ሞት አልሰማህ አለኝ።

ትንሽ ጊዜ ቢያገኝ የሚሠራቸውን ማውጣት ማውረዱን ቀጠለ። ስለ እናት አባቱ ፣ ስለ ልጆቹ ያወጣና ያወርድ ጀመር። በሕይወት የመኖር ፍላጎቱ ጨመረ።  ምትን የለመደውን እንዲህ ብሎ ቋጠረው።

እናቴን ልቅበራት አባቴን ልቅበረው፣
ልጆቼን ላስመርቅ ብዬ ብማጸነው ፣
ሞት አልሰማህ አለኝ ምንም ብማለደው።

ሶማሌ ውስጥ  እያለ ብዙዎቹ ጓደኞቹ በቀይ ሽብር እንደተገደሉ ከሠፈሩ በቅርብ የተሰደደ አግኝቶ ነገረው።  ሰለ ጓዶቹ ሲያስብ እንባውን በጉንጮቹ ላይ አለማቋረጥ ይወርድ ጀመር። ሞታቸውን የሰማ ጊዜ ደጋግሞ ቃል የገባው ታወሰው። የጀመርነው ፍፃሜ ሳያገኝ ትግሉን አላቆምም ብሎ በእነርሱ ስም ምሎ የተገዘተው አይኑ ላይ ድቅን አለበት። ቃል የገባው ፍፃሜ ሳያገኝ  አልጋው ውስጥ ሆኖ ጉልበት አጥቶ ሞቱን በመጠበቅ ላይ በመሆኑ ምርር ብሎ አለቀሰ። “ወይ ነዶ . . . “ ብሎ በቀይ ሽብር ስለተሰውት ጓደኞቼ እያሰበ አጉረመረመ። “አዎ በቅርብ እንገናኛለን። ዶክተሩ እንደማልተርፍ ነግሮኛል ። እኔም ካሁን ወዲህ በዚህ ምድር ምንም የቀረኝ ነገር የለም። እንዲያውም ቶሎ ወደ እናንተ መጥቼ ባገኘኋችሁ” ብሎ ፈገግ አለ።

በሕይወት ውስጥ የደረሰበትንና የአከናወነውን አሰበ። ጓደኞቹን በሰማይ ቤት ሲያገኛቸው ምን እንደሚነግራቸው፣ ምን እንደሚደብቃቸው  ማውጣት ማውረድ ጀመረ። እነርሱ እኮ ይሄን ጊዜ ኢሕአፓ ስልጣን ላይ ወጥቶ፣ ሃገራችን ዴሞክራሲ የሰፈነባት አገር ሆናለች ብለው ይጠብቁ ይሆናል፣ እነርሱ እኮ ይሄኔ ኮምኒዝም ዓለምን የለወጣት ይመስላቸው ይሆናል፣ እነርሱ እኮ ዓለም የላብ አደሮች ሆናለች ብለው ያስቡ ይሆናል፣ እነርሱ እኮ የሃገራችን ገበሬ ያለፈለት ይመስላቸው ይሆናል . . እነርሱ እኮ ይሄኔ . . . .   ብዙ ነገር ያስቡ ይሆናል . . . ። ሃሳብ ይዞት ጭልጥ አለ።  ከቀብሩ በኋላ ምን እንደሚፈጠር አሰበ። እንደገና የጀመረውን ግጥም መጻፉን ቀጠለ።

ምን አዲስ ዜና አለ? ማንንስ አመመው?
ማንንስ ረዳችሁ አለ የቸገረው ?
ቃል ገብታችሁ ነበር የቀብሬ ለታ፣
ህልሜንስ ሰማችሁ በማንስ ተፈታ?

ወይስ

ሁሉም ተበተነ ሄደ ወደቤቱ፣
ወይስ ሃሳብ ገባው እሱም ስለሞቱ?
አርባ ቀኔ ሆነ እንግዲህ ከሄድኩኝ ፣
እቅፍ አድርጌአቸው ልጆቼን ከሳምኩኝ።
ስለሃገሬ ጉዳይ አንስቼ ካወጋሁ ፣
ስለ ልጆቼ መብት ከተከዝኩ ከሰጋሁ፣
ስለአንድነቷም ከጓዴ ካወራሁ፣
አርባ ቀኔ ሆነ ልሳኔንም ካጣሁ።

በጎኔ ከተኛሁ አርባ ቀኔ ሆነኝ፣
ጉልበቴ ከከዳኝ አፈር ከተጫነኝ፣
መኖርም ካቆምኩኝ ማለምም ከተውኩኝ፣
ብቻዬን ካደርኩኝ ዓይኔን ከገለጥኩኝ፣
የልጆቼንም ሳቅ ድምጽ ከሰማሁኝ።

እንደገና በኢሕአፓ ውስጥ የተደረጉትን ክፍፍሎች ያወጣና ያወርድ ጀመር። ጓደኞቹ በቀይ ሽብር የተገደሉት ገና የመጀመሪው ክፍፍል በኢሕአፓ ውስጥ  እንደተፈጠረ ነው። በውልም ለምን ክፍፍሉ እደተከሰተ ላያውቁ ይችላሉ። ከዛም በኋላ ስለተፈጠሩት ክፍፍሎች ማውጣትና ማውረድ . . .  ። ክፍፍል ሁል ጊዜም  ድርጅቱን የገደለ ጉዳይ ነው ብሎ ሃዘን ገባው። መቼ ይሆን ከዚህ የክፍፍል አባዜ የምንወጣው? ራሱን ጠየቀ። ብዙ ማድረግ የነበረበትን ሳያደርግ በመቅረቱ ሃዘን ገባው።   እንዲህ ብሎ ቋጠረው።

ጨክኜም አይደለ እኔ በልጆቼ፣
በእናቴ በአባቴ በእህት ወንድሞቼ፣
በዕድሜ ልክ ወዳጄ በትግል ጓዶቼ ፣
ከሞት ተደራደርኩ እንግዲህ ላንድ ዓመት፣
እንዲሰጠኝ ጊዜ የትም ላልሄድበት።

ከዛም ወደ ሰሜን አሜሪካ እንዴት እንደመጣና በሰሜን አሜሪካ እንደገና ፓርቲውን በሙሉ ልቡ ለመርዳት አብሮም ለመታገል እንደተቀላቀለ ታሰበው ። በተቻለው መጠን ደከመኝ ሳይል ይታገል ጀመር። በፓርቲው ውስጥ አዲስ ክፍፍል ተጀመረ።   አንደኛውን ክፍል ተቀላቀለ።  በተለይ የሚወዳቸው ጓዶቹ በሌላው ክፍል መሆናቸው አሳዘነው። ግን ምንም ማድረግ አልቻለም። . . .  ንዴት . . .ንዴት . . .  ለበሽታ ጣለው። አሁን ይኽው ሞቱን እየጠበቀ ነው። ምንም ድካም ቢሰማውም ያለውን ኋይል አጠራቅሞ  መጻፉን ቀጠለ። አንድ የመጨረሻ ኑዛዜ ለቀሪ ጓዶቹ ለመተው ሃሳብ መጣለት።

ውድ ጓዶች

ይህ የኑዛዜ ቃሌ ነው።  ለቤተሰቤ የማወርሰው ምንም ንብረት ስለሌለኝ ኑዛዜ አያስፈልገኝም። ገንዘቤም ንብረቴም  ብዬ ፍቅሬም ለድርጅቴ ሰጥቼ ከወጣትነት ዘመኔ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ደፋ ቀና ስል ያፈራሁት ንብረት የለኝም። ስለዚህ የንብረት ክፍፍል ኑዛዜ አይኖረኝም። ግን አንድ ትልቅ የአደራ ኑዛዜ አለብኝ።  መስራት የነበረብኝና ሳልሰራው ሞት የቀደመኝ ትልቅ ቁምነገር ስላለ ልናዘዘው አስብኩ። ይህን አደራዬን ከእኔ በኋላ በዚህ ምድር ለምትቀሩት ጓዶቼ በኑዛዜ መልክ አውርሻችሁ እሄዳለሁ ።

በቅርብ ጊዜ በተፈጠረው ልዩነት ምክንያት ኢሕአፓ ሁለት ስም ይዞ ይገኛል። ሁለት ዴሞክራሲያ፣ ሁለት ታሪክ ፣ ሁለት አመራር  . . .  ሁለት  . . .  መግለጫ . . .  ። በዚህም የተነሳ የድርጅቱ እውነተኛ ደጋፊዎች ከፓርቲው ርቀው ይገኛሉ። ብዙ በዚህ ፓርቲ እምነት የነበራቸው አባላት ተስፋቸውን ቆርጠዋል። አንዳንዶቹ አልፈው ተርፈው ጥላቻ ደረጃ ደርሰዋል ። ዛሬ በዚህ ኑዛዜዬ ይህ ነው ጥፋቱ፣ ይህ ነው ልማቱ ብዬ ማንንም ለመውቀስ አልፈልግም። ዛሬ የመጨረሻዬን እስትፋሴን በምጠብቅበት ወቅት ኢሕአፓ አንድ ሆኖ ተመልሶ ለማየት እግዜር ስላላበቃኝ አዝናለሁ። ዛሬ ፓርቲው አንድ ሆኖ ሳልመለከት መስዋትነት የከፈሉትን ጓዶችን በቅርብ እቀላቀላለ። ከተሰውት ጓዶች ጋር በሰማይ ቤት ስንገናኝ ጥያቄም እንደሚኖራቸው አስባለሁ። ፓርቲያችን ምን ደረሰ? ብለው እንደሚጠይቁኝ አምናለሁ። እስቲ ሁላችሁም በእኔ ቦታ ሆናችሁ መልሱን ፈልጉ። እንደኔ ጭንቀት እንደሚይዛችሁ አልጠራጠርም። እኔ ዛሬ ለእነርሱ መልስ የሚሆን ማግኘት አለብኝ። ዶክተሩ እንደነገረኝ በዚህ ምድር የቀሩኝ ቀናት ትንሽ ናቸው። ብዙዎቻችሁ በእኔ ቦታ ስላልሆናችሁ እንደኔ ላይጨንቃችሁ ይችላል። ምንአልባትም ስለዚህ ጉዳይ አታስቡ ይሆናል። ግን ደግሞ ይህ ድርጅት፣ የዚህ ድርጅት ዓላማ የሙታን አደራ ነውና ይህንን ካላሰብን ምኑን ሰው ሆነው? ዛሬ  ለእነርሱም ምን አድርገህ መጣህ ቢሉኝ ለመመለስ ይረዳኝ ዘንድ አንድ ኑዛዜ ለመጣል አሰብኩ።

በሕይወት እስካላችሁ ድረስ ፓርቲው አንድ የሚሆንበትን መንገድ ብቻ ፈልጉ፣ ታገሉ፣ በስሙ መስዋዕትነትን የከፈሉትን ልትታደርጉላቸው የምትችሉት በብስለት የተፈጠረውን ልዩነት ፈታችሁ ሃገራችሁ ወደ ነጻነት ጓዳና ልታደርሷት ትችላላችሁ ብዬ አምናለሁ።

ለእኔ ግን አንድ ቁም ነገር እንድታደርጉልኝ እጠይቃለሁ። በመቃብሬ ላይ የሁለቱም አመራር ተወካዮች እንዲገኙልኝ አድርጉልኝ። ምን አልባት መሣፈሪያ ችግር ካለ ካለኝ ትንሽ ገንዘብ ላይ ይሰጣቸው። ይህንን ከፈጸማችሁልኝ በሕይወት  ያልፈጸምኩትን  በመቃብሬ ላይ እንደፈፀምኩት እቆጥራለሁ። ለጓዶቼም ይህንን አድርጌ መጣሁ ማለት እችላለሁ። በዚሁ አጋጣሚ እኔም ከተሰውት ጋር ተቀላቅዬ ውጤቱን እጠብቃለሁ።

ሰላም ለእናንተ ይሁን ።
እንደምታቸንፉ አልጠራጠርም።
ኑዛዜውን ጽፎ ወደ ግጥሙ ተመለሰ።
ምንም እንኳን ቆሜ ባላጫውታችሁ፣
እጄንም ዘርግቼ ሰላም ባልላችሁ፣
አቅፌና ስሜ ከቤት ባልሸኛችሁ፣
አትርሱ ዓላማዬን ቃል እንደገባችሁ፣
አርባ ቀኔም ቢሆን ከተለየኋችሁ።

ግጥሙን ጨርሶ ጽፎ አጣጥፎ ካስቀመጠ በኋላ ሞቱን ይጠብቅ ጀመር ። ከትንሽ ቀናት በኋላ ሕይወቱ አለፈ። ቀብሩም በኑዛዜው መሠረት ከሁለቱም የኢሕአፓ አመራሮች ተገኝተው የቀበሩ ሥነሥርዓት ተፈጸመ። ዛሬ በሁሉም አባላት ላይ የሙት ኑዛዜ ጩኸት ይሰማል። ኑዛዜዬን የት አደረሳችሁት? ይላል።

እኛስ ይህንን የተሰው ጓዶችንን ጥያቄ ከምን አደረስነው?

ማሳሰቢያ ፡ – ይህ ጽሁፍ በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሠረተ ነው። ሌንጮ በሰሜን አሜሪካ ዳላስ ከተማ  ውስጥ ይኖር የነበረ ሲሆን ከመሞቱ በፊት ካደረገው ኑዛዜና በአርባው ላይ እንዲነበብለት ከጻፈው ግጥም በመነሳት በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሠረተ ልብ ወለድ ነው።

 

መስከረም ፩ ቀን ፪፼፮ ዓ.ም

ሎንዶን

Pen


ራዕይ ነበረው፣ ተቀጥሎበታልም።

$
0
0

ራዕይ ለበጎ ነገርና ራዕይ ለመጥፎ ነገር ብለን እንመልከት። የሀገር መሪዎች ለሀገራቸው በጎ ነገር ለመከወን መልካሙን ራዕይ ሰንቀው በመነሳት በኣካባቢያቸው ለተቀየሰው በጎ ነገር የመልካም ተግባር ራዕይ ያላቸውን ኣሽከሮቻቸውን ሳይሆን የሥራ ባልደረቦቻቸውን መርጠው በመያዝ ክንውኖቻቸውን ይቀጥላሉ። በተቃራኒው የቆሙ መሪዎች ደግሞ መጥፎውን ተግባሮቻቸውን ከሚመርጧቸው የሥራ ባልደረቦቻቸው ጋር በመሆን ይያያዙታል።

የትግራይ ሕዝብ ነፃ ኣውጪ ግንባር ቀንደኛ መሪ መለስ ዜናዊ ኣስረስ ኢትዮጵያን ለመበታተን፣ ለማፈራረስ፣ ለመቆራረስ፣ ኣሳልፎ ለመስጠት፣ ለማስማማትና ለመሸጥ ራዕይ ነበረው። ሲተገብር ነበር፣ ጀሌዎቹም እየተገበሩት ነው። መለስ ዜናዊ ኣስረስ ኢትዮጵያውያንን ለመግደል፣ ለማፈናቀል፣ እንደ ሸቀጥ ለመሸጥ ራዕይ ነበረው፣ በተግባር ኣሳይቷል። ያሰለጠናቸው ካድሬዎቹም በተተለመው መሠረት እንደሚተገብሩ ቃል ገብተው ትግበራውን ተያይዘውታል። መለስ ዜናዊ ኣስረስ ለኃያላን መንግሥታት ተላላኪ ለመሆን፣ ሀገሪቷን ከሳሎን እስከ ማዕድ ቤት ድረስ እንዲዝናኑበትና በዋናው በር ሰተት ብለው ግብተው በጓሮ በር እንዲወጡና ኣዛዥና ኣናዛዥ እንዲሆኑ ኣድርጓል፣ እያደረገም ነበር። ጀሌዎቹም ቀጥለውበታል። መለስ ዜናዊ ኣስረስ የሀገርን ሀብት መዝረፍ፣ መሸጥና ማስወሰድ ራዕዩ ስለነበር በተግባር ኣሳይቷል፣ በጀሌዎቹም ተቀጥሎበታል። መለስ ዜናዊ ኣስረስ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን ኣዋርዷል፡ ኣታሏል። መለስ ዜናዊ ኣስረስ ዘርን ለይቶ በማጥፋት ላይ በማተኮር በማምከን፣ በመግደል፣ በማፈናቀል፣ በበሽታ እንዲለከፉ በማድረግ፣ በማስራብ፣ በመሸጥ፣ በማባረርና እንዲሰደዱ በመገፋፋት ራዕዩን ተወጥቷል፣ ኣሁንም የርሱ ሥልጡኖች በመተግበር ላይ ናቸው።

meles

መለስ ዜናዊ ኣስረስ የትግራይ ሕዝብ ነፃ ኣውጪ ግንባር ቁንጮ መሪ በመሆን ድርጅቱን ለኣሥራ ሰባት ዓመታት እየጋለበ መጥቶ ሥልጣን ላይ ወጣ። ሥልጣን ለማግኘት ይደረግ በነበረው ፍልሚያ በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩ የትግራይ ወጣቶችን፣ የኢትዮጵያን ሕዝብ ኣንወጋም ያሉ የትግራይ ኣዛውንቶችን፣ በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ሠራዊትን ገድሏል፣ ኣስገድሏል። የሥልጣን ወንበሩ ላይ ፊጥ ካለ በኋላም ኢትዮጵያውንን ለሃያ ኣንድ ዓመታት ኣረመኔያዊ የኣገዛዝ ዱላውን እያሳፈረባቸው ገዛ። በዚህ በሠላሳ ስምንት የሥልጣን ዓመታት ኣንድም ቀን ለሀገርና ለወገን በጎ ነገር ሳይሠራ መላ ሰውነቱ በኢትዮጵያውያን ደም እንደተነከረ ድንገተኛ ሞት ወሰደው።

በዓለም ላይ የነበሩና ያሉም ኣምባገነን መሪዎች ለሥልጣናቸው ሲሉ ብዙ ወንጀሎችን ቢሠሩም ለሀገራቸው ግን በጎ ነገር ከመሥራት ኣይቆጠቡም። ሕዝባቸውንም ይወዳሉ። መለስ ዜናዊ ግን ኢትዮጵያንም ኢትዮጵያውያንንም ኣይወድም ነበር። ስለሆነም የመጥፎ ተግባር ራዕይ እንደ ነበረው በግልፅ ኣስመስክሮ ኣልፏል። በመሆኑም የርሱ ራዕይ የመጥፎ ድርጊት ተምሳሌት ሲሆን ጀሌ ተከታዮቹም የርሱን መጥፎ ራዕይ እንተገብራለን እያሉ በመፎከር ላይ ናቸው።

ግብፃውያን ንጉሦቻቸውን ከሰው በላይ ከእግዚኣብሔር በታች እየቆጠሩ መለስተኛ እግዚኣብሔሮች (mini gods) እያሉ ያመልኩባቸው ነበር። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ግን የሰው ልጅ ንቃት እየዳበረ ሲመጣና ንጉሦችም እንደኛው ሰዎች መሆናቸውን እያወቁ ስለመጡ የኣምልኮት ተግባሩ ቀረ። እንደ ኣምላክ ይመንናሉ እንጂ እንደ የሰው ልጅ ኣይሞቱም ሲባል የነበረውም ሐሰት ሆኖ ሲሞቱ እኛው ባይናችን ለማየትና ለመመስከር በቅተናል።

የሰው ልጅ በራሱ ኣምሳል በተፈጠረ የሰው ልጅ ማምለክ በቀረበት በ21ኛው ክፍለ ዘመን ላይ ሆነን የትግራይ ሕዝብ ነፃ ኣውጪ ግንባር ኣባላት ግን በሺህ ዓመታት ወደ ኋላ ተመልሰው በመለስ ዜናዊ እያመለኩ ናቸው። ጧት ጧት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን እየሔዱ መቃብሩን (እውነት ተቀብሮ ከሆነ) ሳይሳለሙም የሚቀሩ ኣይመስለኝም። እንኳን በመጥፎ ድርጊቱ በታወቀው መለስ ዜናዊ ቀርቶ በጎ ነገርም ሠርቶ ቢሆን ኖሮ በኣንድ ግለሰብ ማምለኩ ኣስፈላጊ ኣይደለም ማለቱ ብቻ ሳይሆን ኋላቀርነትና በራስ ኣለመተማመንም ነው። ለሀገርና ለወገን የሚበጅ ጥሩ ሥራ ሠርቶ ከሆነ በጎ ሥራው ይመሰክርለታል። ሥራው ያስወድሰዋል። ሥራው ያስከብረዋል። በሞተ ጊዜም በግዳጅ ከማስለቀስ ተጠቃሚ ሕዝብ ካለ ለማልቀስ ትዕዛዝ ባላስፈለገ ነበር። ኣለበለዚያ ግን ሀገር እያጠፋና ሕዝብ እየጨረሰ እንደ ጣዖት የሚሰገድለት ምክንያት የለም። እንዲያውም እንደዚህ ያሉ ኣምባገነን ኣረመኔ  መሪዎች ለሌሎችም የመጥፎ ኣርኣያ ተምሳሌት እንዳይሆኑ መወገዝና መወገድ ኣለባቸው። ፀረ ሀገርና ፀረ ሕዝብ የሚወደስበት ምክንያት ካለ ኣወዳሾቹም ከዚያው ከፀርነት ሥርዓቱ ጋር የሚደመሩ ናቸው። “ግም ለግም ኣብረህ ኣዝግም” ይባል የለ።

የትግራይ ሕዝብ ነፃ ኣውጪ ግንባር ባለሥልጣናት ዛሬ መለስን ቢያወድሱና ቢያመልኩበትም ወደፊት ተግባሩና ተግባራቸው ፈጦ ስለሚታይና ስለሚያጋልጣቸው እነርሱም ነገ ያፍሩበታል፣ ኣሁንም ማፈር የጀመሩ እንዳሉ ከእንቅስቃሴኣቸው እያየንና እየተመለከትን ነው። “እኛስ ብለን ነበር የወለጋን ወርቅ ተቋጥራ ተገኘች በምናምን ጨርቅ” እንደሚባለው የኢትዮጵያ ሕዝብ ኣካሔዳቸው የመልካም ጅምር ስለኣልነበረ እንዲያስተካክሉ ነግሮኣቸው ነበር። የሕዝብን ሃሳብ መቀበልን እንደ ነውር የሚቆጥሩት የወያኔ ኣባላት ግን እነርሱ ካሉት ውጭ መቀበል ስለኣልፈለጉ ለውርደት ተዳረጉ። ገናም መቀመቅ ይወርዳሉ።

የትግራይ ሕዝብ ነፃ ኣውጪ ግንባር ቱባ ባለሥልጣናት መለስ ዜናዊን “ባለራዕዩ  መሪያችን” ብለው የሚያሞካሹ፣ የሚያወድሱና የሚያመልኩ ከሆኑ ማንም ሳይነግራቸው ራሳቸው ራሳቸውን ኣዋርደዋል። ምክንያቱም ካለርሱ ምንም መስራት ኣንችልም ካሉ እርሱ የጋሪው ፈረስ ሲሆን እነርሱ ደግሞ የጋሪው ፈረስ መቀመጫ ሆነው ከኋላው እየተጎተቱ የሚከተሉት እንጂ ኣነርሱ ሃሳብ የማፍለቅና ተወያይተው ውሳኔ የመስጠት ችሎታውና ኣቅሙም ኣልነርበራቸውም ነበር ማለት ነው። ስለሆኑም እርሱን ተክተው መሥራት ስለኣልቻሉ የጣዖቱ ኣምላክ እየመራቸው ነው የሚሠሩት ማለት ነው።

እውነት የፖለቲካ ፓርቲ መሥርተው ይሠሩ ከነበሩ፣ በፓርቲ ኣወቃቀር መሪውን ተክቶ የሚሠራ ሁልጊዜ ዝግጁ ሆኖ ነው የሚቀመጠው። ይኸ ሆኖ ቢሆን ኖሮ መለስ ዜናዊ ሲሞት ወዲያ ተተኪው ሥልጣኑን መረከብ ይችል ነበር። ግን የውሸትና የማወናበጃ ማፊያ ድርጅት ስለሆነ ያፈራቸውም ጀሌዎቹ ማፊያዎች እንጂ ለሀገርና ለወገን የሚበጁ ኣይደሉም። እኔም ራሴ ይኸንን ዐረፍተ ነገር ስጽፍ እያፈርኩ ነው። ምክንያቱም ከራሳቸው ማፊያነትም ኣልፈው ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን ያስወቀሱ፣ሀገሪቷን ምሁር ኣልባ ያደረጉና የመሃይማን መፈንጪያ ያደረጉ፣ ሀገሪቷን በየመድረኩ የመጥፎ ተግባራት ተምሳሌት እንድትሆን ያደረጉ፣ የፖለቲካ ፓርቲ የሚባሉ ድርጅቶችንም ጭምር ያሰደቡ፣ ያሳፈሩና ያስወቀሱ ከመሆናቸውም ኣልፈው በኢትዮጵያ ምድር መፈጠራቸውና ኣሳፋሪና ወንጀለኛ ድርጅት ፈጥረው ሀገርንና ሕዝብን ማሳፈራቸው ነው።

ኢትዮጵያ ሀገር ወዳድ ምሁራን እያሏት በኃያላን መንግሥታትና ባካባቢ ጠላቶቿ እየተመራ ኢትዮጵያን ማስተዳደር ሳይሆን በጭቆናና በግፍ ኣገዛዝ ኢትዮጵያን ሲያፈራርስና ኢትዮጵያውያንን ሲጨፈጭፍ የኖረው ኣረመኔው መለስ ዜናዊ የኣሳፋሪ ድርጊት ፈጻሚ ሆኖ በመሞቱ በርሱ መስመር ላይ ያሉ መሪዎችና የበላይ ኣለቆቹም ኣፍረውበታል። በሌላ ጎኑ ደግሞ ራሳቸውን ማሻሻል ለሚሹ መሪዎች ጀርባቸውን እንዲመረምሩ ትምህርት ሰጥቶኣቸው ማለፉን ልብ ያለው ልብ ይለዋል። የሰው ልጅ መስተዋቱ ሰው ነው ተብሏልና ራሳቸውን የሚያዩበት ትምህርት ሳያገኙ ኣልቀሩም።

ኢትዮጵያን ከመፈራረስ ለመታደግና ኢትዮጵያውያንን ከገፍና ከግፍ ዕልቂት ለማዳን ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን እጅ ለእጅ ተያይዘን ዘብ እንቁም።

ቸር ይግጠመን። abatemsas@gmail.com.

 

የፖለቲካ ካሊፕሶ –“ከፕ/ት ግርማ ይልቅ ቴዲ አፍሮ አስመራ ቢሄድ ይሻል ነበር”– (ከተስፋዬ ገብረአብ)

$
0
0

tesefaye geberab ለኢትዮጵያ የ2006 አዲስ አመት እንኳን አደረሰን!
በተጨማሪ ለኤርትራ የቅዱስ ዮሃንስ በአል እንኳን አደረሰን!
በኢትዮጵያና በኤርትራ የምትገኙ የበአሉ ባለቤቶች ሁሉ እንኳን አደረሳችሁ!!
እንዲህ ለኢትዮጵያና ለኤርትራውያን በዘዴ ሰላምታ ማቅረቡን ከቴዲ አፍሮ ነው የተማርኩት። ቴዲ ገና በወጣትነቱ የፖለቲካ ካሊፕሶ ገብቶታል። ቴዲ አፍሮ ባለፈው ሃምሌ ወር አምስተርዳም ላይ ኮንሰርት አቅርቦ እንደነበር ሰማሁ። እኔ እንኳ ለእረፍት ወጣ ብዬ ስለነበር አመለጠኝ። እንደሰማሁት ከ40% በላይ ታዳሚዎቹ ኤርትራውያን ነበሩ።
(ሙሉውን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ)

መውጫ አብጅቶ መግቢያ የከለከለን አሳዳጁ ማን ነው? –ከግርማ ሠይፉ ማሩ

$
0
0

ከግርማ ሠይፉ ማሩ

ሀገራቸን ኢትዮጵያን ለቀው ለስደት የተዘጋጁት ዜጎችን ቁጥር መገመት አስቸጋሪ ቢሆንም በአንድ ወይም በሌላ ምክንያት መውጣት የቻሉት ግን ላለመመለስ ብዙ ምክንያቶች አሉዋቸው፡፡ ይህን የዜጎች (በተለይ የተማሩና ወጣቶች) ስደት ሀገራችንን ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈላት እንደሆነ እና ወደፊትም ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያስከትል ለማወቅ ሊቅ መሆን የሚያስፈልግ አይመሰለኝም፡፡ አሜሪካኖች በዲቪ እንኳን ሊወስዱት የሚፈልጉት ፊደል ቆጥሮ አንድ ነገር ሊያደርግላቸው የሚችለውን እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ለዜጎች ስደት ምክንያቱ መንግሰት እንደሚለው ህገወጥ ደላሎች አይደሉም ይልቁንም የመንግሰት የተለያየ ፖሊሲ ውጤቶች ናቸው ብዬ ማሳየት ፈለኩኝ እና ይህን ፅሁፍ ጀመርኩ፡፡
Girma Siefuየስራ ዋስትና በሀገራችን የተረጋገጠ አይደለም፡፡ ቀደም ሲል የመንግሰት ስራ ያልተመቸው ኢትዮጵያዊ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ገብቶ በሞያው ማገልገል አንድ የሚታይ ጠባብ አማራጭ ነበር፡፡ ይህ ጠባብ አማራጭ እንደሚታወቀው ከ1997 ምርጫ በኋላ ይህ “የኪራይ ሰብሳቢዎች ምሽግ እንዲፈርስ” በሚል በወጣ አዋጅ ጠባብ አማራጭነቱ ቀርቶዋል፡፡ የዚህ አማራጭ የተዘጋው ህጋዊ በሚመስል እና ለድሆች በማሰብ በሚል ነው፡፡ አዋጅ ቁጥር 621/2001 የበጎ አድራጎትና ማህበራት ምዝገባ አዋጅ እና ተከትለው የወጡትን መመሪያዎች ማየት በቂ ነው፡፡ ውጤቱ ግን ኢህአዴግ እንደሚያስበው የመንግሰት ተቀጣሪነት የሰለቻቸው ሰዎች ፀጥ ለጥ ብለው እንዲገዙ፣ መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋሞች ውስጥም አንፃራዊ ነፃነት አግኝተው ይሰሩበት ከነበረበት ወደ መንገስት ተቋም በመምጣት የመንግሰትን ተቋምን አላሳደጉም፡፡ በተቃራኒው የተገኘው ውጤት አቅም ያለው ሁሉ በአገኘው አጋጣሚ ሁሉ ሀገሩን ጥሎ ነፃነት ወደአለበት ምድር ሁሉ እየተሰደዱ ነው፡፡
የኪራይ ሰብሳቢ ምሽግ ለመናድ የተዘረጋው ወጥመድ በሀገራችን የሚገኙትን የመንግሰትም ሆነ መንግሰታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን በሰለጠነ የሰው ሀይል ከማሳጣት የዘለለ ፋይዳ አላመጣም፡፡ ያመጣው ጥቅም ግን ሳይጠቀስ መታለፍ የለበትም፡፡ መንግሰታዊ ባልሆኑ ተቋሞች የሚሰሩ ዜጎችም አንድ ቀን ውጭ የሚሄዱበት ዕድል እሰኪያገኙ ልኑርበት በሚል ባሉበት ዝም ብለዋል፡፡ አንድ በቅርቡ ያገኘኋት በቅርብ የማውቃት ልጅ ለምን ወደ ሀገር እንደማትመለስ ስጠይቃት አሁን የምትስራበት መሰሪያ ቤት አልተመቻትም፣ ከዚያ ወጥታ ሌላ ተመሳሳይ ቦታ ለመግባት ደግሞ አሁን ባለው ፖሊስ ሰራተኛ መቀነስ እንጂ መጨመር የብዙ መንግሰታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ፕሮግራም አካል አይደለም፡፡ ሰለዚህ አሁን ከምትኖርበት የባሰ ኑሮ ለመኖር ፈቃደኛ ስላልሆነች፤ “የሀገር ፍቅር የትም አይሄድም ነፃነት እና የስራ ዕድል ባለበት ብቆይ ይሻላል” ነው ያለችኝ፡፡ ሁለተኛ ዲግሪ በያዘችበት ሙያ ስራ ባታገኝም፤ አሁን የምትሰራው ስራ እንደተመቻት አጫውታኛለች፡፡ ይህ እንግዲህ አወጅ ቁጥር 621/2001 ያስገኘው ድል ነው፡፡ ይህችን ልጅ በፍፁም ህገወጥ ደላላ አላሳሳታትም፡፡ እርሷን እና መስሎቿን ያሳሳትው የመነግሰት የተሳሳተ የፖሊሲ አቅጣጫ ነው፡፡ የስራ ዋስትናን ማረጋገጥ የማይችል መንግስት ትክክለኛ የህዝብ ድምፅ የሚቆጠርበት የፖለቲካ ምዕዳር ቢኖር እንኳን ለተከታታይ አራት አይደለም አንድ ተጨማሪ ዙር ምርጫ ማሸነፍ የሚችልበት ዕድል አይሰጠውም፡፡ አሁንም መንግሰት ከጊዚያዊ የስልጣን ጥቅምና ፍላጎት ይልቅ ለዘላቂ ሀገራዊ ጥቅም ሲባል በዚህ ምክንያት ሀገር ጥለው የሚሰደዱትን ዜጎች ለመታደግ ይህን አዋጅ ሊያሻሽለው ይገባል፡፡ መንግሰታዊ ያልሆኑ ተቋማትም እሺ እያሉ ነፃነትን ሸጦ ከመኖር በቃን ብለው ድርጅት በመዝጋት ጭምር ተቃውሞ ሊያሰሙ ይገባል፡፡ ካላጎነበሳችሁ አትጫኑም ነው ያለው ማርቲን ሉተር ኪንግ፡፡
በሀገራችን የባለሞያ ስደት ልላው ምክንያት በቂ ክፍያ አለማግኘት እንደሆነ ይታመናል፡፡ በዚህ ምክንያት ከሚሰደዱት ዜጎች አብዛኞቹ የህክምና ባለሞያዎች እንደሆኑ ቢታወቅም በሌሎች መስኮቸም ይህ ችግር ጎልቶ ይታያል፡፡ እነዚህንም ዜጎች መንግሰት እንደሚለው ህገወጥ ደላሎች ያሳሳታቸው ሳይሆኑ መንግስት በሚከተለው ፖሊሲ ምክንያት በሞያቸው የድካማቸውን ያህል ስለማያገኙ፣ እንዲሁም በያዙት ሙያ በሌላ ቦታ የተሻለ ዕድል ስለሚያገኙ ጭምር ነው፡፡ ዘወትር የእኛ ሀገር የባለስልጣናት ደሞዝ ትንሽ ሰለሆነ እውነት የሚመስለው ብዙ ሰው አለ፡፡ ባለስልጣኖች ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ የሚያገኙት ደሞዝ (እዚህ አካባቢ ወ/ሮ አዜብ ትዝ እንደምትላችሁ ገመትኩ) በእርግጥ ትንሽ ነው፡፡ ደሞዝ የሚባለው ማለት ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በተለያየ መንገድ የሚያገኙት ምንዳ ግን በጣም ብዙ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ለዚህም ዋነኛው ምሳሌ በቦርድ ሰብሳቢነት እና በውጭ ጉዞ የሚያገኙትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ በውጭ ሄዶ መታከም፣ ነዳጅ፣ የመኖሪያ ቤት እና ሌሎች ብዙ ጥቅማ ጥቅሞችንም ማንሳት ይቻላል፡፡ ከዚህ አንፃር አንድ ባለሞያ ይህ ዕድል ሳይኖረው በወር ደሞዝ እንዲኖር ሲጠየቅ ጥያቄው የሀገር ፍቅር ሳይሆን የምንኩስና ይሆን እና ስደት አንድ አማራጭ ይሆናል፡፡ ከፍተኛ ሀብት ፈሶባቸው የሰለጠኑ ባለሞያዎች የተወሰነ የማጣሪያ ፈተና በማለፍ ብቻ ሌሎች ሀገሮችን ማገልገል አማራጭ እየሆነ ነው፡፡ አንድ በጥቁር አንበሳ የሚሰራ ሀኪም የነገረኝ ከካርድ ብቻ የሚሰበሰበው ገንዘብ ለሀኪሞች ደሞዝ ቢመደብ ሀኪሞች በደሞዝ ማነስ ምክንያት ከመልቀቅ ይድናሉ ነው የሚለው፡፡ በእውነት ለመናገር በየጤና ተቋሙ የሚመደቡ ካድሬዎች የሚፈጥሩት ጫና በዝቅተኛ ደሞዝ መቋቋም ግዴታ አይደለም፡፡
በነፃነት ለመስራት ያለመቻል በሀገራችን በመንግሰት መስሪያ ቤት ብቻ ሳይሆን በግል ተቋምም ቢሆን ዜጎች በነፃነት የሚሰሩበት የስራ ድባብ ባለመኖሩ አማራጭ ያለው ሁሉ ከሀገር ተሰዶ መኖርን አማራጭ ካደረገ ውሎ ሰንብቶዋል፡፡ ለኢህአዴግ ዳኝነት ቢሆን ህክምና ወይም ምሕንድስና አብዮታዊ ዲሞክራሲ አመለካከት ካልገባው ትርጉም ያለው ዕውቀት አይደለም፡፡ ለዚህ ነው ለኢህአዴግ አድረናል ብለው የነበሩ በአጋጣሚ ሁሉ የውጭ ሀገር ዕድል ሲያገኙ እየተንጠባጠቡ የሚቀሩት፡፡ በነገራችን ላይ በተደጋጋሚ ውጭ የሚመላለሱ እና ስልጣን ላይ ያሉ የገዢው ፓርቲ አባላት በጣት ከሚቆጠሩት በስተቀር አንድም ልጅ በቤታቸው የለም፡፡ ልጆቻቸው በሙሉ ውጭ ሀገር ላይመለሱ ሄደዋል፡፡ ይህ የባለስልጣኑ የነፃነት እጦት መገለጫ ነው፡፡ አንድ ቀን ምን እንደሚመጣ ያለማወቅ፡፡ ሁሌ በሀገራችን ይመጣል እያሉ የሚያሰቡት ሟርት ከመጣ ልጆቻቸውን እንዳይነካ በማሰብ የተደረገ ነው፡፡ አሁን በልማት ልናስመነድገው ነው የሚሉት ሀገር ለእነርሱ ልጆች ሳይሆን ለድሆች ልጆች ነው፡፡ ይህ በእውነት ደግነት ነው፡፡ ይህ ሁሉ ድካም ለሰው ልጅ ብሎ ስለሆነ፡፡ እኔ የምር የምላችሁ እነዚህ ባለስልጣናት በህይወት እያሉ ልጆቻቸው እንደሚያዝኑባቸው ጥርጥር የለኝም፡፡ የመንግሰቱ ኃይለማሪያም ልጆች ከሀገር ተሰደው በመኖራቸው ደስተኞች ሊሆኑ ይችላሉ ብዬ አላስብም፡፡ የማንም ባለስልጣን ልጅ ሀገሩን የሚናፍቅ እንዲሆን እኔ ፍላጎት የለኝም፡፡ ባለሀገር ልጆች እንዲኖሩን ሁላችንም ልጆቻችንን ለስደት ሳይሆን በሀገራችን በሚፈጠር ሀገራዊ ዕርቅ በነፃነት ሀገራቸው እንዲኖሩ ማበረታታ ያለብን ይመስለኛል፡፡ እባካችሁ ለንግግር እና ሀገራዊ መግባባት ለመፍጠር ጊዜ እንመድብ፤ ግንብና ግንባታ ይደረስበታል፡፡ “የሰላም እጆች ይዘርጉ የአዲስ ዓመት መልዕክቴ ነው”፡፡ የሶሪያ ዲሞክራሲና ሠላም ዕጦት ግንቡን ሁሉ ነው የበላው፣ እየበላውም ያለው፡፡
ሀገራችን ኢትዮጵያ ሀገር ለቆ ለመውጣት ብቻ ሳይሆን ለመግባት ፍላጎት ያለቸው እጅግ ብዙ ዜጎች አሉዋት፡፡ ዳሩ ምን ያደርጋል አሁን ያለው መንግስት እነዚህ በአንድ ወይም በሌላ መልክ ከሀገር ወጥተው የነበሩ ዜጎች (ዜግነትም ቀይረውም ቢሆን) አሁን እንዲመጡ የሚፈልገው ኪሳቸውን በዶላር ሞልተው ነፃነት ሲፈልጉ ደግሞ እዛው በለመዱበት ብቻ የሚል አቋም ይዞ ነው፡፡ ነፃነት በለመዱበት ሀገር ሆነውም ቢሆን ግን ገዢውን ፓርቲ በነፃነት መተቸት አይቻልም ከእነርሱ የሚጠበቀው የሚጠይቀውን ገንዘብ ሲጠየቁ መስጠት ብቻ ነው፡፡ የማያምኑበት ፖሊሲ እንዲፈፀም የእነርሱ ገንዘብ ማዋጣት ግድ ብቻ ሳይሆን ካላዋጡ ፀረ ልማት እና ለሀገር ጠላቶች የሚል ቅፅል ስም ሀቃቸው ይመስላል፡፡
በሰለጠኑበት ሙያ ለማገልገል የሚችሉበት ምቹ ሁኔታ ያለመኖር አንዱ ነው፡፡ በውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን በሰለጠኑበት ሞያ አገልግሎት መስጠት ቢፈልጉ አብዮታዊ ዲሞክራሲ መቀበል ይኖርባቸዋል፡፡ ይህም በቀጥታ የሚጠየቅ ሳይሆን የፈለጉ ሳይንቲስት ቢሆን መንግስትን መቃወም አይቻልም፡፡ ሞያቸውን ለሀገር ካለው ፋይዳ አንፃር ሳይሆን የሚመዘነው ለገዢው ፓርቲ ካለው የፕሮፓጋንዳ ጠቀሜታ አንፃር ነው፡፡ አንድ አንድ ባለሞያዎች ከዚህ አንፃር ትንሽ ቀደዳ ሳይኖር አይቀርም ብለው ወደ ሀገር ሲመጡ የመጀመሪያ ሰለባ የሚሆኑት በኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ወይም ኢቢኤስ ለሚባል የቴሌቪዥን ጣቢያ ነው (ይህ ጣቢያ በኢትዮጵያ የብሮድካስት ህግ መሰረት ህገ ወጥ ነው)፡፡ እነዚህ ዜጎች መስጠት የሚፈልጉትን ከመሰጠታቸው በተጨማሪ ገና እንደገቡ በሚከቧቸው አጫፋሪዎች ታጅበው ስለ ሀገሪቱ ዕድገት፣ ሰለ አለው ዲሞክራሲያዊ ስርዓት፣ ወዘተ ዲስኩር እንዲሰጡ በማድረግ ቅርቃር ውስጥ ይከቷቸዋል፡፡ ለዚህ ሁነኛ ምሳሌ የሚሆነው ኤርሚያስ አመልጋ ይመስለኛል፡፡ ሌሎችም ብዙ አሉ፡፡
አሁን በሀገራችን ያለውን ሁኔታ በተግባር ለመፈተን ብለው የፖለቲካ ብቻ ሳይሆን የኤኮኖሚ ምዕዳሩም ጠባብ እንደሆነ ብቻ ሳይሆን በፍፁም እንደማያንቀሳቅስ ተረድተው ከጫወታ የወጡትን ዜጎች ቤቱ ይቁጠራቸው በማለት የሚታለፍ አይደለም፡፡ እነዚህ ዜጎች በውጭ ደክመው ያገኙት ገንዘብ እንደዋዛ ከስረው ከጫወታ ሲወጡ ሌሎች መምጣት ለሚፈልጉት ምን መልዕክት እንዳለው መረዳት ተገቢ ነው፡፡ ይህን ፅሁፍ ስፅፍ ኤርሚያስ አመልጋ ወደ ሀገር የመኖሪያ ፈቃድ መልሶ ሲመጣ እና ዛሬ ምን እንደሚሰማው ጥያቄ ማቅረብ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ በዚህ ጉዳይ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እንዲሁም በሀገር ውስጥ ያሉ ዜጎች በደረሰባቸው ጉዳት የኤርሚያስን ስም መስማት የሚያስጠላቸው ቢሆንም ይህ ለምን ሆነ ብለው ከስሜት በወጣ እርጋታ ሊያስቡት እንደሚገባ ይሰማኛል፡፡ የኦላንድ ካር ባለቤት የነበረው ኢንጂነር ታደሰም ቢሆን ለዚህ ጥሩ ምሳሌ የሚሆን ይመስለኛል፡፡ እሲኪ ድምፃችሁን አሰሙና መንግሰት ምን ደገፋችሁ ምንስ አደረጋችሁ፡፡ እንግዲ የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም ይባል የለ፡፡
ደቡቡ ሱዳን የምትባል አዲስ ጎረቤታችን ብዙ ኢትዮጵያዊያ ለስራ እንደሚሄዱ አውቃለሁ፡፡ አዲሷ ሀገር እንኳን አሁን ኢትዮጵያዊያ ወደ ሀገሯ ሲገቡ እንደማይቀሩ ለማረጋገጥ የባንክ አካውንት መጠየቅ ጀምራለች፡፡ እንደ አጋጣሚ እኔም ሄጄ ይህችን ጎስቋላ ሀገር አይቻታለሁ፡፡ ብዙ ኢትዮጵያዊያ እዚህች ሀገር ለምን ተሰደው ይሄዳሉ? ለሚለው ጥያቄ ሁሌ የምሰጠው መልስ ምንም ነገር ስለሌለ ሁሉ ነገር ስራ ነው በማለት ነው፡፡ ብዙ ትርፍ በአጭር ጊዜ ለማግኘት የፈለገ ከነስጋቱ ሄዶ በአጭር ጊዜ ሊከብር ይችላል፡፡ ይህ በኢህአዴግ ሰፈር “ኪራይ ሰብሰቢ” ያሰብላልና ማንም ብቅ አይልም፡፡
ሌሎች ሀገሮችን በተለይ አሜሪካን እና አውሮፓን ሳይ ቅናት ያድርብኛል ብዙ ስራ እንደሚቀረን ይስማኛል፡፡ በተነፃፃሪም ያለው ነፃነትና ዕድል ብዙ ሰው ሊያማልል እንደሚችል ይገባኛል፡፡ በተለይ ብራዚሊያ የምትባል ከተማ እና ብራዚል የሚባል ሀገር ካየሁ በኋላ ኢህአዴግ 22 ዓመት እንዳባከነ እና የብራዚሊያን ያህል 5 በመቶ እንዳልሰራ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ብራዚሊያ የምትባለው የብራዚል ዋና ከተማ ከተመሰረተች ከ50 ዓመት ብዙ አትዘልም፡፡ ኢህአዴግ ባለፉት 22 ዓመት ግማሹን መስራት ይኖርበት ነበር፡፡ ለዚህም በውጭ የሚኖረ ኢትዮጵያዊያን እውቀትና ገንዘብ ብዙ ሚና ሊኖረው ይችል ነበር የሚል እምነት አለኝ፡፡ ማስተባበር የሚችል የፖለቲካ ሰርዓት መዘርጋት ቢቻል፡፡ በቅርቡ የአሜሪካው ፕሬዝዳን ባራክ ኦባማ ብራዚልን እንዲህ ብለው ገልፀዋታል “ከአንባገነን ስርዓት፣ በሰላም ወደ ዲሞክራቲክ ስርዓት የተሸጋገረች” እውነት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህገ መንግሰት በተወሰነ ማሻሻያ የብራዚል ዓይነት ዲሞክራሲ ሊያመጣ እንደሚችል እኔም ይሰማኛል፡፡ የብራዚል ህገ መንግሰት እንደ እኛው ህገ መንግሰት ፓርላሜንተሪ ነበር፡፡ መሪያቸውን በቀጥታ አይመርጡም ነበር፡፡ ህገ መንግስቱን አሻሽለው ብራዚላዊያን ዛሬ ማን እንደሚመራቸው በቀጥታ ይመርጣሉ፡፡ እኛም ሲናፍቀን ይኖራል ማለት አይደለም፡፡ አንድ ቀን ዘሩ/ጎሳው ማን ነው? ሳንል ለኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን ባለው ራዕይ መሪያችንን እንመርጣለን፡፡ ተሰፋ አለኝ፡፡
የተነሳሁበት ሀገር ለቆ የመሰደድ ምንጭ የሚያማልል ነፃነትና ዕድል ያለባቸው የአሜሪካና አውሮፓ ከተሞች ብቻ ሳይሆኑ ጎሰቋላዋ ደቡብ ሱዳን ጭምር ነች እያልኩ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን በዚህም በዚያም ሀገራቸው ስትገፋቸው ለምቾት ብቻ ሳይሆን ችግርም ለመጋፈጥ በመወሰኝ በረሃና ውቅያኖስ አቋርጠው ይሰደዳሉ፡፡ መንግሰት ግን የችግሩ ምንጭ ህገ ወጥ ደላሎች ናቸው እያለ ትክክለኛ መፍተሔ ለመሻት ዝግጁ የሆነ አይመስልም፡፡ አሁንም ችግሩን ከስሩ ማየት ተገቢ ነው የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ ነው ጊዜ ወስደን ሃሳባችንን የምናካፍለው፡፡
አንድ እናት ለፆም መፈሰጊያ ምግብ እያዘገጁ ሳለ መፈሰጊያ ሠዓት ሳይደርስ ጨው ለመቅመስ ብለው ቀመሱ፣ ፆም ሲያዝም እንዲሁ የተረፈው እንዳይደፋ ብለው ፆም ገደፉ፡፡ ደግነቱ ይህን ለንስሀ አባታቸው በሀቅ ሲናገሩ አንቺ ሴት ፆሙን እንዳይገባ እንዳይወጣ ከለከልሽው አሏቸው ይባላል፡፡ የእኛም መንግሰት ዜጎች በሀገር እንዳይቆዮ እና ወደ ሀገር እንዳይመለሱ ተግቶ እየሰራ ነው፡፡ ችግሩ ይህን ግልፅ አድርጎ የሚነግረው የንሰሃ አባት ያጣ ይመስለኛል፡፡ በእኔ እምነት የዚህ ድርጊት ጥቅም ጊዚያዊ የስልጣን ፍላጎት ብሎም ለግል ደህንንት ካለ ሰጋት ብቻ የሚመነጭ ነው፡፡ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር (እርሳቸው ከልባቸው ከሆነ የአሁኖቹም ሌጋሲ ማሰቀጠል ከፈለጉ) ይሉ እንደ ነበረው ሀገር ማለት ሰዉ እንጂ ጋራና ሽንተረር ብቻ አይደለም፡፡ ባለሀገር ሊሆን የሚገባውን ትውልድ እያባረሩ (የእራሳቸውን ልጆች ጨምሮ)፣ ሌሎች ያባረሯቸውም እንዳይገቡ በሩን ጥርቅም አርገው ዘግተው ሀገር ማለት ሰው ነው የሚለው አይገባኝም፡፡ በቅርቡ እንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ በመብራት ሀይል አዳራሽ በጠራው የህዝብዊ ስብሰባ ላይ ሀብታሙ አያሌው የሚባል ወጣት “ሀገር ማለት ልጄ” የሚል የአንድ እውቅ ገጣሚ ግጥም በሰሜት አንብቦ አስለቅሶናል፡፡ ሀገር ማለት ልጄ ለልጆች የሚተላለፍ ታሪክ ያለው ሲሆን ነው ልጄ፡፡
በሀገራችን በነፃነት ለመስራት ያለመቻል ያቀረበልን አማራጭ ከገዢው ፓርቲ ጋር ተናንቆ ለውጥ እንዲያመጣ መግፋት ወይም ሀገር ለቆ የመስራት ነፃነት እና ዕድል ወደአለበት መሰደድ ነው፡፡ ምርጫው የግል ቢሆንም መንግሰት ግን ዜጎች በዚህን ያህል ደረጃ ለስደት ሲዘጋጁ አሳዳጅ ሆኖ መገኘቱ ሊያሳስበው እና መፍትሔ ሊፈልግለት ይገባል፡፡ ይህ በምንም መመዘኛ “የኒዎሊብራል”፣ የኪራይ ሰብሰቢ፣ ወይም የህገ ወጥ ደላሎች ስራ አይደለም፡፡ መንግሰት የሚከተለው የልማት አቅጣጫ ዜጎችን የሚያገል እና የፓርቲ ደጋፊዎችና ጥቂት የሚባሉ ለገዢው ፓርቲ ለማጎብደድ የቆረጦ ዜጎች ብቻ ተጠቃሚ የሚያደርግ ሰለሆነ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ብዙ የሚሰራባት ሀገር ነች፡፡ እንደ ደቡብ ሱዳን ባንሆንም ምንም ከሚባለው ብዙ ከፍ የማንል ሁሉ ነገር ሰራ ሊሆን የሚችልባት ሀገር ነች፡፡ ይህችን ሀገር በጋራ ለማልማት መነሳት ይኖርብናል፡፡ ይህ የፖለቲካ ሹመት ጥያቄ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ዜጎች ሳይሸማቀቁ መሪዎቻቸውን የሚመርጡበት የፖለቲካ ምዕዳር መፍጠር ብቻ ነው፡፡ ለዚህም መተማመን እና ሀገራዊ መግባባት ማሰፈን ይቅር ባይነት በሁሉም በኩል የግድ ይላል፡፡
ይህ ካልሆነ ግን ወደፊት ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር በውጭ የሚኖሩ የነበሩ በእደሜያቸው የመጨረሻ ዘመንም ቢሆን በሀገራቸው ለመኖረ የቆረጡ እንዲሁም የትም መሄጃ አጥተው በሀገር የቀሩ የሰድተኛ ወጣቶች ወላጆች ሁሉም የሚያመርቱ ሳይሆን ጡረተኞች ሀገር እንዳትሆን ሰጋት አለኝ፡፡ ይህ ከስጋትም ያለፈ እውነት ነው፡፡ አንድ ዘመዴ ያለችኝ እዚህ ጋ መጥቀስ ተገቢ ነው፡፡ “ምርታማ ዕድሜን ውጭ አሰለፉ ለጡረታ ሀገር ከመሄድ የከፋ በደል የለም ነው” ያለችው በበዳይነት ሰሜት፡፡
ቸር ይግጠመን አዲስ ዓመት የመነጋገሪያ የመግባቢያ ዘመን እንዲሆን ሁላችንም የበኩላችንን መወጣት ይኖርብናል፡፡ ነፃነታችን በእጃችን ይዘን የሌሎችን ነፃነት እናክብር፡፡ ፈጣሪ ይርዳን፡፡ አሜን!!!!

የኢትዮጵያውያን ባህልና የጋብቻ ቅድስና – (ተፈራ ድንበሩ)

$
0
0

ኢትዮጵያ ቅድስት መሆኗን የሚያሳዩ ማስረጃዎች፤
ኢትዮጵያ የሚለው ያገራችን መጠሪያ የተገኘው በካም ወገን ሴማዊ ከሆነውና ከነሙሴና አሮን በፊት ካህን ከነበረው መልከጼዴቅ ከሚባል ኢየሩሳሌምን ከመሠረተው ንጉሥ በተወለደውና ኢትዮጵ ከሚባል በኋላ ኢትዮጲስ ተብሎ የኢትዮጵያ ንጉሠነገሥት ከነበረ ሰው የመጣ ስያሜ መሆኑን የቤተክርስትያን መረጃዎች ያመለክታሉ (ፍቅሬ ቶሎሳ 1-10)። ኢትዮጵያውያን ከሁለቱ የኖህ ልጆች ካም (በኩሽ በኩል) እና ሴም (በአብርሃም በኩል ከእሥራኤላውያን ወገን) የተገኙና ተደባልቀው የተባዙ ዘሮች ሲሆኑ ለምሳሌም አፋር (ከ Ophir) የሴም ወገን ከሆነው ነገደ ዮቅጣን የመጣና በአፍሪካ ቀንድ ከጥንት ጀምሮ የነበረ ሕዝብ ሲሆን የአህጉሩ መጠሪያም ከዚሁ ቃል እንደተገኘ ይነገራል። በአርኪዎሎጂና አንትሮፖሎጂ ጥናት ከመረጋገጡ በፊት ሔሬዶተስና ዲዎዶረስ የተባሉ የጥንት የታሪከ ፀሐፊዎች የመጀመሪያው ሰው የኖረው በኢትዮጵያ እንደነበረ ጽፈዋል (Gates 68)። ኢትዮጵያውያን ዛሬ በቋንቋ ተለያይተው ይታዩ እንጅ፣ የካም፣ የሴም፤ የኦሞቲክና የኒሎቲክ ነገዶች ውሁድ የሆነ አንድነት አላቸው። በባህል ብቻ ሳይሆን በዘርም ተቀላቅለዋል። አሁን ባገራችን ከሚነገሩት ከ፹ በላይ ቋንቋዎቻችን ውስጥም ብዙዎቹ ከጥንቱ ግዕዝ፣ ከሳባ (ሱባ)፣ እብራይስጥ፣ ግሪክና ከሌሎች የሴምና የኩሽ እንዲሁም በአባይ ወንዝና ኦሞ ሐይቅ የተሰየሙ (ኒሎቲክ እና ኦሞቲክ ) አፍሪካዊ ቋንቋዎች ተገኝተውና ተቀያይጠው ትውልዶች እየበዙ ሲሄዱ በተጓዳኝ የተባዙ ናቸው።

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያመለክተን ኢትዮጵያ በእግዚአብሄር ዘንድ ከፍተኛ የቅድስና ደረጃ አላት (መዝሙር ፷፰፤፴፩፣ ትንቢተ አሞጽ ፱፡፯)። አገራችን መንፈሳዊነት የሰፈነበት ባህል ያላት ስለሆነች ልዩነቶችን አቻችሎ አብሮ መኖርን፣ ለጋስነትን፣ መረዳዳትንና እንግዳ ተቀባይነትን አዋህዳ ለቤተሰብም ከፍተኛ ክብር በመስጠት የኖረች የጥንት አገር ነች። ሆኖም ትውልድ እየበዛ ሲሄድ ይህች ምድራዊ ገነት የሆነች አገር በየቦታው የተሟላ የተፈጥሮ ሀብትና የአየር ንብረት ስላላት ብዙዎች ሕዝቦቿ በተለያዩ አካባቢዎች በወንዝ፣ ተራራ፣ ወዘተ ተካለውና ራሳቸውን ችለው ለረጅም ዘመናት ሲኖሩ በቋንቋዎቻቸውም እንደዚሁ ተለያይተው ዛሬ የሚታየውን የብሔር-ብሔረሰብ ሰያሜዎች ዝርዝር ሊያስከትል ችሏል (ተፈራ ድንበሩ 59-60) ።
eth church cry
በመዝሙር ፷፰፡፴፩ ላይ “ኢትዮጵያ ታበፅሕ እደዊኃ ሀበ እግዚአብሔር” የተባለችበትም ያለምክንያት አይደለም፤ ከእግዚአብሔር በሲና ተራራ ሕገ-ኦሪትን የተቀበለው ሙሴ የተመላለሰባት፣ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ጋር በሕፃንነቱ ተሰዶ የሄደባት አገር በመሆኗ ኢትየጵያ ለቅድስት ድንግል ማርያም አሥራት እንደተሰጠችና በሷ አማላጅነት የመዳን ተስፋ እንደተሰጠን ቅዱሳት መጻሕፍት ይናገራሉ። በ፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በቅዱስ ፍሬምናጦስ/አባሰላማ/ አማካይነት ክርስትና በመንግሥት ደረጃ ቢታወጅም ከዚያ በፊት ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌልን ያስተማረበት አገር ነበረች፤ ቅዱስ ፊልጶስ ያጠመቀው የቤተመንግሥት ሹም ወደ ኢየሩሳሌም ለአምልኮት መሄድ ቀደም ሲል ኢትዮጵያውያን ከኢየሩሳሌም ጋር የነበራቸውን ሃይማኖታዊ ትሥሥር ያመለክታል (የሐዋርያት ሥራ ፰፡፳፮)። ክርስትና ቀድሞ ከገባባቸው አገሮች አንዷ ኢትየጵያ ስለሆነች ኦሪትንና ሐዲስን አጣምራ የቆየች ብቸኛ አገር ነች። እንዲሁም ፳፻/ ሁለት ሺ/ ዓመታት ከክርስቶስ ልደት በፊት በሥነጽሐፍ ዕድሜው ተወዳዳሪ ያልተገኘለት የግዕዝ ቋንቋችን በጽሐፍ ላይ የነበረ የመንግሥት መገልገያ ቋንቋ ሲሆን መጽሐፍ ቅዱስ መጀመሪያ ከተጻፈባቸው በጣት ከሚቆጠሩ — እብራይስጥ፤ አርማይክ፣ ፅርእ/ግሪክ/፣ ሲራይክ፣ ኮፕቲክ እና ከላቲን ቋንቋ በፊት የነበረ የአገራችን ትልቅ ሰነድ መሆኑ ሊያኮራን ይገባል። በቀደምት ሥነጥበብ ሙያ የሚታወቁት እነሼክስፔር፣ ሚካኤል አንጀሎና ላዎናርድ ዳቪንሲ ከመፈጠራቸው ከ፩ ሺ ዓመት በፊት ዓለም በጭለማ ውስጥ በነበረበት በ፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ታላቁ የቤተክርስትያናችን የዜማ አባት ቅዱስ ያሬድ ድጓ፣ ጾመድጓ፣ ምእራፍ፣ ዝማሬና መዋሴትን ደርሶ የግዕዝ፣ እዝልና አራራይን ቅኝት ለዓለም አበርክቷል።
አገራችን የብዙ ጻድቃንና ሰማዕታት አገር ነች፤ ለምሳሌ በ፲፭ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረችው ክርስቶስ ሰምራ የኃጢአት ምንጭ የሆነው ሰይጣን ከአምላካችን ይቅርታ ተደርጎለት የሰው ልጅ ሁሉ ሥርየት እንዲያገኝ ቀንና ሌሊት በመፀለይ የቅድስና ሥራ የሠራችና ሌሎች እንደ አቡነ ገብረመንፈስቅዱስ፣ አቡነ ተክለሃይማኖት፣ አቡነ አረጋዊ፣ አባ ሣሙኤል ዘዋልድባ፣… ወዘተ ያሉ የቅድስና ገድሎቻቸው በቤተክርስትያን የሚታወቅላቸው ታላላቅ መንፈሳውያን አገር ነች። እንዲሁም ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተልሔም እንደሚወለድ አወቀው ለክብሩ የሚገባውን ስጦታዎች ይዘው በኮከብ እየተመሩ ወደ ኢየሩሳሌም ከሔዱት ሰባሰገል ከሚባሉ አዋቂ ሰዎች መካከል ኢትዮጵያውያን ነበሩበት። ኢትዮጵያ ኦሪትን ከሐዲስ ኪዳን ጋር አስማምታ ፈሪሀ እግዚአብሄር ያደረበትንና የሰውን ልጅ አክብሮ፣ መብቶቹን ጠብቆ ማኅበራዊ አኗኗርን አዋህዶ የተሟላ ባህል ካላቸው ቀደምት አገሮች ውስጥ የሚተካከላት እንደሌለ ያሁኑ ልጆቿ ጠንቅቀው ያውቃሉ?

የሮማው መሪ ጁሊየስ ቄሣርና የአይሁድ መሪ ሄሮድስ ሥልጣናቸውን ለማቆየት የተወለደ ሕፃን ሁሉ ሲገድሉ ኢትዮጵያ ሰብአዊነትን በሚከተሉ የጥበብ ሰዎች ትመራ ነበር (ፍቅሬ ቶሎሳ 29-30)። እንደ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ እንግሊዝ የመሳሰሉ የአውሮጳ አገሮች ማንበብ መጻፍ በማያውቁባቸውና ያልሠለጠኑ (barbarians) በነበሩባቸው ዘመናት አገራችን በራሷ ፊደል በተጻፈ ሕግና በመንግሥት ትመራ ነበር። በአውሮፓ ሰዎች በባህር ላይ ዘረፋ (piracy) ሲተዳደሩ በነበሩ ጊዜ ኢትዮጵያ ሕግና ሥርዓት የሰፈነባት አገር ነበረች። ሰብአዊ መብት በሌላው ዓለም እየተጣሰ ሰላማዊ ሕዝቦች ሲበደሉ ያገራችን መሪዎች ታድገዋቸዋል። የአይሁድ አክራሪዎች በአረቢያ ናግራን፣ በግብፅ የእስልምና አክራሪዎች በክርስትያኖች ላይ የፈጸሙትን የሰብአዊ መብት ጥሰት ተከላክለዋል፤ ሆኖም በዓለም ላይ በተፈጸመው የሃይማኖት ጦርነት ውስጥ ኢትዮጵያ አልተሳተፈችም። የአገራችን መሪዎች ከ፪፻ በላይ የእስልምና እምነት ተከታዮችን በእምነታቸው ምክንያት ለሕይወታቸው ሲሸሹ በስደት እኤአ በ፮፻፲፫ እና ፮፻፲፭ ዓም ተቀብለው አስተናግደዋቸዋል። ስደተኞቹን እንዲመልሱ የአረቢያው መሪ አቡ ሱፊያን በኃይል ለመጠቀም ቢዝትም የኢትዮጵያ ንጉስ አርማህ (አል አስማሃ ወይም ነጋሽም ይባሉ ነበር) የሚመጣውን ኃይል በኃይል መክቶ ለመመለስ በመወሰን የስደተኞቹን መብት በማስከበር በዓለም የመጀመሪያው መሪ ነበሩ። በዚህ የተነሣ ንጉሡን ነጃሽ በማለት በስማቸው መስጊድ አሠርተው አክብረዋቸዋል፤ ሆኖም አንዳንድ የአሁኑ እስልምና ሃይማኖት ፀሐፊዎች ለክብራቸው የተሠራላቸውን መስጊድ እንደማስረጃ በመውሰድ ንጉሥ አርማህን እስላምናን ተቀብለዋል እስከማለት ደርሰዋል።

ኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት በእንግድነት ወይም በጥገኝነት መጥተው በሰላም የሚኖሩ የማናቸውንም የሕዝብ ወገኖች ተቀብላ በማስተናገድ የታወቀች ነች። ማናቸውንም ሃይማኖት የሚከተሉ ኢትዮጵያውያን ሰው በመግደል ጽድቅ አለ ብለው ሳይሆን በመፈቃቀር የሚያምኑ ሲሆን፤ የእስልምና፣ የአይሁድና የክርስትና እምነት ተከታዮች ተከባብረው በሰላም የሚኖሩባት አገር ነች። ኢትዮጵያዊ ስደተኞችን መንገድ በመምራት የምትታወቅ ሲሆን፣ ዛሬ እንደ ሲናይ ባሉ የአረብ በረሀዎች ስደተኞች በእንግድነታቸው መንገድ ሲጠይቁ በአጻፋው በአንድ በኩል ሃይማኖት አለን ብለው በሚመጻደቁ በሌላ በኩል ደግሞ ነፍሰገዳይ በሆኑ ሰዎች ንብረታቸው ተዘርፎ የሚሰጡት ሲያጡ የሰውነት ሕዋሳቶቻቸው ተቆራርጦ የሚሸጥበት ዓይነት ክስተት በኦጋዴን፣ አውሳ፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ ትግራይ፣ አፋር… ወዘተ በማናቸውም የኢትዮጵያ ክፍለ ሀገር ባላገር ዘንድ እንዲህ ያለ ድርጊት አስነዋሪ ነው።
ኢትዮጵያ ዲፕሎማሲን በማስተማር ቀደምት ከሆኑ አገሮች አንዷ ስትሆን ንግሥት ሳባ ለንጉሥ ሰሎሞን ባበረከተችው ስጦታ በእሥራኤልና ኢትዮጵያ መካከል አንድነት አንዲፈጠር ከማድረጉም በላይ ከንጉሥ ሰሎሞን በተወለደውና በኋላም በኢትዮጵያ በነገሠው ቀዳማዊ ምንሊክ አማካይነት የመጀመሪያው ጽላት ወደ አገራችን ገብቶ ይገኛል። ክርስቶስ የተሰቀለበት ግማደ-መስቀልም እንደዚሁ በአገራችን በግሸን ገዳም የሚገኝ ሲሆን በአገራችን የተፈጸሙ አያሌ መንፈሳዊ ገድሎችን ከቤተክርስትያን መረጃዎች ማግኘት ይቻላል።

ኢትዮጵያ በሕዝቦቿ የተባበረ ኃይል ወራሪዎችን እየመከተች የቆየች እንጂ በቅኝ ያልተያዘች አገር ከመሆኗም በላይ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ቻርተር ካረቀቁት አገሮች አንዷ ነች። በቅኝ ግዛት የተያዙ የአፍሪካ አገሮችን ነፃ እንዲወጡ እንደነ ኔልሰን ማንዴላ ያሉትን በቅርቡም የናሚቢያን የነፃነት ታጋዮችን በማሠልጠንና ሌሎች በቅኝ አገዛዝ ሥር ለነበሩ አገሮች የቁሳቁስና የዲፕሎማሲ እርዳታ በማድረግ በአፍሪካ የፀረ-ቅኝ አገዛዝ ትግል ከፍተኛ ሚና ተጫውታለች። በ፲፱፻፶፭ ዓም የተመሠረተው የአፍሪካ ኅብረት በኢትዮጵያ መሪዎች የተገኘ ውጤት ነው ። እነዚህ አገራችንና ሕዝቦቻችንን ከሚያኮሩ ብዙዎች ነገሮች ጥቂቶች ብቻ ናቸው።

ኢትዮጵያዊ ሥነምግባር እጅግ የሚየኮራ — ሌብነት፣ ቅጥፈት፣ ሰውን በግፍ መግደል በየትኛውም እምነት የተወገዘ (taboo) ነው፤ እንኳንስ በሰው ላይ በእንሰሳት ላይ አንኳ ግፍ መፈጸም ከጥንት ጀምሮ በኢትዮጵያ ውጉዝ ነው። ዛሬ በአገራችን ከአሥራአምሰት እስከ ሃያ ሚሊዮን ሕዝብ ሥራ የሌለውና በአጠቃላይ 80% የሚሆነው ሕዝባችን ከድህነት መሥመር /poverty line/ በታች የሚኖር እንደሆነ የሚታወቅ ሲሆን አንደችግሩ መጠን ቢሆን ኖሮ በሌሎች አገሮች የሚፈጸሙ ወንጀሎች መናኸሪያ በሆነ ነበር፤ ሆኖም በዚህ የኑሮ ደረጃ ላይ ካለው ሕዝባችን ውስጥ እናቶች መቀነታቸውን እየፈቱ ያላቸውን ሲለግሱ ማየት የተለመደ ሲሆን፣ በየትኛውም አካባቢ ያለ ሕዝባችን ያለውን አካፍሎ የመኖር ባህል አለው። በበለፀጉ አገሮች በመንፈስ ጭንቀት ራስን ማጥፋት የተለመደ ሲሆን፣ የአገራችን ደሀ እንኳ በቅድስናው ስለሚያምን በተስፋ የተሞላ ስለሆነ መሬት ራሷ አፏን ከፍታ ካልዋጠችው በስተቀር እጁን ለሞት አይሰጥም።
ኢትዮጵያዊ ባህል በእድር፣ በእቁብ፣ ደቦና ሌሎች ማኅበራዊ ተቋሞች ተባብሮ ተጋግዞ መኖር ነው። ከመልካም ባህሎቿ መገለጫዎች ውስጥ ጋብቻ የተከበረ ተቋም ነው።

ቅዱስ ጋብቻ፤
ጋብቻ በሌላ አገላለጽ ትዳር ይባላል። ትዳር መተዳደር ከሚለው ቃል የተገኘና ኑሮን መሥርቶ በኃላፊነት ባለቤት ሆኖ ቤተሰብ ማስተዳደር ማለት ነው። ስለሆነም አንድ ሰው ትዳር ይዟል ሲባል በመሸበት አዳሪ ከመሆን ወይም ከነጠላነት/ላጤነት/ ወደሰከነና የተከበረ የኅብረተሰብ ሚና ተሸገጋግሮ ቋሚ/ሙሉ/ መተደዳሪያ ይዞ መኖርን ያመለክታል። በጋብቻ ተሳሥሮ ወልዶ ከብዶ መኖር የተቀደሰ ባህላችን ሲሆን በቤተሰብ አባላት መካከል ያለው መደጋገፍና መተሳሰብ በዓለም ላይ ተወዳዳሪ የሌለው ነው፤ ወላጆችን መጦር ወንድምና እህትን ብቻ ሳይሆን ዘመድ አዝማድን ወይም ረዳት የሌለውን የቤተሰብ አካል አድርጎ በሞግዚትነት ማሳደግ፣ ማስተማር ወይም ትዳር ማስያዝ ኢትዮጵያዊ ወግ ነው። ባል (ወንድ) እና ሚስት (ሴት) ተጋብተው ልጆችን በማፍራት የትውልድ ሐረግ የሚፈጠርበት ዓይነተኛ ሥርዓታችን ቤተሰብ ነው።

ጋብቻ ከባህላችን መገለጫዎች ውስጥ መሠረታዊ ሥርዓት ሲሆን በየብሔረሰቡ ያሉትን ዝርዝር የጋብቻ ሥርዓቶች በስፋት ለመግለጽ ጊዜና እቅም የሚጠይቅ ስለሆነ በዚህ ጽሑፍ ትኩረት ለማድረግ የተሞከረው በጋራ ባህሎቿና የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነትን በሚከተሉት ወገኖች ያለውን ልማድ (tradition) ነው።

ስለጋብቻ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤ “ እግዚአብሔርም ሰውን በመልኩ ፈጠረው፤ በእግዚአብሔር መልክ ፈጠረው፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው፤ እግዚአብሔርም ፣ ባረካቸውም፣ እንዲህም አላቸው፤ ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት ግዟትም፤ የባህርን ዓሣዎች የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቃሱትንም ሁሉ ግዟቸው” (ኦሪት ዘፍጥረት ፩፡ ፳፯-፳፰)። “እግዚአብሄር አምላክም በአዳም ከባድ እንቀልፍን ጣለበት፤ አንቀላፋም፤ ከጎኑም አንዲት አጥንትን ወስዶ ስፍራውን በሥጋ ዘጋው፤ እግዚአብሔር አምላክም ከአዳም የወሰዳትን አጥንት ሴት አድርጎ ሠራት፤ ወደ አዳምም አመጣት። አደምም አለ፤ ይህች አጥንት ከአጥንቴ ናት፤ ሥጋም ከሥጋዬ ናት፤ እርስዋም ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል። ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፤ በሚስቱም ይጣበቃል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ” ኦሪት ዘፍጥረት ፪፡ ፳፩-፳፬። እንዲሁም በማቴዎስ ወንጌል ፲፱፡ ፬-፮፣ ኦሪት ዘፍጥረት ፪፡ ፳፪-፳፬፣ የሐዋርያው ጳውሎስ መልእክት ወደ ኤፌሶን ሰዎች ም ፭ ቁ ፴፩-፴፪ ሁሉ እንደተገለጸው የእግዚአብሔር ቃል “ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፤ ሁለቱም አንድ ይሆናሉ” ይላል።
ዝሙትም ፈጽሞ የተከለከለና ኃጢአት ነው። “አመጸኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን? አትሳቱ ሴሰኞች ቢሆኑ ወይም ጣኦትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም። (፩ኛ ቆሮንጦስ ፮፡ ፲-፲፩) “ሥጋችሁ የክርስቶስ ብልቶች እንደሆነ አታውቅምን? እንግዲህ የክርስቶስን ብልቶች ወስጄ የጋለሞታ ብልቶች ላደርጋቸውን? አይገባም። ወይስ ከጋለሞታ ጋር የሚተባበር አንድ ሥጋ እንዲሆን አታውቁምን? ሁለቱ አንድ ሥጋ ይሆናል ተብሏልና። ከጌታ ጋር የሚተባበር ግን አንድ መንፈስ ነው። ከዝሙትም ሽሹ። ሰው የሚያደርገው ኃጢአት ሁሉ ከሥጋ ውጪ ነው፤ ዝሙትን የሚሠራ ግን በገዛ ሥጋው ላይ ኃጢአትን ይሠራል (፩ኛ ቆሮንጦስ ፮፡ ፲፭-፲፰)። እንዲሁም በማቴዎስ ወንጌል ፲፱፡ ፲፰-፳ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰዎች በሰጠው ሕግ “አትግደል፤ አታመንዝር፣ አትሥረቅ፣ በሐሰት አትመስክር፣ አባትህንና እናትህን አክብር፤ ባልንጃራችህን እንደራስህ ወደድ” ብሏል። ፩ኛ ቆሮንጦስ ፯፡ ፪-፮ ላይ፣ “ስለዝሙት ጠንቅ ለእያንዳንዱ ለራሱ ሚስት ትኑረው፣ ለእያንድንዲቱ ደግሞ ለራስዋ ባል ይኑራት። ባል ለሚስቱ የሚገባትን ያድርግላት፤ እንደዚሁም ደግሞ ሚስቲቱ ለባልዋ። ሚስት በገዛ ሥጋዋ ላይ ሥልጣን የላትም፤ ሥልጣን ለባልዋ ነው እንጂ፤ እንዲሁም ደግሞ ባል በገዛ ሥጋው ላይ ሥልጣን የለውም ሥልጣን ለሚስቱ ነው እንጂ።…እርስበርሳችሁ አትከላከሉ፤ ራሳችሁን ስለ አለመግዛት ሰይጣን እንዳይፈታተናችሁ ደግሞ አብራችሁ ሁኑ” ይላል።
እግዚአብሔር ጋብቻን የመሠረተው ሰው ብቻውን ከሚሆን ይልቅ ከሚስቱ ጋር እንዲረዳዱ፣ በመንሳዊ አንድነት በፍቅር ተባብረው አንዲኖሩና ዘር እንዲተኩ ነው። ስለሆነም ከዚህ ውጭ የሚደረግ ግንኙነት ሁሉ ሕገወጥና ኃጢአት ነው። ኦሪት ዘሌዋውያን ም ፲፰፡ ፳፫-፳፫ ላይ፣ “ከሴትም ጋር እንደምትተኛ ከወንድ ጋር አትተኛ ጸያፍ ነገር ነውና፤ እንዳትረክስበትም…” ይላል። ኦሪት ዘሌዋውያን ፳፡ ፲-፲፮ እንደተገለጸው የሚያመነዝር ወይም ግብረሰዶም የሚፈጽም ወይም ከእንሳሳ ጋር የሚገናኝ በሞት እንዲቀጣ ያዛል።

ልጅ በወላጆቹና ዘመዶች ታፍሮና ተከብሮ የሚኖርበት ኢትዮጵያዊና ማኅበራዊ ትልቅ እሴት ሲወርድ ሲዋረድ የቆየው ቤተሰብ ሲሆን፣ የመንፈሳዊ መሠረቱ ጥንካሬ በክርስትያኑ ሕዝባችን ብቻ ሳይሆን በሌሎች እምነት ተከታዮች ጭምር ጋብቻ በአገራችን ክቡርና የተቀደሰ ሆኖ ቆይቷል።

ቀደም ሲል ልጅህን ለልጄ እየተባለ ቤተሰቦች የልጆችን ጋብቻ ይወስኑ የነበረው ባህል ዛሬ ኋላ-ቀር ሆኖ ቢታይም በወቅቱ በነበረው ሁኔታ ለቤተሰብ መጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያደረገና ተቀባይነት የነበረው ባህል ነበር። ለአቅመ አዳምና ሔዋን ያልደረሱ ሕፃናት በቤተሰቦቻቸው ውሳኔ ተጫጭተው አንድ ላይ እንዲያድጉ ከተደረገ በኃላ ዕድሜአቸው ደርሶ በአካል መገናኘት ሲጀምሩ ጋብቻው እውን እየሆነ ይሄድ ነበረ። ሁለቱም ሌላ የሚያውቁት ጓደኛና የፆታ ግነኙነት ስለማይኖራቸው ጋብቻውን ከማክበርና ትዳራቸው እንዲሳካ እንደ አንድ አካል ለአንድ ዓላማ በመቆም ጠንካራ ቤተሰብ ከመገንባት በስተቀር ሌላ ምርጫ አልነበራቸውም፤ ሆኖም ይህ የቆየ ልምድ መሥመሩን ስቶ በተለይ ሴቶች ልጆች ሰብአዊ መብታቸው እየተገፈፈ ቅጥ ያጣ የወንድ ጭቆና እየከፋ ስለሄደ በሕግ የቀረ ሲሆን ሴቷም የመምረጥ ዕድል ልትቀዳጅ ችላለች።

ሆኖም ጋብቻን በነፃ ምርጫ የመፈጸሙ መብት የማያወላዳ ሲሆን ነፃነቱም በአግባቡ ትግባራዊ ካልሆነ የራሱ መዘዝ ሳይኖረው አልቀረም። ዛሬ በሃይማኖት ሥርዓት ካልተገዙ በስተቀር ወንዱም ሆነ ሴቷ ብዙ ጋደኞችን ሲፈትሹ ከቆዩ በኋላ ይጋባሉ፤ በራሳቸው ምርጫ መጋባታቸው በጉልህ የሚታይ የመብት መሻሻል ሲሆን ለወጣቶቹ መሳሳብ ቀጥታና ተዘዋዋሪ ምክንያት (ውበት፣ ሀብት፣ ፀባይ፣ ማህበራዊ ሚና፣ ወዘተ) እንደሚኖር የታወቀ ነው። ሆኖም ሲፈላለጉ የተሳሳቡበት/ የተማረኩበት ነገር ሲለወጥ ወይም ወረቱ ሲያልቅ መውደድ ሚዛኑን ያጣና በሰበብ አስባቡ አለመግባባትና የፍቅር መሻከር ይከተላል። ሲተጫጩ ሊማረኩበት የቻሉበት ነገር የፍቅር መነሻ መሆኑ ባይከፋም በመንፈሳዊ ኃይል ካልተጠናከረ መጀመሪያ ያሳሳባቸው ነገር ቢለወጥ፣ መንፈሳዊ እምነትና የቤተሰብ ጫና በበጎ መልኩ መፍትሔ ሊሰጥ የሚችልበት ኃይል ስለማይኖር የጋብቻው ኅልውና አደጋ ላይ ሊወድቅ ይችላል። ቤተሰብም የመበተን ዕድል ሊያጋጥመው ይችላል። እንዲየውም ሠልጥኗል በሚባለው ዓለም ውስጥ የግለሰብ መብት በከፍተኛ ደረጃ ስሚከበርና ይህም ለማኅበራዊ ፍላጎት ሳይሆን ለግለኝነት የሚያመቻች ስለሆነ በቅዱስነቱ ልጆችን ወልዶ በጋራ በአንድ መንፈስ በማሳደግ ፋንታ ጋብቻ እንደማንኛውም ኮንትራት እየታየ ጥቅሞችን እንደመስጠትና መቀበል ያሉ ቁሳዊ ልውውጥ ተራ ባህርይ ውስጥ ስለሚገባ ማኅበራዊ እሴትነቱና ለዛው ጠፍቶ በሕግ ሽፋን ውስጥ ብቻ እርቃኑን ስለሚቀር ፍቅር አልባ ይሆናል፤ ዓላማውን ለመፈጸም ብቃት ከማጣቱም በላይ ሕልውናውም አስተማማኝ አይሆንም።
በሌላ መልኩ ዛሬ በመብት ስም በተለይም ሠለጠኑ በሚባሉት አገሮች እየተከሠተና አልፎ አልፎም በመንግሥት ደረጃም ዕውቅናን ያገኘው እጅግ አሳፋሪ የሆነው የተመሣሣይ ፆታ ጋብቻ /same sex marriage/ ጉዳይ ሲሆን ኅብረተሰባችን ውስጥ ያልገባ ቢሆንም በተለይ በመደበኛ ትምህርት ቤት በሥነፍጥረት /biological science/ ትምህርት የሰዎች የግል ምርጫ መሆኑን እንዲያይ ተደርጎ የሚማረው ወጣት በማኅበራዊ ኑሮ ላይ የሚያስከትለውን አደገኛነት ጠንቅቆ እንዲያውቀው ማድረግ ያስፈልጋል።

ስለተመሣሣይ ፆታ ግንኙነት ወይም ጋብቻ እግዚአብሔር በሰዶምና ገሞራ ሕዝቦች ላይ ቅጣት በመፈጸም ለዓለም ሕዝብ ትምህርት ሰጥቷል። ይህም በኦሪት ዘፍጥርት ም ፲፰ እና ፲፱ ላይ ተገልጿል። ሰዶምና ገሞራ በሚባሉ በዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻ በሚገኙ ሁለት የጥንት ከተሞች ውስጥ እግዚአብሔር ከፈቀደው የተፈጥሮ የፆታ ግንኙነት ውጭ ወንድ ከወንድ እየተገናኘ ኃጢአት ስለበዛ እግዚአብሔር ከተማውን ከነሕዝቡ ሊያጠፋ እንዳሰበ ለአብርሃም ነገረው። አብርሃምም ጥቂት ንጹሐን ሰዎች ቢገኙ እንዲምርለት ለምኖት ፲ እንኳን ንጹሐን ሰዎች ቢገኙ በነዚያ ምክንያት ሁሉንም እንደሚምርለት እግዚአብሔር ቃል ገባለት። በመሸ ጊዜ ሁለት ሰዎች ወደሰዶም ገቡ፤ ሎጥም በሰዶም በር ተቀምጦ ነበር፤ ሎጥም በእንግድነት ተቀብሎ ያሳድራቸው ዘንድ ለመናቸው፤ በቤቱም አስተናገዳቸው፤ ሆኖም የሰዶም ሰዎች ተሰብስበው እንደተለመደው ሁለቱን ሰዎች በግበረሥጋ ሊደፍሯቸው የቤቱን በር ሰብረው ሊገቡ ሎጥን በታገሉት ጊዜ በሰዎች ተመስለው የመጡት ሁለት እንግዶች መላእክት ስለነበሩ ሕገወጦቹን ሰዎች አሳወሯቸው፤ ሎጥንም አሉት፣ ቤተሰብህን ይዘህ ከዚህ ከተማ ውጣ፤ እኛም ይህን ከተማ እናጠፋዋለን አሉት፤ በዘገየ ጊዜም አዝነውለት እጁን ይዘው አወጡት፤ ወደኋላም እንዳያይ ነገሩት፤ ከነቤተሰቡም ከሰዶም ወጥቶ ከመቅሰፍቱ ሲድን ሰዶምና ገሞራ ከነሕዝቡ ተቃጠሉ፤ ሆኖም የሎጥ ሚስት ወደኋላ ስለተመለከተች የጨው ሀውልት ሆና ቀረች። ከዚህ በኋላ ሕገወጥ የፆታ ግንኙነት ግብረሰዶም ተባለ።

ዛሬ ያለው ችግር በአንዳንድ ማህበረሰቦች ዘንድ እንዲህ ያለ የፆታ ሥርዓት እንደ የግለሰብ ነፃነት ወይም የፆታ ግንኙነት ምርጫ መታየቱ ሲሆን ሊሰመርበት የሚገባው ጉዳዩ በግለሰብ ላይ ብቻ ሳይቆም ቤተሰብን፣ ብዙሓን ሕዝቦችን፣ እንዲሁም አገርን የሚበክል ነገር መሆኑ ነው።
The liberal choice for sexual orientation does not stop on an individual. Homogeneous marriage distorts the basic fabric of the social network reflected in a natural family of parent-offspring relationship by obliterating this human relationship and throwing it into the abyss of mere sexualized instinct.

ባሁኑ ጊዜ በአንዳንድ መንግሥታት የተመሣሣይ ፆታ ጋብቻ መፈቀድ በጥንቃቄ ሊታይ የሚገባው ጉዳይ ነው። ሰዎች በዚያ ባሕርይ በመነደፋቸው ምክንያት ኅብረተሰቡ እየተጸየፋቸው ስላገለላቸው ራሳቸውንም እስከማጥፋት የደረሱ ስላሉ በአብዛኛው መንፈስ መድልዎ /discrimination/ ሳይፈጸምባቸው እንደሌሎች ዜጎች በሰላም የመኖር ነፃነት እንዲኖራቸው ተብሎ አገርን ከማስተዳደር አንፃር እየተወሰደ ያለ እርምጃ ነው አንጂ ትክክል ሆኖ አይደለም ። ለምሳሌ ሲጋራ አጫሾች ሰብአዊ መብት ተጠብቆላቸው በተከለለ ቦታ ማጨሳቸው ምርጫቸው ተቀባይነት አለው ማለት አይለም፤ ሲጋራንም የጤንነት ጠንቅ ከመሆን አያስቀረውም። ከሰብአዊነትና ደህንነት አንፃር የግለሰቦችን ነፃነት ለመጠበቅ የሚወሰደው ሕጋዊ አቋም ወይም አስተዳደራዊ እርምጃ የግለሰቦቹን ጥፋትና ስህተት ትክክለኛ አያደርገውም፣ መቻቻልን /tolerance/ እንጂ። በመንፈሳዊ መንገድም ብናየው እግዚአብሔር ሕግን የሰጠን በፈቃዳችን አንድንፈጽም ሲሆን ሕጉን ባለመከተል ኃጢአት ብንሠራ የምናጣውን ሁሉ ገልጾልናል (፩ኛ ጴጥሮስ ፪፡ ፲፮፣ ገላትያ ፭፡ ፩ የዮሐንስ ወንጌል ፰፡ ፴፩-፴፮)፤ ለመዳን ፈቃደኞች ካልሆንን እና የመዳኛውን ሕግ ትተን የመሞቻውን ነፃነት የምንመርጥ ከሆነ እንጎዳበታለን። ስለሆነም የእግዚአብሔርን ሕግ ከመከተል በስተቅር ሌላ የሚጠቅም አማራጭ እንደሌለ ማውቅ ብልህነት ነው።

የተፈጥሮ ቤተሰብና ሚናው፣
ሰው ሊወለድ የሚችለው ከተፈጥሮ እናትና አባት ብቻ ነው። ሆኖም በማደጎ እጅ ላይ የወደቀ ልጅ የማደጎ ወላጆቹ ምንም ያህል ደጋግ ቢሆኑ የማንነት ጥያቄ ማንሳቱ አይቀርም፤ ይህ ደግሞ የሥነልቡና ችግር ይኖረዋል። ወላጆቻቸው የሞቱባቸው ልጆች እንኳ ከማደጎ ወላጆች ጋር የሚኖራቸው ግንኙነት እስከሞት ድረስ ያደረሰ ቀውስ ማስከተሉ በየጊዜው በዜና ማሠራጫዎች ይሰማል። በአሜሪካን አገር ብቻ ከ፲፱፻፹፱ እስከ ፳፻፲፫ ዓም በማደጎ ከውጭ አገር ከመጡ ሕፃናት ውስጥ ፪፻፺፫ ሞትና ሌላ ከባድ ጉዳት እንደደረሰባቸው ኒጌል ባርበር የተባለ ሳይኮሎጅስት ካቀረበው ስታትስቲከስ ታውቋል።

የተመሣሣይ ፆታ ጋብቻ ብለው ግብረሰዶማውያን የሚጠሩት እውነተኛ ጋብቻ ሳይሆን ሕገወጥ እና በወሲብ ላይ ያተኮረ ግንኙነትና ዝሙት ነው። በአሁኑ ጊዜ ዓለምን እየበከለ ያለው የተመሣሣይ ፆታ ጋብቻ ዓላማው ፍትወተሥጋ (ወሲብ) ብቻ ሲሆን ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት የሚለውን አምላካዊ ቃል የሚፃረር ስለሆነ ልጆች ከወላጆቻቸው ውጭ በእንጀራ እናት ወይም እንጀራ አባት ሥር ስለሚያድጉ የእናት-አባት የወንድም-እህት ወዘተ ቤተሰባዊ ፍቅርና ጣእም ከቶውንም ያጣሉ። ምክንያቱም ከተቃራኒ ፆታዎች (ባልና ሚስት) ውጭ የሚጋቡ ሰዎች ልጅ ለማግኘት በማደጎ ማምጣት አለበለዚያም አመንዝራ የመፈጸም ምርጫ ውስጥ ይገባሉ። እግዚአብሔር ለሰዎች የፈቀደውን የወላጅ-ተወላጅ የተፈጥሮ ሕግ ተከትሎ በቤተሰባዊ ግንኙነት ማኅበራዊ ኑሮ በመኖር ፋንታ እንደ እንሰሳ በዘፈቀደ የመገናኘትና አንደከብት የአባቱን ማንነት ጥያቄ ውስጥ የሚጥል ተወላጅን (offspring) ያስከትላል። በዚህ መልክ ልጆች የተባሉ ተወላጆች ሁሉ እውነተኛ አባትና እናት ሳይሆን በማደጎ ወላጆች ሥር ስለሚያድጉ ይህ የትውልድ ሐረግን ስለሚያጠፋ ሰዎችን በዝምድና ማየት ሳይሆን በአካል ብቻ የመቁጠር ዕድል ስለሚያስከትል ፍቅር፣ ኃላፊነት፣ ሞራል፣ የማንነት ጉዳይ…ወዘተ እየደበዘዙ ሰብአዊነት በእንሰሳዊ ባሕርይ ይዋጣል።

ቤተሰብ ከእግዚአብሔር የተሰጠን በረከትና ልጆች በማኅበራዊ ፍጡርነት ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ፀጋ ፍቅርን የሚያዩበት፣ የሚገልጹበት ትንሹ የኅብረተሰብ ሕዋስ ነው። “ዞሮ ዞሮ ከቤት ኖሮ ኖሮ ከመሬት…” እንደሚባለው ቤተሰብ ተወዳዳሪ በሌለው መስዋዕትነት የተፈጥሮ ፍቅር የሚተገበርበትና ልጅ በወላጁ፣ ወላጅ በልጁ..ወዘተ ፍጹም ተስፋ የሚጥልበትና የሚመካበት የአለኝታነት መገለጫ ነው፤ ቤተሰብ የሰዎች ሰብአዊ ክብርና የትውልድ ሐረግን ተከትሎ የሚመጣ ወግና የማንነት መግለጫ ነው፤ ቤተሰብ በተፈጥሮ የሚተማመኑበት የአንድነትና የባለቤትነት መገለጫ አካል ነው፤ ቤተሰብ የራሴ ከሚሉት አካል ጋር በእውነት ስለ እውነት ከምንም ጋር በማይተካከል ነፃነት የሚገናኙበት በእግዚአብሔር ፀጋ የተገኘ ሕዋስና ርህራሄን፣ ምህረትን፣ ይቅርታንና ልግሰናን የሚያገኙበት ትንሹ መንግሥት ነው፤ ቤተሰብ ተወዳዳሪ በሌለው ቅንነት ኃላፊነት የሚፈጸምበት የኅብረተሰብ አካል ነው። ቤተሰብ ይህን ሁሉ ማኅበራዊ እሴት ተሸክሞ የሚቆም የኅብረተሰብ ምሰሶ ነው። ነገር ግን ከላይ እንደተገለጸው የተመሣሣይ ፆታ ግንኙነት ሕገወጥ ከመሆኑም በላይ ቤተሰብን መሠረት ያሳጣዋል።

መልካም ባህላችንን ጠብቀን ለሌላው ዓለም ማስተማር፣
ምሰሶ ከተዛባ ቤት እንደሚናጋ ሁሉ ቤተሰብም ከእግዚአብሔር የተሰጡትን ማኅበራዊ እሴቶች መሠረት ካጣ ኅብረተሰብ ይናጋል፤ የሰው ልጅም መንፈሳዊ ኃይሉን ስለሚያጣና ለእንሰሳዊ /instinct/ ሥጋዊ ፍላጎት በመገዛት ሙሉ ሰብአዊነቱን ስለሚያጣ የራሱን ክብር ዝቅ ያደርጋል። በዚህ የተነሣ መንፈሳዊ ሙሉነት አይሰማውም። ሰብአዊ ክብሩን የማይጠብቅ ሰው ጥሩ ማኀበራዊ ባህል ሊኖረው አይችልም። ፍቅር፣ ኃላፊነት፣ ይሉኝታ፣ ሞራል በተሞላበት ማኅበራዊ ባህል ያልተገነባ ቤተሰብ ደግሞ ለቁሳቁስና ግብረሥጋ ግንኙነት የሚተባበር ልቅ የሰዎች ስብስብ ስለሚሆን ለማናቸውም ሕገወጥ ተግባሮች የተጋለጠ ነው፤ ምክንያቱም ሥጋዊ ፍላጎቱን ሊገዛ ካልቻለ እንኳንስ ለመንፈሳዊ ሕይወት ቀርቶ ሰው-ሠራሽ ለሆነውም የመንግሥት ሕግ መገዛት አይችልም። ስለዚህም ነው የአመንዝራ ትውልድ እየበዛ የአንድ ወላጅ ልጆች የሚበዙበትና ስብእናቸው ያልተሟላ ስለሚሆን ቁሳዊ ችግር እንኳ ሳያግጥማቸው ሰዎች በመንፈስ ጭንቀት ሐሳርና መቅስፍት የሚደርስባቸው።

ሰው ራሱን መግዛት አቅቶት በሥጋዊ ፍላጎቱ ከተሸነፈ ለእንስሳዊ ባህርይ ስለሚገዛ የራሱን ሰብአዊ ክብር ከማጣቱም በላይ የቤተሰቡን /ዘመዶቹን/ የተፈጥሮ ግንኙነት በጣጥሶ ህልውናቸውን ያጠፋል። ቤተሰብ ጠንካራ ማኅበራዊ መሠረት ከሌለው ደግሞ አንድነት የሌለው በደመነፍስ ፍላጎት የተሞላ የግለሰቦች ጥርቅም ስለሚሆን አጥንት እንደሌለው ሥጋ የመፈራረስ ዕድል ውስጥ ይወድቃል። የቤተሰብ መዳከም ደግሞ የኅብረተሰብን ድርና ማግ ይበጣጥሰዋል፤ ይህም መልካም ሰብእናን የሚያሳሳ ስለሚሆን የአገርን ማኅበራዊ እሴቶች በማጥፋት ዜጎችን ከኅብረተሰቡ ጋር ትሥሥር ሳይኖራቸው የግል ፍላጎታቸውንና ጥቅማቸውን ለማሟላት ብቻ የሚፈልጉ በዘፈቀደ ስሜት የሚመሩ የግለሰቦች ክምችት በማድረግ ሰብአዊነትን ስለሚያጠፋ ለመልካም አስተዳደር መጓደል ከፍተኛ አስተዋፅዖ ሊያደርግ ይችላል።
“እንሰሳ ሰው ሆነ ሰውም እንሰሳ ሆነ” እንደተባለው ከኅብረተሰባችን ውጭ ያሉትም ቢሆኑ በአርዓያሥላሴ የተፈጠሩ ስለሆኑ በዚህ መነሻውም ሆነ መድረሻው ወሲብ ብቻ በሆነ ባህርይ እየተለከፉ ከሄዱ ይህ ልምድ ለሥጋቸውም ሆነ ለነፍሳቸው የዘለቄታ ጥቅም ስለሌለውና በመጨረሻም ትውልዳቸውን ጭምር እያበላሸ ተጨማሪ ማህበረሰቦችንም ሊበክል ስለሚችል ከዚህ ልምድ እግዚአብሔር እንዲያወጣቸው ልንፀልይላቸው ይገባል። ሆኖም በእነዚህ ርካሽ በሆኑና በእንሰሳዊ ደመ-ነፍስ (instinct) ባህርይ በተበረዙ ልማዶች የራሳችንን መልካም ባህል ማዳከም የለብንም፤ የአገራችንን የጋብቻ ሥርዓት በአጠቃላይም በመልካም ባህላችን ውስጥ ያሉ ማኅበራዊ እሴቶቻችንን እያዳበርን ልንጠብቃቸው እና ሌሎችን ኅብረተሰቦች ልናስተምራቸው ይገባናል እንጂ።
ይህ ክስተት ወደ ባህላችን ዘልቆ ስላልገባ አሳሳቢ የማይመስላቸው የዋህ ወገኖች አሉ። ይኽም ራሷን አሸዋ ውስጥ ደብቃ የሚሆነውን ሁሉ አላይም ብላ የቀረውን አካሏን ለአደጋ እንደተወችው እንሰሳ እንደመሆን ነው። ሆኖም ዛሬ ዓለም እየተቀራረበች ባለችበት ዘመን በተለይ ወጣቱን ትውልድ በቅድሚያ በማስተማር በአገሩ ባህል ሙሉ እምነት አድሮበት ከዚህ መጥፎ ባህል ራሱን እንዲጠብቅ በወቅቱ ማስገንዘብ ይመረጣል።

አዲስ ፕሬዚደንት በአዲስ ዓመት –በተክሉ አባተ

$
0
0

ይድረስ ለአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ፡

unknown_personጤና ይስጥልን አቶ አንዳርጋቸው እንደምን አሉ ፤ በኢሳት መስኮት እንዳየሁዎ ጤናዎ በመልካም ሁኔታ ላይ ይገኛል ብየ እገምታለሁ ። እንደባህላችን ከብቶቹስ እንዴት ናቸው እንዳልልዎ ኤርትራ ከብት ለማርባት እንዳልሄዱ አውቃለሁና ምንም እንዲሉኝ አልጠብቅም ። ልጆቹስ እንዳልል መንታዎቹ ልጆችዎ በ single  mother ለንደን በእንክብካቤ እያደጉ መሆኑን ስለሰማሁ በጥያቄ አላስቸግርዎትም ። ትግሉ ብል ይሻላል እንዴት ነው እየሰመረ ነው ? በረሃውን እየለመዱት ነው ? በቃ የግንቦት ሰባት ህዝባዊ ህይል በየጦር ሜዳው ወያኔን እያርበደበደው ነው አይደል ? እንግዲህ አራት አመት ሞላዎ እኮ ! ዘመኑ እንዴት ይሮጣል ጃል ።  ቀጣዩን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

Viewing all 1664 articles
Browse latest View live


<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>